Tuesday, September 30, 2014

በልበሌቲ ጽጌ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን

በልበሌቲ ጽጌ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ከአዲስ አበባ 418 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል። ቦታውም ለመድረስ ከአዲስ አበባ በናዝሬት፣ አሰበ ከዛም በበዴይሳ አድርገው ወደ ገለምሶ ይጓዛሉ በመጨረሻም ቤተክርስቲያኑ የሚገኝበት በልበሌቲ መሻገር ይኖርቦታል። መንገዱ ለማንኛውም መኪና ምቹና ቤተ ክርስቲያኑም መንገድ ዳር በመሆኑ ምንም እንግልትና የእግር ጉዞ የለውም።

ይህ ቤተ ክርስቲያን የሚገኘው በምዕራብ ሐረርጌ ሐብሮ ወረዳ በልዩ ስሙ በልበሌቲ በመባል በሚታወቀው መንደር ሲሆን ለምዕራብ ሐረርጌ የመጀመሪያው ቤተክርስቲያን ነው። የተተከለውም በእምዬ ምንሊክ በፊታውራሪ ዘመንፈስ በ1870 ከአርሲ እያስገበሩ ሲመጡ በምዕራብ ሐረርጌ ሲያልፉ እንደተከሉት ይነገራል። ቤተ ክርስቲያኑ ሲዘዋወር አሁን ያለበት ቦታ ሰባተኛው ሲሆን እምዬ ምንሊክ ለቤተ ክርስቲያኑ የሰጡት ርስት 18 ጋሻ መሬት ቡሩሪ በሚባል ቦታ ህንጻውም ባለ ደርብ(under ground) የሆነ ነበር። በጣልያን ወረራ ጊዜ ቤተ ክርስቲያኑ በመቃጠሉ ከተሰጠው ርስት በመነሳት በሽሽት ቀርጫ የሚባል ጫቃ ውስጥ ለ 5 ዓመት ስብሐተ እግዚአብሔር ሲደርስ ቆይቷል። በዚህ ወቅት ያ 18 ጋሻ መሬት የለውም እዛ ቦታ ላይ ሌሎች ሁለት ቤተ ክርስቲያን ታንጸው እሱ የሚገኘው ሌላ አዲስ በተመራው ቦታ ላይ ነው። በዚህ ቤተ ክርስቲያን የሚነግሱ ታቦታት ሶስት ሲሆኑ እነሱም ቅዱስ ጊዮርጊስ በሚያዚያ 23ና ጥር 18፣ ኪዳነ ምህረት በየካቲት 16፣ ሩፋኤል በጷግሜ 3 ይነግሳሉ።

ደብሩን ምን ልዩ ያደርገዋል

ስለት ሰሚነቱ
በአገር ውስጥም ከአገር ውጪም ባሉ የአካባቢው ሰዎች የበልበሌቲው ጊዮርጊስ አንተው ስለቴን ፈጽምልኝ ብለው የተሳሉ ሁሉ ላመኑት ክርስቲያኖች ብቻ ሳይሆን ከክርስናው ውጪ ላሉትም ሰዎች እንኳ ሳይቀር ስለታቸው ደርሶላቸው በድብቅ (ሰው በመላክ) በግልጽም (ራሳቸው በመምጣት) ስለታቸውን ይልካሉ። በሐኪም እንደማይወልዱ የተነገራቸው፣ ትዳር ያጡ፣ በህመም የሚሰቃዩ፣ ውስብስብ ችግር የገጠማቸው፣ ብዙ ብር ጠፍቶባቸው የነበሩ ሌሎች ሌሎችም የህይወታቸው እንቆቅልሽ ተፈቶላቸው አምላከ
ቅዱስ ጊዮርጊስ ይክበር ይመስገን ብለው አመስግነዋል። እኛም ዛሬ ምንም ለኛ ከባድ የመሰለን ችግር ቢገጥመንም የበልበሌቲው ቅዱስ ጊዮርጊስ ብለን ብንሳል በእርግጠኝነት ስለታችን ደርሶ እርሱን ለማክበር በልበሌቲ እንሄዳለን።

ማስታረቅ(ማስተማመን)
የማስታረቅ(የማስተማመን) ሁኔታ የጨለማን ሥራ ወይም ጨለማን ተገን አድርጎ በደል ሲፈጸም የተጠቃው ሰው ጠላቱን ካላወቀው ወይ ከተጠራጠረው ለቤተ ክርስቲያን መጥቶ ይናገራል፤ ከህናቱም ታምረ ማርያም ከተነበበ በኋላ እንዲህ እንዲህ ያደረክ ሰው መጥተህ አጥፍቻለው ብለህ ተናገር ተብሎ ከሁለት እስከ ሦስት እሁድ ይታወጃል ከዛ ያሰው በስውር እራሱን ለካህን ከተናገረ ካህናቱ ያስታርቋቸዋል እኔ ነኝ የሚል ከጠፋ ግን ታምረ ማርያም ይታጠፍና መቋሚያ ተጥሎ ይረገማል ከሳምንት እስከ ወር ባለው ጊዜ ውስጥ ያንን ክፉ ተግባር የፈጸመው ሰው በግልጽ የሆነ ጉዳት ደርሶበት ይታወቃል። በዚህም ምክንያት የአካባቢው አስታራቂ እንዲተማመኑ የሚያደርግ ከክፉ ሥራ እንዲታቀቡ የሚገስጽ በመሆኑ ህዝቡ አቤቱታውን ለቤተ ክርስቲያን በማሰማት ሰላሙን ያገኛል።

የአገልጋዮቹ ፍቅር
በዚህ ደብር ከትንሽ እስከ ትልቅ የአገልጋዮቹ እንዲሁም የሕዝቡ ፍቅርና አንድነት ልዩ ነው። በተለይ ፍቅር ጠፍቶ ጭቅጭቅ የሚበዛበት ደብር ላለ ሰው እዚሁ መቅረትን ያስመኛል። በተጨማሪም የቤተ ክርስቲያናችንን ሥርአት አዛዥ ኖሮባቸው ሳይሆን በፍቅር ስለሚያገለግሉ በትክክል ጠብቀው የሚሄዱ በመሆናቸው ምዕመኑም በካህናቱ አገልግሎት ስለሚረካ በአገልጋዮቹ ላይ ምንም ቅሬታ ሳይኖረው በጥምረት እግዚአብሔርን ያመሰግናል። ሌላው ይሄንን ደብር ለየት የሚያደርገው በፍልሰታ ጾም ወቅት ከየት መጣ የማይባል ነብር ከ16ቱ ቀን አንድ ቀን መታየቱ ነው። አይተናኮልምም።

በደብሩ የተፈጸሙ ተዓምራቶች
ዝርፊያ
አንድ ኢአማኒ በ1983 ዓ/ም በነበረው የመንግስት ለውጥ ቤተ ክርስቲያን መጥቶ ታቦቱ ለጥምቀት የሚያድርበትን ድንኳንና መጾር መስቀል ወስዶ መስቀሉ ወርቅ መስሎት ቢሸርፈው አብዶ እየለፈለፈ ውሰዱልኝ ብሎ ለካሕናቱ አስረክቧል። ከዚያ በኋላ እርሱ ምላሱ ተሰንጥቆ ሰውነቱ በሙሉ ቆስሎ ከንፈሩንና የተሰነጠቀውን ምላሱን እየበላ ሰውነቱ በጠቅላላ ተልቶ ሞቷል። በሱ ብቻ አላባቃም የ8 ወር እርጉዝ ሚስቱ፣ ልጆቹ፣ ከብቶቹ፣ ዘመዶቹ ሁሉም አልቀው አንድ ለምስክር ወንድሙ ቢቀር እርሱም እጁና እግሩ ተንጋዶ ቀርቷል። በዚያኑ አመት ሌሎች ዘራፊዎች መጥተው የቤተ ክርስቲያኑን ቁልፍ ሰብረው በሩ አልከፈት ቢላቸው ሲቀጠቅጡ አድረው ሲነጋባቸው ትተውት ጠዋት ካሕናቱና ሕዝቡ ተሰባስበው በስንት እግዚኦታ ከፍተው ገብተው ኪዳን ማድረስ ችለዋል። ይህ ሁሉ የመጣው ቤተ ክርስቲያኑን የሚጠብቅ ጠባቂ(ዘበኛ) ባለመኖሩ ቢሆንም ሰማዕቱ ግን የራሱን ቤት እራሱ እየጠበቀ ይገኛል። እስካሁንም ግቢው ዘበኛ የለውም። ምንም እንኳን ቤተክርስቲያኑ መንገድ ዳር ቢሆንም ደጀ ሰላሙ ላይ ያለውን ሙዳየ ምጽዋት እዛው ውሎ ቢያድርም የሚዳፈረው የለም።

ልዩ መዐጠንትና መዓዛ
መስከረም 27/ 2004 ከቀኑ 11፡30 በእለቱ የሰርክ ጉባኤ እንዲጀመር መዝሙር ለመክፈት ወደ ቤተ መቅደሱ የገቡት ካህን ምንም የሚጨስም ሆነ የሚሸት መዓዛ ባይኖርም መዝሙሩ ተከፍቶ የመጀመሪያው የካሴት አንዱ ክፍል እንዳለቀ ካሴቱን ለመገልበጥ ወደ መቅደሱ ሊገቡ በሩ ጋር ሲደርሱ ይሄ ነው የማይባል ልዩ መዓዛ ይሸታቸዋል እሳቸውም ተመልሰው ለአንድ መምህር ስለ ማዕዛው ቢነግሯቸው መምህሩም አንገታቸውን አስገብተው ቢያሸቱ ያ የተባለው ልዩ መዓዛ ይሸታቸዋል። ይሄን የመሰለ መዓዛ ከየት ሊመጣ ይችላል ብለው በመደናገጥ የመቅደሱን መብራት እንዲታያቸው ቢያበሩት ምንጩ የማይታወቅ ጉም የመሰለ ነገር መቅደሱን ሞልቶት ሁለቱ መተያየት አልቻሉም ነበር። መቼ የተረሳ እሳት ነው ተብሎ ቢፈለግ እሳት ሊገኝ አልቻለም የእሳቱን ምንጭ ለማወቅ አሁንም ቤተልሔም ቢኬድም የተቀጣጠለ እሳት የለም መቅደስ ገብተው ቢመለከቱ ልክ ለቅዳሴ እንደሚዘጋጀው መጎናጸፊያውም መስቀሉም በትክክል ተቀምጦ አዩ ማን ይህን አደረገው በማለት ወደ ጽናው ዞር ቢሉ ማንም ያላስቀመጠው ሶስት ትልልቅ ፍም አገኙ። ካህኑም ህዝቡን ለመጥራት ደውሉን ይደውላሉ ይዝቡም ተሰበሰበ የተሰበሰበው ህዝብ ያ የሰው ቋንቋ የማይገልጸው መዓዛ ሲሸተውና ጉም የሚመስለውን ጢስ ሲመለከት ተያይዞ መላቀስ ሆነ እስከ ምሽቱ 2፡00 ሰዓት ህዝቡም እየመጣ መዓዛው ሲሸተው እያለቀሰ አምላኩን እያመሰገነ አመሸ ይህ ሲሆን ቅዳሜ ምሽት ለእሁድ አጥቢያ ነበር ሌሊት ለአገልግሎት ሲገባም ያው መዓዛ አልጠፋም ነበር ጠዋትም ቅዳሴ ለሚያስቀድሰው ሰው ሁሉ ይሸት ነበር። እግዚአብሔር ሥራው ግሩም ድንቅ ነው።

ጉሬዛ
በአካባቢው ጉሬዛ አይኖርም ነገር ግን በዛኑ አመት በአብይ ጾም አድራሻው የማይታወቅ ጉሬዛ ከቤተ ክርስቲያኑ ግቢ ውስጥ ካለ አንድ የባህር ዛፍ አጸድ ላይ ወጥቶ ለሶስት ቀን ከዛፉ ላይ ሳይወርድ ሳይንቀሳቀስ ምዕመኑ በትልልቅ ረጃጅም እንጨት የሚበላ ዳቦ እና ውሃ በቆርቆሮ ቢያቀርቡለት አልበላም አልጠጣም አለ ሁለት እናቶች ቢበላ ብለው ከዱር የሾላ ፍሬ ፈልገው ቢያመጡም እሱ ግን ለመብላት እሺ አላለም። በዚህ ሁኔታ ለሶስት ቀን ከዛፉ ላይ ቆይቶ ከኪዳን በኋላ በመጣበት አኳኋን እየሮጠ ሄዷል።

የመላእክት ማህሌት (ምሥጋና)
ይህ ቦታ ያለማቋረጥ ሰውና መላእክት ያመሰግኑበታል። የካቲት 12 2006 ዓ/ም ከሌሊቱ 6፡00- 11፡00 ሰዓት ቤተክርስቲያን ግቢ ውስጥ ያደሩት ካህናት ሳይሰሙ በከተማ ያሉ ምዕመናን ሰምተው ዛሬ እንዴት ያለ ማሕሌት ነው!? ኪዳነ ምህረት በ16 ነው የምትነግሰው በ12 ምንም ዓመታዊ ክብረ በዓል ሳይኖር እንዲህ ያለ ዜማ እንዲህ ያለ ማሕሌት እንዴት ሊኖር ቻለ!? ብለው በማድነቅ ቤተ ክርስቲያኑ ግቢ ውስጥ መጥተው ቅልጥ ያለ የደመቀ ማሕሌት እየሰሙ የቤተ ክርስቲያኑ በር ቁልፍ መሆኑን ባዩ ጊዜ ይበልጡኑ እየተገረሙ ቆመው ሌሊቱን ሙሉ በመደነቅ ሲሰሙ 11፡00 ሰዓት ላይ ደግሞ የህጻናት ድምጽ(ምሥጋና) ሲሰሙ እንዳደሩ ምዕመኑ በአንድ ድምጽ መስክረዋል ይመሰክራሉም። ታዲያ ካህናቱ ያልቆሙት ማሕሌት የመላእክት ካልሆነ የማን ሊሆን ይችላል!? ለዚህ አንክሮ ይገባዋል። ለዚህ ተዓምር መስካሪዎች ካህናቱ ሳይሆኑ ጠቅላላው ምዕመን ነው ምክንያቱም ካህናቱ አልሰሙምና።

የቅዱስ ጊዮርጊስ ምልጃና ረድኤት አይለየን። አሜን።
ዲ/ን ዳንኤል ክብረት

No comments:

Post a Comment