Tuesday, September 19, 2017

ሙስሊሟዋ ድንቅ ተዓምር በሸንኮራ ዮሐንስ ተደረገላት

" ደስታና ተድላም ይሆንልሃል፥ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል። በጌታ ፊት ታላቅ ይሆናልና፥ የወይን ጠጅና የሚያሰክር መጠጥ አይጠጣም፤ ገናም በእናቱ ማኅፀን ሳለ መንፈስ ቅዱስ ይሞላበታል።ከእስራኤልም ልጆች ብዙዎችን ወደ ጌታ ወደ አምላካቸው ይመልሳል " ሉቃ.1፡14
ሸንኮራው ቅዱስ ዮሐንስ ድንቅ ተአምር
ሃይማኖቴ "ወልድ ፍጡር፣ ቤተክርስቲያን ድንጋይ ናት" ሎቱ ስበሐት ። ከሚሉ አሕዛብ ወገን ነበርኩ የምትለዋ እህታችን መኖሪያዋ በመዲናችን አዲስ አበባ ነው ። ክርስቲያን የሚባል አልወድም፣ ፍጹም ጥላቻንም የተሞላው ነበርኩ። አምላኬን ያስደሰትኩ መስሎኝ አንድ አብሮ አደግ ክርስቲያን ጓደኛ አለችኝ። ብሰድባት ብተፋባትም ጉዳይዋ አይደለም ኣትቀየመኝም። ቅዱስ ዮሐንስን በጣም ትወደዋለች።
እኔ በስኳር በሽታ ምክንያት አንድ እግሬ በጋንግሪን (የተወሰነ አካል መሞት) እንዲቆረጥ ሐኪም ወሰነ። ያች ጓደኛዬ ግን የዮሐንስ ጸበልን ቤቴ አመጥታ ሰጠችኝ። ተቀብያት ከፊቷ ይህ እኮ "ውሐ" ነው ተረት አታውሪ ብዬ ስደፋው የጸበል ዕቃውን የያዘ እጄ ሰለለ ሽባ ሆነ፤ ደነገጥኩኝ። የጥፋተኝነት ስሜት ተሰማኝ። አይዞሽ ምልክት ነው መጥምቁ ያማልድሻል አለችኝ። "ኦፕራሲዮኑን ተይው አንቺ ካልዳንሽ እኔ ሃይማኖቴን እቀይራለው" ስትል ቤተሰቤ በሃሳብ ለሁለት ተከፈለ። እግሬ በአስቸኳይ ይቆረጥ ተብሏል። እግሬም ቁስሉ ሽታ አመጣ። በዚያ ላይ በሃይማኖቴ፣ ቤተሰቤ ሁሉ በአይነ ርግብ ተሸፍኖ የሚሄድ ነው። መገላለጥ የለም፤ "እዛ ብትሔጂ እንረግምሻለን" አሉኝ። በመጨረሻ ውሳኔ የኔ ሆነና ከሶስት ቤተሰብና፣ ከዚህችው ወዳጄ ጋራ ሸንኮራ ሄድን። ወደ ጸበሉ መውረድ አልቻልኩም አምጥተው አጠመቁኝ። ቁስሉ እንደቅርፊት ወደቀ። እንደውም ጸበሉን የደፋሁበት እጄ ዳነ። የምን መቆረጥ የምን ጋንግሪን።
የሕመሜም ምክንያት የነበረው 23 አመት ያሰቃየኝ ስኳሩም ዳነ። አብራኝ የሄደች አንድዋም ቤተሰቤ በፍንጢጣ ኪንታሮት ትሰቃይ ነበር የባህል መድሐኒት ወስዳ ጽኑ ህመም ላይ ነበረች እርስምዋ ዳነች።በሰማዕትነት ለአምላኩ ምስክር የሆነው መጥምቁ ዮሐንስ ከአምላክ አማልደህ ካዳንከኝ ጥላ በሬ ላምጣ አልልም አንተ ምስክር ለሆንክለት “በክርስቲያን አምላክ በኢየሱስ ክርስቶስ አምናለው” ብዬ ነበር።
ይህም ድኜ ለስዕለቴ በቃው ከስምንት ቤተሰቤ ጋር ሃብተ ወልድና ስመ ክርስትና ተቀበልኩኝ። ትለናለች።
እህተ ዮሐንስ፤ፍቅርተ ዮሐንስ፤ወለተ ብርሐን፤ተጠምቀ መድህን፤ክፍለ ዮሐንስ፤ገብረ ዮሐንስ፤ወልደ ዮሐንስ፤አርከ ዮሐንስ ተብለን የቀራኒዮ ቤዛ ወደ አብ ወልደ ማርያም ኢየሱስ ክርስቶስ ነቢይ ሳይሆን አምላክ እንደሆነ አምነን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠምቀናል።
ቅዱስ ዮሐንስም ተአምር ግን ድሮ ነው የጀመረው ጎረቤቴ ዝክሩን ስታደርግ አትጥሪኝ እላት ነበር። ዝክሩንም አልበላም ጣኦት አምላኪ አድርጌ ነው የምቆጥራት። የክርስቲያኖች አምላክም ብዙ ነበር የሚመስለኝ። አወይ አለማወቅ በድብቅ ግን ዝክሩን በልጆች ስም አስመጥቼ እበላ ነበር።ይጣፍጠኛል ለካ በስተመጨረሻው የሕይወት እንጀራን ስጋ ወደሙ ሊያበላኝ ኖሯል እንዲያ የጣፈጠኝ፤ ትላለች እህታችን በጥምቀቱ ስነ ስርአት በዓይኔ በአካል ተገኝቼ በከተማችን በሚገኝ አንድ አጥቢያ ተከታትያለው ይለናል አንተነህ ሐይሌ።
እኛ የእምነት አቃቂር ስናወጣ ጥቅስ ስናገላብጥ የዛሬ 2000 አመት አንገቱ የተቆረጠው መጥምቁ ዮሐንስ ስንት የጠፋውን መንጋ ጥቅስ ሳይጠቅስ ቃላት ሳያዥጎደጉድ በፍቅሩ አስሮ በምልጃው ጠብቆ ለጌታው ምርኮን አስገባ። ይህን ያደረገ የመጥምቁ አምላክ ክብር ይግባው ዮሐንስ ነቢይ ሰማዕት እኛንም ያማልደን አሜን።
ከአንተነህ ኃይሌ ገጽ ተገኝቶ ጥቂት እርማት የተደረገበት የእውነት ምስክርነት። ወደፊት ግለሰቦቹ አነጋግረን የበለጠ መረጃ ለማድረስ እሞክራለሁ። “ እላችኋለሁ፥ እንዲሁ ንስሐ ከማያስፈልጋቸው ከዘጠና ዘጠኝ ጻድቃን ይልቅ ንስሐ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ በሰማይ ደስታ ይሆናል።”ሉቃ 15:7

No comments:

Post a Comment