Tuesday, August 4, 2020

የአየር አጋንንት እና የብኩንነት ሕይወት

በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም
አጋንንት በሕይወታችን የሚያደርስብንን ችግር እስክናውቅ እንቸገራለን፣ ውጊያው እስኪገባን ግራ እንጋባለን፣ እውነቱ እስኪገለጥልን እውነቱ ሐሰት ይመስለናል፡፡
ሼር በማድረግ ለወዳጆ አዳርሱ!
ተወዳጆች ሆይ በክፍል ሃያ ዘጠኝ የአየር አጋንት እና የቤተሰብ ዛር እራሳችንን እንድናጠፋ እንደሚያደርገን አይተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ አጋንንት እንዴት በሕይወታችን ብኩን እንደሚያደርገን እናያለን፡፡ የቅዱሳን አምላክ ምስጢሩን ይግለጽልን፡፡ ወዳጆቼ በሰፊው እንዳየነው የአየር አጋንንት በተንኮል የተካነ ስለሆነ በሕይወታችን ብኩን እንድንሆን ያደርገናል፡፡  አጋንንት ቀድሞ በተሰጠው ጸጋ ስላልተጠቀመ እኛም በሕይወታችን እግዚአብሔር በሰጠን ጸጋ መክሊት እንዳንጠቀም ያደርገናል ያባክነናል፡፡ ሕይወታችን ብኩን፣ ትዳራችን ብኩን፣ ገንዘባችን ብኩን፣ የጨበጥነው እንደ ጉም እየተነነ፣ የያዝነው እየመነመነ ባዶ ያደርገናል፡፡ የአየር አጋንንት ከሰላቢ መንፈስ ጋር በማበር የምናገኘውን፣ የያዝነውን ይስልብብናል፡፡
ወዳጆቼ ስለ ብኩንነት ካነሳን አጋንንት በተለያየ እና በማናውቀው መንገድ ብኩን ያደርገናል፡፡ አንዳንዶቻችንን ለዘመናት በመጠንቀቅ እና በመጠበቅ ይዘን የቆየነውን ለተክሊል ክብር ያሰብነውን ድንግልና በማባከን በዝሙት ለክፎን የማንወጣበት ሕይወት ውስጥ ከቶ ያባክነናል፡፡ ሌሎቻችንን ገዳማት፣ አብያተ ክርስትያናት በመሄድ፣ በመጸለይ፣ በመመጽወት ያገኘነውን ጸጋ በዝሙት ጥሎን ጸጋችንን አስጥሎን የመንፈሳዊ ብኩን ያደርገናል፡፡ የበረቱትን ቅዱስ ቁርባን በመቀበል ያገኙትን መለኮታዊ ጸጋ በሐሜት፣ በምቀኝነት ጸጋቸውን አስጥሎ የቆራቢ ወረኛ አድርጎ ብኩን ያደርጋቸዋል፡፡ ወጥተው ወርደው፣ ሌት ተቀን እንቅል አጥተው ሠርተው ያገኙትን ገንዘብ በመጠጥ፣ በአልባሌ ውሎ፣ በመልካም ጓደኝነት አስመስሎ ገንዘባቸውንም ሕይወታቸውንም ብኩን ያደርጋል፡፡ ብቻ የአጋንንትን ተንኮሉን፣ ውጊያውን ካላወቅን በሥጋም በነፍስም ብኩን እንሆናለን፡፡ 
ወዳጆቼ አንዳንዴ በኪሳችን፣ በቦርሳችን ያያዝነው ገንዘብ የረባ ነገር ሳንገዛበት፣ ምኑንም ሳናውቅ ገንዘቡ የለም፡፡ አንዳንድ ሞኞች ‹‹አሁን አጋንንት ገንዘብ የሚሰልበው እንደ ሰው አይጠቀምበት፣ምን ይሠራለታል›› እያሉ እየተሰለቡ ይሟገታሉ፡፡ ወዳጄ አጋንንት ኑሮህን ለማቃወስ፣ በገንዘብህ ያሰብክበት ቦታ እንዳትደርስ ገንዘብህን ይሰልበዋል፡፡ ያኔ በማታውቀው ስልት ገንዘብህ ከእጅህ ሲወጣ፣ የመደናገጥ ጣጣ ይመጣል፡፡ አሥራት ያልወጣበት ገንዘብ፣ ጸሎት የሌለበት ሕይወት፣ የእግዚብሔር ረድኤት ስለማይኖረው የአጋንንት መጫወቻ ነው የሚሆነው፡፡
በተለይ አንዳች ጥሩ ነገር ካለን፣ ባለን ለመለወጥ ስንጥር፣ አጋንንት የማጨናገፊያ ድንበር እየሠራ የሙሉ ጎዶሎ ያደርገናል፡፡ ያለንን ይነጥቀናል፣ ያገኘነውን ያባክንብናል በዚህም ሕይወት ለእኛ የቀን ጨለማ ይሆናል፡፡ ግን አሁንም በመባከን ሕይወት ውስጥ ካለን ወደ እግዚአብሔር በንስሐ ተመልሰን፣ በጸሎት የምንማልል ከሆነ እግዚአብሔር በአጋንንት የተንኮል ሴራ የባከነ ሕይወታችንን በመቀየር አዲስ የሕይወት ምዕራፍን ይከፍትልናል፡፡
ብዙዎቻችን በአንድም በሌላም ብኩን ሆነናል፡፡ የእውቀት ብኩን፣ የማስተዋል ብኩን፣ የጊዜ ብኩን፣ የቸርነት ብኩን፣ የአዛኝነት ብኩን፣ የዕድሜ ብኩን፣ የበረከት ብኩን፣ የፍቅር ብኩን፣ የስኬት ብኩን፣ የትዕግሥት ብኩን፣ የሥራ ብኩን፣ ወዘተ ሆነናል፡፡ አጋንንት በተለያየ የፈተና ስልት ሕይወታችንን ሲያባክን ከመንቃት እና ወደ እግዚአብሔር ከመጠጋት ይልቅ ሥጋዊ አስተሳሰብ ተጭኖን በራሳችን ላይ ያለ ቀስቃሽ ተኝተናል፡፡
ጌታችን ዛሬ የምንኖረውን የብኩንነት ሕይወት በሉቃስ ወንጌል ላይ በምሳሌ አስተምሮናል፡፡ ከወላጅ አባቱ ‹‹ገንዘቤን አካፍለኝ›› ብሎ የተለየው ወጣት ገንዘቡን ይዞ ወደማያውቀው ሀገር ተሰዶ በዚያም ገንዘቡን በትኖ ኖረ፡፡ ገንዘቡ ሲያልቅ የሚበላው ቢያጣ ከአንዱ ጋር ተዳበለና የእርያ ጠባቂ ሆነ፡፡ ከረሃቡ ጽናት የተነሳ የእሪያዎችን አሰር ለመብላት ተመኘ፡፡ ግን እሪያዎች የሚበሉትን አሰር የሚሰጠው ጠፋ፡፡ በመጨረሻም ወደ ልቡ ተመልሶ፣ በስሕተቱ አልቅሶ ወደ አባቱ ቤት በክብር ተመልሷል፡፡ /ሉቃ 15÷11-32/
እኛም ከእግዚብሔር ጋር ስንለይ ነው ከአጋንንት ጋር የምንዳበለው፡፡ ከእግዚአብሔር ስንለይ፣ የአጋንንት ሲሳይ እንሆናለን፡፡ አጋንንቱም እንደ ጠፋው ልጅ የእኛንም ውድ ሕይወት እያባከነ፣ ጸጋችንን በኃጢአት እያስበተነ ብኩን ያደርገናል፡፡ የጠፋው ልጅ ወደ ልቡ ተመልሶ ወደ አባቱ ቤት በመምጣቱ ከቀድሞው የተሻለ ሽልማት እና ሕይወት አግኝቷል፡፡
እኛም ከመባከን ሕይወት ወጥተን፣ ወደ አባታችን ወደ እግዚአብሔር ከተመለስን አዲስ የበረከት ሕይወት ይኖረናል፡፡ የጠፋው ልጅ የአባቱን ቤት ማዕድ ንቆ፣ የእሪያን አሰር ለመብላት ናፍቆ ነበር፡፡ ወደ አባቱ ቤት ሲመለስ ግን ፍሪዳ አርዶለት ደግሶ ነው የተቀበለው፡፡ እኛም የእግዚአብሔርን የበረከት ሕይወት ረግጠን፣ ንቀን የአጋንንትን የመከራ እንጀራ ነው የበላነው፡፡ ግን ወደ እግዚአብሔር ከተመለስን ከመለኮት ማዕድ ከቅዱስ ቁርባን ተቋድሰን፣ በጸጋው ተሸልመን በክብር እንኖራለን፡፡
ስለዚህ አጋንንት የነጠቀንን ሊመልስልን የሚችለው እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ አጋንንት የወሰደብንን ሊሰጠን የሚችለው እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ከእግዚአብሔር መለየት ልዩ ብኩንነት ነው፡፡ እኛ ብኩን የሆነው አጋንንት ሲጠናወተን ሳይሆን እግዚአብሔር ሲለየን ነው፡፡ ከእግዚብሔር መለየት ብኩንነት ብቻ ሳይሆን የቁም ሞት ነው፡፡ እኛ በቁማችን ለአጋንንቱ ሞተንለት ነው እርሱ የሚገድለን፡፡ ስለዚህ ከሕይወት ብኩንነት ለመውጣት ወደ እግዚአብሔር መጠጋት ያስፈልጋል፡፡
‹‹ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቶአል›› ት.ሆሴ 4÷6
‹‹ከትውልዱ ማን አስተዋለ?›› ት.ኢሳ 53÷8
ክፍል ሠላሳ አንድ
የአየር አጋንንት የተረጋጋ መንፈስ እንዳይኖረን ያደርጋል
ይቀጥላል ……
ሰኔ 8-10-12 ዓ.ም
አዲስ አበባ

Tuesday, July 21, 2020

የአየር አጋንንት የተረጋጋ መንፈስ እንዳይኖረን ያደርጋል

በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም
አጋንንት በሕይወታችን የሚያደርስብንን ችግር እስክናውቅ እንቸገራለን፣ ውጊያው እስኪገባን ግራ እንጋባለን፣ እውነቱ እስኪገለጥልን እውነቱ ሐሰት ይመስለናል፡፡
ሼር በማድረግ ለወዳጆ አዳርሱ!
ተወዳጆች ሆይ በክፍል ሠላሳ የአየር አጋንንት እና የብኩንነት ሕይወትን አይተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ የአየር አጋንንት እንዴት የተረጋጋ መንፈስ እንዳይኖረን እንደሚያደርገን እናያለን፡፡ ወዳጆቼ በዚህ ዘመን የተረጋጋ ሰው የታደለ ነው፡፡ የአየር አጋንነት አንዱ የፈተናው ስልት መረጋጋትን ማሳጣት ነው፡፡ የአየር አጋንንት ሲፈትነን አንድ ቦታ አርፈን አንቀመጥም፣ እንቅበዘበዛለን፣ እንኳን አካላችን ምላሳችንም አይረጋጋም፣ ሰው ሲናገረን ስደበው ተናገረው እያለ ይገፋፋናል፡፡ በተለይ ቤተ ክርስቲያን ስንገባ ውስጣችን ያለው ዓይነ ጥላ ከአየር አጋንንት ጋር በማበር ተረጋግተን እንዳናስቀድስ፣ እንዳንጸልይ፣ እንዳንማር የማስጨነቅ ሥራ በመሥራት ከቤተ ክርስቲያን በሆነ ምክንያት በማሳመን ‹‹ውጣ ውጣ›› ይለናል፡፡ የውሳኔ ሰው መሆን አንችልም፡፡ አንድ ነገር ብንወስንም ልክ ያልሆነ ውሳኔ ነው የምንወስነው፡፡ በስሕተቱ እንጸጸታለን፡፡ በዚህ የተነሳ አጋንንቱ በራስ የመተማመናችንን መንፈስ ያሳጣናል፡፡
የአየር አጋንንት ያለ መረጋጋት ስሜት ሲያሳድርብን ፊታችን የተረበሸ ይመስላል፣ ግራ ይገባናል፣ የደስተኝነት ስሜት አይነበብብንም፣ ያኮረፈ የተቆጣ ፊት እንዲኖር ያደርገናል፡፡ ብዙዎችን የአየር አጋንንት እየፈተናቸው በዓመት አንዴ የስቅለት ስግደት ቀን ጨንቋቸው፣ ሥርዓቱ አላልቅ ብሏቸው ከቤተ ክርስቲያን የሚወጡ አሉ፡፡ ቅዳሴ ለማቋረጥ የሚሞክሩና የሚያቋርጡ አሉ፡፡
ወዳጂቼ የአየር አጋንንተት በጸሎት ጊዜ ሲፈትነን የምናየው ምልክት አሉ፡፡ አንደኛ ጸሎቱ አልገፋ አላልቅ ይለናል፡፡ ሁለተኛ ጸሎቱ ስልችት ይለናል፡፡ ሦስተኛ ልባችንን ሕሊናችንነ ሰውሮ ከተጣላነው ሰው ጋር አንባ ጓሮ አስገጥሞን የጸሎት መጽሐፋችን ገጽ ያስቆጥረናል፡፡ አራተኛ ጸሎት ይዘን መረጋጋት ስንችል እንቁነጠነጣለን፡፡ አምስተኛ ወገባችን፣ ጉልበታችን እግራችን ይብረከረካል መቆም ያቅተናል፡፡ ስድስተኛ ጸሎት እያደረግን ኩንታል እንደተሸከመ ሰው ሰውነታችን ሁለ መናችን ይከብደናል፡፡ ሰባተኛ ጸሎቱ ባለበት ሐሳባችን ልባችን አይኖርም፡፡ ስምንተኛ በጸሎት ሰዓት እግዚአብሔር ፊት ምስጋናችንን አስረስቶ ጸሎታችንን ጭቅጭቅ ያደርግብናል፡፡ ለምሳሌ ‹‹እግዚአብሔር ምን አደረገልህ? ያንቺ ጸሎት ምን አመጣ? እነ እከሌ ጠንቋይ ቤት እየሄዱ ሕይወታቸው ተለወጠ አንቺ ግን እግዚአብሔር ይዘሽ ቤተ ክርስትያን ተመላልሰሽ ይኸው ባዶሽን አለሽ፣ ሥራ የለሽ፣ ትዳር የለሽ፣ ወይ ገዳም አልገባሽ ወይ ሞተሸ አልተገላገልሽ ወዘተ›› እያለ መጸለያችን ሳይታወቀን ጸሎቱን እንጨርሳለን፡፡ ስምንተኛ ሰውነታችን ላይ በተለይ ጀርባችን ላይ የሚርመሰመስ የሚሄድ ስሜት ይሰማናል። ዘጠነኛ ጸልት ይዘን ከፍተኛ የማናውቀው ፍርሃት ይሰማናል። አስረኛ ከፊት ለፊታችን ከጀርባችን ከጉናችን ውልብ ስልብ የሚል የማናውቀው ምስል ይታየናል: ሰው አብሮን የቆመ ሸከክ ክብድ ይለናል።
ለመቀበል የዘገየነው፣ የረሳነው ያበደርነው ገንዘብ ሁሌም ትዝ የሚለን ጸሎት ላይ ነው፡፡ ቀን ስልክ እደውልለታለሁ ያልነው ሰው ትዝ የሚለን ጸሎት ስንጀምር ነው፡፡ ብቻ የረሳነውን ነገር የምናስታውሰው፣ አደርገዋለሁ ብለን ጊዜ ያጣንበት ነገር የሚታወሰን ጸሎት ላይ ነው፡፡ የሚገርመው ቁጭ ብለን የማናስበው የሥራ እቅድ ጸሎት ላይ ሐሳቡ የሚመጣልን፡፡ ነጋዴ ከሆንን ትርፉ ወለል ብሎ የሚታየን፣ ኪሳራውም የሚታወቀን ጸሎት ላይ ነው፡፡ ወዳጆቼ ይህን ሁሉ ሐሳብ የአየር አጋንንት በጸሎት ጊዜ እያመጣ የሚጭንብን የተረጋጋ ጸሎት እና  መንፈስ እንዳይኖረን ለማድረግ ነው፡፡ አጅግ የሚገርመው የመንፈስ እርጋታ እና የነፍስ እፎይታ የምናገኝበት ቤተ ክርስትያን ሄደን የባሰ የምንጨነቅ፣ ስሜታችን ዝብርቅርቅ የሚልብን አለን፡፡ ይህ ሁሉ የእሱ ውጤት ነው፡፡
መረጋጋትን ያጣው የአየር አጋንንቱ እኛን ያለመረጋጋት ስሜት ውስጥ ይከተናል፡፡ እኛን እንዲህ ያድርገን እንጂ መነኮሳትን ከባዕታቸው ከገዳማቸው ሰላም በማሳጣት ያለመረጋጋት ስሜት ወስጥ እየከተታቸው እየረበሻቸው ክፉኛ ይፈትናቸዋል፡፡ እነሱም የአየር አጋንንቱን ያለመረጋጋት ፈተና መቋቋም ሲያቅታቸው በምክንያት ከገዳማቸው ይወጣሉ፡፡
የአየር አጋንንት ሰውን በማንከራተት የተጠመደ ነው፡፡ መነኮሳትን ንቀውና ጥለው የመጡትን ዓለም እንደ ገነት በማሳየት፣ ከገዳም ይልቅ የጽድቅ ሥራ በዓለም እንዳለ በማሳሰብ፣ ከገቡበት ገዳም በማስወጣት በዓለም እንዲንከራተቱ ያደርጋቸዋል፡፡ አጋንንቱ በፈተና ምክንያት ዓለም ውስጥ ከከተታቸው በኋላ ዓለማዊ ሕይወትን በማለማመድ፣ በቁሳዊ ነገር በመጥመድ በተንኮሉ መዳፍ ያስገባቸዋል፡፡ በገዳም ያለውን ፈተና ሳይቋቋሙ አጋንንቱ በሰፈረበት ዓለም ፈተናውን የሚቋቋሙት ምናልባት በእግዚአብሔር ፈቃድ በዓለም እንዲኖሩ የተፈቀደላቸው ብቻ ናቸው፡፡ የአየር አጋንንት ሰፍሮብን ብዙ ነገር ካለማመደን በኋላ ወደ ቀደመ ሕይወታችን ለመመለስ እጅጉን እንቸገራለን፡፡ እያንከራተተ ያኖረናል፡፡
አንድ መንፈሳዊ ሰው የተረጋጋ መንፈስ ከሌለው አንኳን ከሰው ከእግዚአብሔር ጋር አይስማማም፡፡ መረጋጋት የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ የመላበስ ምልክት ነው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወት ያለ መረጋጋት ካለ ለስሕተት እና ለኃጢአት እጅጉን የተጋለጥን ነን፡፡ ስለዚህ በሕይወታችን ያለመረጋጋት ክሥተት ከታየብን ቆም ብለን ራሳችንን መቃኘት፣ወደ ሰማይ አምላክ መመልከት ያስፈልገናል፡፡ የመረጋጋት መንፈስ ልግስና ከሰማይ አምላክ ነውና፡፡
‹‹ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቶአል›› ት.ሆሴ 4÷6
‹‹ከትውልዱ ማን አስተዋለ?›› ት.ኢሳ 53÷8
ክፍል ሠላሳ ሁለት
በአየር አጋንንት እና በሌሎች ሥራችንና ዕቅዳችን ይበላሻል
/ሩቅ አሳቢዎች ቅርብ አዳሪዎች፣አመድ አፋሾች/
ይቀጥላል …..
ሰኔ 8-10-12 ዓ.ም
አዲስ አበባ

Tuesday, July 7, 2020

ለእግዚአብሔር ያልንተንበረከከ፣ በአጋንንት የተማረከ ትውልድ

በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም
አጋንንት በሕይወታችን የሚያደርስብንን ችግር እስክናውቅ እንቸገራለን፣ ውጊያው እስኪገባን ግራ እንጋባለን፣ እውነቱ እስኪገለጥልን እውነቱ ሐሰት ይመስለናል፡፡
ሼር በማድረግ ለወዳጆ አዳርሱ!
ተወዳጆች ሆይ በክፍል ሠላሳ ሦስት የጠንካራ መንፈሳውያን ሰዎችን የአጋንንት ፈተና ተመልክተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ ከላይ የጠቀስኩትን እናያለን፡፡ የቅዱሳን አምላክ ምስጢሩን ይግለጽን፡፡ አሁን ያለነው ትውልድ በአጋንንት ስውር ደባ ስለተማረክን ለእግዚአብሔር ተገዝተን መንበርከክ አልቻልንም፡፡ የእኛ ትውልድ ከፍተኛ የማንነት ቀውስ ውስጥ እና የአጋንንት የተንኮል ውርስ ውስጥ ገብቷል፡፡ ከእግዚብሔር መንገድ ርቀን በራሳችን መንገድ ታንቀን ስለምንሄድ የአጋንንት ሰለባ እየሆንን ነው፡፡
በተለይ ወጣቱ የአጋንንትን የፈተና ስልት ስላላወቀ በሥጋ ፍላጎቱ እንደታነቀ ይኖራል፡፡ የእኛ ትውልድ አዋቂ ነኝ ይላል ግን ማወቁ ከፈተናው ለመላቀቁ ፍንጭ አልሰጠውም፡፡ ዛሬ መቶ መስገድ የዳገት መንገድ የሆነብን ለምንድን ነው? አንድ ሰዓት ቆመን ስናወራ የማይታክተን ለሃያ ደቂና ውዳሴ ማርያም መጸለይ ያቃተን ለምንድን ነው? ጽኑ እምነት አጥተን ሃይማኖትን በእምነት ሳይሆን በሥጋዊ እውቀት የምንመዝነው ለምንድን ነው? ጆሮአችን ቃለ እግዚአብሔር ሳይሆን ሐሜት ለመስማት ለምን ይዳክራል?
ጓደኛችን ለፍቶ ሠርቶ ከሚለወጥ አፈር ከደቼ በልቶ ቢፈጠፈጥ ደስ የሚለን ምቀኝነት ናላችንን ያዞረን ለምንድን ነው? እለት እለት ከአንደበታችን እውነት ሳይሆን ውሸት የሚወጣው፣ ከውሸት አልፈን ቅጥፈት የለመድነው ለምንድን ነው? ወዘተ …
ለእግዚአብሔር መንበርከክ ትተን ለአጋንንት ስንማለር መገለጫችን መንፈሳዊ በረከቶችን መጠራጠር፣ በእምነት መነጽር አለማየት፣ አለማመን፣ መንፈሳዊ ጸጋን በሥጋ እውቀት ማየት፣ ቸልተኛ፣ ግዴለሽነት፣ በሥጋም በነፍስም ተስፋ መቁረጥ፣ በዶግማና በቀኖና መናወጥ፣ በመንፈሳዊ ሕይወት አለማደግ አለመለወጥ ወዘተ ነው፡፡ ይህን ገዳፋ የምናተርፈው በቤሰተባችን የእምነት ደካማነት እና በአጋንንት ተጽዕኖ ነው፡፡ ወዳጆቼ መንፈሳዊ ጸጋ የራቀን የሥጋዊ ዝቅጠት የተጫነን ለእግዚአብሔር ከመንበርከክ ይልቅ እኛን እስከጠቀመን ድረስ ለአጋንንት ስንማረክ ትርፋችን ይህ ነው፡፡
ሱስና መጠጥ ያሠረው ወጣት ለአጋንንት መጫወቻና የአጋንንት ፍላጎት ማስፈጸሚያ ቢሆን አይገርምም፡፡ ይህ ትውልድ አይወቀስም አወቅን ዘመናዊ ሆንን ያሉ በእግዚአብሔር መባረክን ያልወደዱት ወላጆች የዘሩት ውጤት ነው፡፡ ቤተሰብ ልጆችን በሕፃንነታቸው በዕለተ ሰንበተ ቅዱስ ቁርባን ማቁረብ ትተው ወደ መጫወቻ ቦታ ይዘው በመሄዳቸው የእግዚአብሔርን ጸጋ ሳይሆን የዓለምን ዋጋ እንዲያዩ ነው ያደረጉት፡፡ በዕለተ እሑድ ማስቀደስ ሳይሆን መደነስ የለመደ ወጣት የአጋንንት ቁራኛ ቢሆን አይደንቅም፡፡
ትላንት በልጅነቱ እናት ‹‹ቅዳሴ ሂድ›› ስትለው ልጅ የዓይነ ጥላውና የአፍዝዝና የቤተሰብ ዛር ልጁ ላይ እያለቀሰ ‹‹አልሄድም›› ሲል አባት ‹‹ተይው ካልፈለገ አታስገድጅው፣ እንዲ ሆኖ ቢሄድም ምንም አይጠቅመውም›› በማለት ከቅድስናው ደጅ እያራቀ ሲከላከል የነበረው ቤተሰብ በሕፃኑ ላይ የዘራውን የቸልተኝነት፣ የእንቢተኝነት፣ የመብቱ ነው ጥያቄ ሲያድግ በልጁ መከራ ያጭደዋል፡፡
ትላንት ልጆችን የአጋንንት አረም ሲበቅልባቸው አረሙን ከመንቀል፣ መንፈሳዊ ሕይወታቸውን ከመከታተል ይልቅ ለሥጋዊ ደስታቸው እያደላን ሰማያዊ ደስታቸውን እናጨልማለን፡፡ ልጆቻችን በአጋንንት ምትሐታዊ ፍላጎት እየተነዱ በሕፃንነታቸው የአዋቂን ጸያፍ ሥራ ሲሠሩ ‹‹እሷ ፈጣን ናት፣ እሱ ብልጥ ነው፣ የሕፃን አዋቂ ናቸው›› እያልን በሃይማኖት ሳንገራቸው አሳድገን የሕፃንነት የኃጢአት ሕልማቸውን ከመሬት ብቅ እንዳሉ ያሳዩናል፡፡ ያኔ ቤተ እግዚአብሔር ሄደን ብንጮህ አጉልና የማይሰማ ጩኸት ነው፡፡ብቻ በልጅነታቸው ያሳየናቸውን የጥፋት መንገድ፣ አድገው መከራና ፈተና ሲያሳጭዱን እንኖራለን፡፡ እኛ ተባርከን ልጆቻችንን እንዳናስባርክ፣ እኛው ተሰላችተን አጋንንቱ መንገድ ዘግቶብን ለልጆቻችን የእርግማን መናፍስትን እናወርሳቸዋለን፡፡
በቅዳሴው በቁርባኑ፣በቃሉ ስላላስባረክናቸው አጋንንት እንደ ፈጣን ፈረስ እየሰገራቸው ወደ ጥፋት እና ወደ ኃጢአት ሜዳ ይጋልባቸዋል፡፡ ለልጆቻችን ንብረት እንጂ ሃይማኖታችንን ስለ ማውረስ ስላልተጨነቅን ልጆቻችን ንብረት አጥፊ፣ እግዚአብሔር ላይ አሿፊ ትውልድ ይሆናሉ፡፡ ሠርተን ያወረስናቸው እንጂ ተባርከን የሰጠናቸው መንፈሳዊ ስጦታ ስለሌለ አመንዝራና ሱሰኛ ይሆናሉ፡፡ ይህ የእኛ ድክመት ልጆቻችንን የአጋንንት መሥዋዕት እንዲሆኑ በሩን መክፈት ብቻ ሳይሆን የጥፋትንም መንገድ አሳይተናቸዋል፡፡ ዛሬ በየቤታችን የተሸከምናቸው የልጆቻችን ችግሮች መሠረቱ እኛው ነን፡፡ ስለዚህ ስንዴ ካልዘራንበት እርሻ አረማችንን አጭደን በቤታችን ከምረን መኖራችን ግድ ነው፡፡
በኖኅ ዘመን የነበረው አመንዝራ ትውልድ፣ በሎጥ ዘመን የነበረው ግብረ ሰዶማዊው ትውልድ ቤተሰባቸው አረም ሆነው የዘሩት የጥፋት እና የመቅሠፍት ትውልድ በእኛም ዘመን እያየነው ነው፡፡ ስለዚህ ለእግዚአብሔር ያልተንበረከከ ትውልድ፣ ለሰይጣን የጥፋት እንጨት ሆኖ ሲማገድ፣ በኃጢአት ሲነድ ማየት ግድ ብሎናል፡፡
ወላጆች እስኪ ልጆቻችሁ የሚያዩትን የሕፃናት ፊልሞች ተመለከቱ፡ ምዕራባውያን በሕፃናት ፊልም ሰይጣንን እያለማመዷቸው ነው፡፡ በሕፃናት ፊልም ላይ የሚታዩትን ገጸ ባህሪያት ብናያቸው ወጣ ያሉ፣ የሚያስፈሩ፣ የሉሲፈር ገጽታ ያላቸው ወዘተ ናቸው፡፡ የሚጫወቱት ጌሞች ለንቃተ ሕሊና የሚረዱ ሳይሆን አጋንንትን የሚያለማምዱ ናቸው። እነዚህን ምዕራባውያን የራሳቸውን ትውልድ በሚፈልጉት መንገድ አበላሽተዋቸው ሱሰኛ፣ ሺሻ የሚያጨስ፣ በወጣትነቱ የሚገድል የሚደበድብ እናት አባቱም የማያከብር እንዲሆም አድርገዋል፡፡ አሁን የእኛ ነው የቀራቸው እኛንም ልጆቻችንን በፊልማቸው በአሻንጉሊት ትዕይንታቸው እያደነዘዙን እያፈዘዙን ነው፡፡
እባካችሁ ጨቅላ ሕፃናቶቻችንን በልጅነታቸው የአምልኮ፣የጾም፣የጸሎት፣የስግደት ሥርዓት እያስተማርን አሳድገን ከአጋንንት ምርኮ እንታደጋቸው፡፡
‹‹ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቶአል›› ት.ሆሴ 4÷6
‹‹ከትውልዱ ማን አስተዋለ?›› ት.ኢሳ 53÷8
ክፍል ሠላሳ አምስት
በጸሎት የራቀን ዲያብስ፣ ወደ እኛ መመለስ
https://www.facebook.com/memehirhenok

Tuesday, September 19, 2017

ሙስሊሟዋ ድንቅ ተዓምር በሸንኮራ ዮሐንስ ተደረገላት

" ደስታና ተድላም ይሆንልሃል፥ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል። በጌታ ፊት ታላቅ ይሆናልና፥ የወይን ጠጅና የሚያሰክር መጠጥ አይጠጣም፤ ገናም በእናቱ ማኅፀን ሳለ መንፈስ ቅዱስ ይሞላበታል።ከእስራኤልም ልጆች ብዙዎችን ወደ ጌታ ወደ አምላካቸው ይመልሳል " ሉቃ.1፡14
ሸንኮራው ቅዱስ ዮሐንስ ድንቅ ተአምር
ሃይማኖቴ "ወልድ ፍጡር፣ ቤተክርስቲያን ድንጋይ ናት" ሎቱ ስበሐት ። ከሚሉ አሕዛብ ወገን ነበርኩ የምትለዋ እህታችን መኖሪያዋ በመዲናችን አዲስ አበባ ነው ። ክርስቲያን የሚባል አልወድም፣ ፍጹም ጥላቻንም የተሞላው ነበርኩ። አምላኬን ያስደሰትኩ መስሎኝ አንድ አብሮ አደግ ክርስቲያን ጓደኛ አለችኝ። ብሰድባት ብተፋባትም ጉዳይዋ አይደለም ኣትቀየመኝም። ቅዱስ ዮሐንስን በጣም ትወደዋለች።
እኔ በስኳር በሽታ ምክንያት አንድ እግሬ በጋንግሪን (የተወሰነ አካል መሞት) እንዲቆረጥ ሐኪም ወሰነ። ያች ጓደኛዬ ግን የዮሐንስ ጸበልን ቤቴ አመጥታ ሰጠችኝ። ተቀብያት ከፊቷ ይህ እኮ "ውሐ" ነው ተረት አታውሪ ብዬ ስደፋው የጸበል ዕቃውን የያዘ እጄ ሰለለ ሽባ ሆነ፤ ደነገጥኩኝ። የጥፋተኝነት ስሜት ተሰማኝ። አይዞሽ ምልክት ነው መጥምቁ ያማልድሻል አለችኝ። "ኦፕራሲዮኑን ተይው አንቺ ካልዳንሽ እኔ ሃይማኖቴን እቀይራለው" ስትል ቤተሰቤ በሃሳብ ለሁለት ተከፈለ። እግሬ በአስቸኳይ ይቆረጥ ተብሏል። እግሬም ቁስሉ ሽታ አመጣ። በዚያ ላይ በሃይማኖቴ፣ ቤተሰቤ ሁሉ በአይነ ርግብ ተሸፍኖ የሚሄድ ነው። መገላለጥ የለም፤ "እዛ ብትሔጂ እንረግምሻለን" አሉኝ። በመጨረሻ ውሳኔ የኔ ሆነና ከሶስት ቤተሰብና፣ ከዚህችው ወዳጄ ጋራ ሸንኮራ ሄድን። ወደ ጸበሉ መውረድ አልቻልኩም አምጥተው አጠመቁኝ። ቁስሉ እንደቅርፊት ወደቀ። እንደውም ጸበሉን የደፋሁበት እጄ ዳነ። የምን መቆረጥ የምን ጋንግሪን።
የሕመሜም ምክንያት የነበረው 23 አመት ያሰቃየኝ ስኳሩም ዳነ። አብራኝ የሄደች አንድዋም ቤተሰቤ በፍንጢጣ ኪንታሮት ትሰቃይ ነበር የባህል መድሐኒት ወስዳ ጽኑ ህመም ላይ ነበረች እርስምዋ ዳነች።በሰማዕትነት ለአምላኩ ምስክር የሆነው መጥምቁ ዮሐንስ ከአምላክ አማልደህ ካዳንከኝ ጥላ በሬ ላምጣ አልልም አንተ ምስክር ለሆንክለት “በክርስቲያን አምላክ በኢየሱስ ክርስቶስ አምናለው” ብዬ ነበር።
ይህም ድኜ ለስዕለቴ በቃው ከስምንት ቤተሰቤ ጋር ሃብተ ወልድና ስመ ክርስትና ተቀበልኩኝ። ትለናለች።
እህተ ዮሐንስ፤ፍቅርተ ዮሐንስ፤ወለተ ብርሐን፤ተጠምቀ መድህን፤ክፍለ ዮሐንስ፤ገብረ ዮሐንስ፤ወልደ ዮሐንስ፤አርከ ዮሐንስ ተብለን የቀራኒዮ ቤዛ ወደ አብ ወልደ ማርያም ኢየሱስ ክርስቶስ ነቢይ ሳይሆን አምላክ እንደሆነ አምነን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠምቀናል።
ቅዱስ ዮሐንስም ተአምር ግን ድሮ ነው የጀመረው ጎረቤቴ ዝክሩን ስታደርግ አትጥሪኝ እላት ነበር። ዝክሩንም አልበላም ጣኦት አምላኪ አድርጌ ነው የምቆጥራት። የክርስቲያኖች አምላክም ብዙ ነበር የሚመስለኝ። አወይ አለማወቅ በድብቅ ግን ዝክሩን በልጆች ስም አስመጥቼ እበላ ነበር።ይጣፍጠኛል ለካ በስተመጨረሻው የሕይወት እንጀራን ስጋ ወደሙ ሊያበላኝ ኖሯል እንዲያ የጣፈጠኝ፤ ትላለች እህታችን በጥምቀቱ ስነ ስርአት በዓይኔ በአካል ተገኝቼ በከተማችን በሚገኝ አንድ አጥቢያ ተከታትያለው ይለናል አንተነህ ሐይሌ።
እኛ የእምነት አቃቂር ስናወጣ ጥቅስ ስናገላብጥ የዛሬ 2000 አመት አንገቱ የተቆረጠው መጥምቁ ዮሐንስ ስንት የጠፋውን መንጋ ጥቅስ ሳይጠቅስ ቃላት ሳያዥጎደጉድ በፍቅሩ አስሮ በምልጃው ጠብቆ ለጌታው ምርኮን አስገባ። ይህን ያደረገ የመጥምቁ አምላክ ክብር ይግባው ዮሐንስ ነቢይ ሰማዕት እኛንም ያማልደን አሜን።
ከአንተነህ ኃይሌ ገጽ ተገኝቶ ጥቂት እርማት የተደረገበት የእውነት ምስክርነት። ወደፊት ግለሰቦቹ አነጋግረን የበለጠ መረጃ ለማድረስ እሞክራለሁ። “ እላችኋለሁ፥ እንዲሁ ንስሐ ከማያስፈልጋቸው ከዘጠና ዘጠኝ ጻድቃን ይልቅ ንስሐ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ በሰማይ ደስታ ይሆናል።”ሉቃ 15:7