Showing posts with label አቡነ ኤዺፋንዮስ. Show all posts
Showing posts with label አቡነ ኤዺፋንዮስ. Show all posts

Tuesday, September 1, 2015

አቡነ ኤዺፋንዮስ

ግንቦት 17- ዕረፍቱ ለአቡነ ኤዺፋንዮስ፡- "ኤዺፋንያ" ማለት የመለኮት መገለጥ ሲሆን "ኤዺፋንዮስ" ማለት ደግሞ ምሥጢረ መለኮት የተገለጠለት ማለት ነው::
ቅዱስ ኤዺፋንዮስ የተወለደው ክርስቶስን ከሚጠሉ አይሁዳውያን ቤተሰቦች ሲሆን ቤተሰቦቹ ከአንድ አህያ በቀር ምንም የሌላቸው ድኆች ነበሩ፡፡ በዚያ ላይ በልጅነቱ አባቱ በመሞቱ ከእናቱና ከአንዲት እህቱ ጋር በረኃብ ሊያልቁ ሆነ፡፡ ሕጻኑ ኤዺፋንዮስ በአህያው እንዳይሠራ አህያው ክፉ ነበርና በእናቱ ምክር ሊሸጠው ገበያ አወጣው፡፡ ሊሸጠውም ከአህያው ጋራ ሲጓዝ ፊላታዎስ ከሚባል ጻዲቅ ክርስቲያን ጋር ተገናኘ፡፡ ፊላታዎስም ሊገዛው ፈልጎ ለግዢ ሲደራደሩ አህያው የኤዺፋንዮስን ኩላሊቱን ረግጦት ለሞት አደረሰው፡፡ በዚህ ጊዜ አብሮት ያለው ጻድቁ ክርስቲያን ፊላታዎስ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ብሎ በትእምርተ መስቀል አማትቦ በቅፅበት አዳነው፡፡ አህያውንም "ስለ እኛ በተሰቀለው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ትሞት ዘንድ ይገባሃል" ብሎ በቃሉ እንዲሞት ቢያዘው አህያው ወዲያው ሞተ፡፡ ኤዺፋንዮስም እነዚህን አስገራሚ ሁለት ተአምራት ካየ በኀላ ጻድቁን ክርስቲያን "በስሙ ተአምራት የምታደርግበት የተሰቀለው ኢየሱስ ክርስቶስ ማነው?" አለው፡፡ ፊላታዎስም ክርስቶስን ሰበከለት፣ ኤዺፋንዮስም እያደነቀ ሔደ፡፡
ከወራት በኀላ ሀብታም አይሁዳዊ አጎቱ ወሰደውና ገንዘቡን ሁሉ አውርሶት ስለሞተ ኤዺፋንዮስ ገና በ16 ዓመቱ ባለጠጋ ሆነ፡፡ የኦሪትን ሕግ ሁሉ እየተማረ ቢያድግም ያቺ ገበያ ላይ ያያት ተአምር ግን በልቡ ውስጥ ትመላለስ ነበር፡፡
በአንዲት ዕለትም ስሙ ሉክያኖስ ከሚባል ጻድቅ መነኩሴ ጋር ተገናኘ፡፡ አብረው ሲሔዱም አንድ ነዳይ አገኙና ምጽዋትን ጠየቃቸው፡፡ ጻድቁ ሉክያኖስም ገንዘብ ስለሌው የሚለብሰውን የጸጉር ዐፅፉን አውልቆ ለድኃው መጸወተው፡፡ በዚያን ጊዜ የብርሃን ልብስ ከሰማይ ሲወርድለት መላእክት ሲያለብሱት ኤዺፋንዮስ ተመለከተ፡፡
ይህንንም ድንቅ ነገር ከተመለከተ በኀላ ኤዺፋንዮስ ከመነኩሴው እግር ሥር ሰግዶ ክርስቲያን እንዲያደርገው ለመነው፡፡ መነኩሴውም ወስዶ ለኤጲስቆጶሱ ሰጠውና አስተምሮ አጠመቀው፡፡ መመንኮስም አንደሚፈልግ ቢነግረው "ሀብት ንብረት እያለህ መነኩሴ መሆን አይገባህም" አሉት፡፡ ከዚህ በኀላ ኤዺፋንዮስ እኅቱን አምጥቶ አስጠመቃትና ገንዘቡን ሁሉ ሸጦ ለድኆችና ጦም አዳሪዎች መጸወተው፡፡ በተረፈው ደግሞ ቅዱሳት መጻሕፍትን ገዛ፡፡ ከዚህም በኀላ መነኮሰና ለእርሱም ለእኅቱም ለጥምቀት ምክንያት ወደሆነው ስሙ ሉክያኖስ ወደተባለው መነኮስ ገዳም ገባ፡፡ በዚህም ጊዜ ዕድሜው 16 ብቻ ነበር፡፡
ከዚህም በኀላ ሽማግሌውን አባ ኢላርዮስን አገኘውና ሕግጋትን ሁሉ አስተማረው፡፡ ከዚህም በኀላ መናንያኑ እስኪያደንቁት ድረስ በፍጹም ትጋትና ቅድስና ተጋደለ፡፡ ብዙ አስገራሚ ተአምራትን አደረገ፡፡ ድውያንን ፈወሰ፣ በጸሎቱ ሙታንን አስነሣ፣ ከደረቅ መሬት ላይ ውኃን አፈለቀ፡፡ ያለጊዜውም ዝናም አዘነመ፡፡ ብዙ አይሁዶችንም ተከራክሮና በተአምሩ እያሳመነ አጠመቃቸው፡፡
ከዚህም በኀላ መምህሩ ኢላርዮስ በነገረው ትንቢት መሠረት በቆዽሮስ ደሴት ላይ ዻዻስ ሆኖ ተሾመ፡፡ ብሉይን ከሐዲስ የወሰነ እጅግ ምጡቅ ሊቅ ነውና ብዙ መጻሕፍትን ተረጎመ፡፡ በሺሕ የሚቆጠሩ እጅግ ጠቃሚ ድርሳናትን ደረሰ፡፡ በአፍም በመጽሐፍም ብሎ መናፍቃንንና አይሁድን ምላሽ በማሳጣቱ ቤተ ክርስቲያን "ጠበቃየ" ትለዋለች፡፡ ከደረሳቸው መጻሕፍት መካከል "ሃይማኖተ አበው ዘኤዺፋንዮስ፣ መጽሐፈ ቅዳሴውና አክሲማሮስ (ስነ ፍጥረት የሚተነትን) በዋነኛነት ይጠቀሳሉ፡፡ በተለይም አክሲማሮስ በተሰኘው ድርሰቱ ስነ ፍጥረትን እንዴት አድርጎ እጅግ ጥልቅ በሆነ መንገድ እንዳብራራው በቃላት ለመግለጽም አስቸጋሪ ነው፡፡ እጅግ በጣም የሚደንቅ ነው በእውነት፡፡ እግዚአብሔር ለቅዱሳኑ የሚገልጥላቸውን ሰማያዊ ዕውቀት ከማድነቅ ውጭ ልላ ምን ማለት እንችላለን!!!
ሊቁ ቅዱስ ኤዺፋንዮስ በመልካም እረኝነትና በሚደነቅ ቅድስና ሲያገለግል ኖሮ በ406 ዓ/ም ዐርፏል፡፡ የዕረፍቱን ሁኔታ በተመለከተ ከዮሐንስ አፈወርቅ ጋር የተገናኘ ታሪክ አለው፡፡
በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዘመን የነበረችው ጨካኟና አረመኔዋ ንግሥት አውዶክሲያ የድሃ ንብረት እየቀማች ተወስድ ስለነበር ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም ዘወትር ይመክራትና ይገሥጻት ነበር፡፡ አንድ ቀን አንዱ ድሃ ሄዶ ለዮሐንስ አፈወርቅ ነግሮት ሄዶ ‹‹የድሃውን ንብረት መልሺለት›› ቢላት እምቢ ስትለው ከቤተ ክርስቲያን እንዳትገባና ከክርስቲያኖችም ህብረት እንዳትቀላቀል አወገዛት፡፡ ‹‹ከግዝትህ ፍታኝ›› ብትለውም ‹‹የድሃውን ገንዘብ ካልመለሽ አልፈታሽም›› ስላላት ‹‹በከንቱ አወገዘኝ አባት ያስተምራል እንጂ እንዲህ አያደርግም›› እያለች ታስወራበት ጀመር፡፡ ለቅዱስ ኤጲፋንዮስም ‹‹ዮሐንስ ያለ አግባብ አውግዞኛልና መጥተህ አስፈታኝ አለዚያ ሃይማኖቴን እቀይራለሁ፣ ቤተ ክርስቲያንንም አቃጥላለሁ›› ብላ ላከችበት፡፡ ቅዱስ ኤጲፋንዮስም ሄዶ ዮሐንስ አፈወርቅን ‹‹ሰይጣን በልቧ አድሮባታል ያሰበችውንም ያስፈጽማታልና ለአገልግሎታችንም እንቅፋት እንዳትሆን ፍታት›› ቢለው ቅዱስ ዮሐንስም እምቢ አለው፡፡ እርሷም በየከተማው እየዞረች ‹‹ተመልከቱ ዮሐንስ ኤጲፋንዮስንም አወገዘው›› እያለች በውሸት ታስወራ ጀመር፡፡ ኤጲፋንዮስም እንዲህ ማለቷን አልሰማም ነበርና ከዮሐንስ ጋር በኋላ ተሰነባብተው ሊለያዩ ሲሉ ዮሐንስ ‹‹ለምን በነገሬ ገባህብኝ›› አለው፡፡ ኤጲፋንዮስም ‹‹አልገባሁም›› ቢለው በንግግር ሳይግባቡ ቀርተው ተጣሉ፡፡ በዚህም ጊዜ ሁለቱም የሚሞቱበት ጊዜና የሚሞቱበት በምን ዓይነት ሁኔታ እንደሆነ ተገልጦላቸው አንዳቸው ለአንዳቸው ትንቢት ተነጋግረዋል፡፡ ዮሐንስ ኤጲፋንዮስን ‹‹ሄደህ ከቤትህ አትገባም ከመንገድ ላይ አንበሳ ሰብሮ ይገድልሃል›› አለው፡፡ ኤጲፋንዮስም ለዮሐንስ ‹‹የእኔን ትላለህ አንተም እንጂ ደግሞ ተግዘህ በከሃዲዮች ተወግዘህ በአንጾኪያ ደሴት ታስረህ ተሠቃይተህ ትሞታለህ›› አለው፡፡ በተነጋገሩትም ትንቢት መሠረት ኤጲፋንዮስ ወደ በዓቱ ሲሄድ አንበሳ ገደለውና የአንበሳ ሆድ መቃብሩ ሆነለት፡፡ ስንክሳሩ ግን በመርከብ ሲሄድ እንዳረፈ ይገልፃል፡፡ ዮሐንስም በግዞት ታስሮ ብዙ ከተሠቃየ በኋላ ግንቦት 12 ቀን ዐረፈ፡፡ ጨካኟና አረመኔዋ ንግሥት አውዶክሲያም ‹‹ዮሐንስ ኤጲፋንዮስን አውግዞት ወደ ሀገሩ አባሮት በመንገድ ላይ እንዲሞት አደረገው›› እያለች በሀሰት አስወርታ የቤተ ክርስቲያን ጠላቶች የሆኑትን ሰዎች ሰብስባ ዮሐንስን እንዲያወግዙት ካደረገች በኋላ በግዞት ታስሮ እንዲኖርና ተሠቃይቶ እንዲሞት አድርጋዋለች፡፡
የቅዱስ ኤዺፋንዮስ ምልጃና በረከቱ በምልጃው በምንታመን በሁላችን ላይ ይደርብን! አሜን!!!
(የግንቦት ወር ስንክሳር፣ የቅዱሳንታሪክ-37-39፣ መዝገበ ታሪክ፣ የዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ጽሑፍ)