Showing posts with label አቡነ ዳንኤል ዘገዳመ አስቄጥስ. Show all posts
Showing posts with label አቡነ ዳንኤል ዘገዳመ አስቄጥስ. Show all posts

Monday, August 3, 2015

አቡነ ዳንኤል ዘገዳመ አስቄጥስ

ግንቦት 8-ዕረፍቱ ለአቡነ ዳንኤል ዘገዳመ አስቄጥስ
አቦ ገድሉ ከማር የሚጣፍጠውን የዚህን ታላቅ ጻድቅ ታሪክ ያንብቡና ነፍስዎትን እርክት ያድርጉ!
አቡነ ዳንኤል በመቃርስ ገዳም በደብረ ሲሐት ይኖር የነበረ ሲሆን እርሱም እጅግ ገድለኛ አባት ነው፡፡ 40 ዓመት በአስቄጥስ ገዳም ሲኖር ከቅጠል በቀር ተመግቦ አያውቅም፡፡ በአስቄጥስ ገዳም ዜናው ሁሉ በዓለም በተሰማ ጊዜ የነገሥታት ልጆችም ወደ እርሱ እየመጡ እየተባረኩ ይሄዱ ነበር፣ ግማሾቹም በዚያው ይመነኩሱ ነበር፡፡ ይህም አባ ዳንኤል ስሟን እንጣልዮስ አስብላ የነበረች ንግሥት የነበረችውን ቅድስት በጥሪቃን የገነዛት ነው፡፡ እርሷም ወንድ የነበረች ሲሆን ይህም የታወቀው ከሞተች በኋላ ነው፡፡ አውሎጊስ የሚባለውን የወፍጮ ድንጋይ እየወቀረ በመሸጥ ለድኆች የሚመጸውትን ጻድቅ ሰው ዋስ እሆነዋለሁ በማለት ከእግዚአብሔር ዘንድ ለምኖ ሥልጣንና ብዙ ወርቅ እንዲያገኝ ያደረገው ይህ አባ ዳንኤል ነው፡፡ በኋላም አውሎጊስ ሀብቱና ንብረቱ ከእግዚአብሔር የሚያርቀው ቢሆን አባ ዳንኤል በጸሎቱ መልሶ ሀብቱን እንዲያጣ አድርጎታል፡፡ አውሎጊስ የሚባል ጻድቅ የወፍጮ ድንጋይ እየወቀረ (እየጠረበ) በመሸት የሚየገኘውን ለድኆችና ጦም አዳሪዎች ይመጸውት ነበር፡፡ አባ ዳንኤልም የአውሎጊስን መልካም ሥራ ተመልክቶ እጅግ ደስ ብሎት ለአውሎጊስ የሀብቱን መጠን እንዲጨምርለትና ይበልጥ እንዲመጸውት በማሰብ ወደ እግዚአብሔር በጸሎት አሳሰበ፡፡ ለአውሎጊስም ዋስ ሆነውና ሀብቱ ተጨመረለት፡፡ አንድ ቀን የሚወቅረውን ድንጋይ ሲፈቅል በሸክላ ዕቃ የተደፈነ ሙሉ ወርቅ አገኘ፡፡ ወደ ቁስጥንጥንያም ከተማ ሄዶ ለንጉሡ አስረከበና የንጉሡ የሠራዊት አለቃ ሆኖ ተሾመ፡፡ ከተሾመም በኋላ የቀድሞውን የጽድቅ ሥራውን ተወ፡፡ አባ ዳንኤልም ስለ እርሱ ሰምቶ ሊያየው ቢሄድ በፈረስ ላይ ተቀምጦ በሠራዊት ታጅቦ በትዕቢት ተመልቶ አገኘው፡፡ ክፉ የትዕቢት መንፈስ አድሮበት ነበር፡፡ አባ ዳንኤልም አውሎጊስ ሀብት እንዲያገኝ በመለመኑ አዘነ፡፡ በሌሊትም የአውሎጊስ ነፍስ በእርሱ ምክንያት እንደጠፋች ራሱ አባ ዳንኤልም ሲሰቀልና እመቤታችን ስለ እርሱ ስትማልድ ራእይ አየ፡፡ ከእንቅልፉም በቃ ጊዜ የአውሎጊስ ሀብት እንዲጠፋና ወደ ቀደመ ግብሩ እንዲመለስ በጾም ጸሎት ሱባኤ ያዘ፡፡ መልአክም ተገልጦለት በእግዚአብሐር የፍርድ ሂደት ውስጥ ጣልቃ በመግባቱ ከገሠጸው በኋላ አውሎጊስም ምሕረት እንደሚያገኝ ነገረው፡፡ አውሎጊስን የሾሸመው ንጉሥም ሞተና ሌላ ንጉሥ ነገሠ፡፡ አውለጊስንም ንብረቱን ሁሉ ቀምቶ ነፍሱንም ለመግደል አሳደደው፡፡

አውሎጊስም ነፍሱን ለማዳን ሽሽቶ ወደ ሀገሩ በመግባት የቀድሞ ሥራውን መሥራት ጀመረ፡፡ ነዳያንንም እንደዱሮም መመገብ ጀመረ፡፡ አባ ዳንኤል ከታለቁ ጻድቅ ንጉሥ ከቅዱስ አኖሬዎስ ጋር የተገናኘ ታሪክ አለው፡፡ ይኸውም አባ ዳንኤል 40 ዓመት ሙሉ በአስቄጥስ ገዳም ሲኖር ከቅጠል በቀር ተመግቦ አያውቅም ነበርና ከጽድቁና ከብቃቱ የተነሣ ከብዙ ዘመን በኋላ የመመካት ክፉ ሀሳብ መጣበት፡፡ ‹‹በገዳም ውስጥ እንደእኔ ትርሕምትን ገንዘብ ያደረገ ይኖር ይሆን?›› ብሎም አሰበ፡፡ ሰውን ወዳድ የሆነ ጌታችንም ይህን ክፉ ሀሳቡን ሊያርቅለት ሽቶ ብርሃናዊ መልአኩን ላከለት፡፡ መልአኩም አባ ዳንኤልን ስለ ትምክህቱ ቢቆጣውም አባ ዳንኤል መልአኩን መልሶ ‹‹ጌታዬ ከእኔ የሚሻል ካለ ንገረኝ፣ ወደ እርሱ ሄጄ አየው ዘንድ እወዳለሁ፣ በመመካቴም ወደ ፈጣሪዬ በልመና እመለስ ዘንድ›› አለው፡፡ መልአኩም ‹‹እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው የሮሜና የቁስጥንጥንያ ንጉሥ አኖሬዎስ በመንግሥተ ሰማያት ባልንጀራህ ነው›› አለው፡፡ ‹‹ንጉሥ አኖሬዎስም የመነኮሳትን ሥራዎች ሁሉ ስለሚሠራ ከልብሰ መንግሥቱ ሥር በሥጋው ላይ ማቅ ይለብስ ነበር›› ተብሎ በስንክሳሩ ላይ የተጻፈለት ጻድቅ ንጉሥ ሲሆን ሰማያውያን የሆኑ ቅዱሳን መላእክትም ቅድስናውን የመሰከሩለት በንግሥና ያለ ታላቅ የእግዚአብሔር አገልጋይ ነው፡፡ አባ ዳንኤልም ይህ በሰማ ጊዜ መሬት ላይ ወድቆ በራሱም ላይ አመድ ነስንሶ የዚህን የሮም ንጉሥ አኖሬዎስን ግብር ያሳየው ዘንድ ጌታችንን ለመነ፡፡ ደመናም መጥታ ነጥቃ ወሰደችውና ንጉሥ አኖሬዎስ ደጅ አደረሰቸውና ንጉሡን በዙፋኑ ላይ ሆኖ ባየው ጊዜ ከግርማው የተነሣ አይቶት በታላቅ ፍርሃት ውስጥ ሆኖ ከእግሩም በታች ሰገደለትና አኗኗሩንም ይነግረው ዘንድ በጌታችን ስም አማፀነው፡፡ ንጉሥ አኖሬዎስም ሰሌን በመታታት በእጅ ሥራው ደክሞ ከሚያገኘው በቀር ምንም ሳይበላና ሳይለብስ 40 ዓመት እንደሆነው፣ ሰሌን ታቶ ሸጦ ካገኘውም ውስጥ ከዕለት ምግቡ መግዣ የሚተርፈውን ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች እንደሚመጸውት፣ ምግቡም እንጀራና ጨው፣ ቅጠል መጻጻም እንደሆነ፣ የማንንም ንብረት ፈጽሞ እንዳልንካ፣ ድንግልናውንም ጠብቆ እንደሚኖር ነገረው፡፡ አባ ዳንኤልም ድጋሚ ከእግሩ ሥር ወድቆ ሰግዶለት ስለ ትምክህቱም ፈጽሞ እያዘኑ ወደ በዓታቱ ተመልሷል፡፡ አባ ዳንኤል አንድ ቀን ከረድኡ ጋር ወደ እስክንድርያ ሲጓዝ ስሙ ምህርካ የሚባል እብድ አገኘ፡፡ ብዙ እብዶችም ይከተሉት ነበር፡፡ እርሱም ለአገሩ ሰዎች ሁሉ በእውነት ያበደ ይመስላቸው ነበር፡፡ አባ ዳንኤልም እጁን ይዞ ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ወስዶ ትሩፋቱን ተጋድሎውን ነገረው፡፡ ከሊቀ ጳጳሳቱም ጋር ሆነው እብዱን ስለራሱ እንዲነግራቸው በእግዚአብሔር ስም ባማሉት ጊዜ ከዝሙት ጦር በመሸሽ ራሱን እብድ እንዳስመሰለ ነገራቸው፡፡
አንድ ቀን አባ ዳንኤል በሌሊት በበረሃ ውስጥ በጨረቃ ብርሃን ሲጓዝ በተራራ ላይ ተቀምጣ ጠጉሯ መላ ሰውነቷን የሸፈናት በዚያም በረሃ ስትኖር በተሰነጠቀ ዓለት ውስጥ 38 ዓመት ብቻዋን ማንም ሳያያት የኖረች ጻድቅ እናት አግኝቶ ምሥጢሯን ሁሉ ነግራዋለች፡፡ እርሷም ቅድስት አመተ ክርስቶስ ናት፡፡ አባ ዳንኤልም 38 ዓመት ሙሉ በዚህ በረሃ ምንም ሰው ሳታይ የኖረችበትን ተገድሎዋን በዝርዝር ነግራቸዋለች፡፡ እርሳቸውም ወደ ገዳማቸው ተመልሰው ለአበ ምኔቱና ለመነኮሳቱ ታሪኳን በመንገር ልብስ ይዘውላት ቢመጡ ዐርፋ አግኝተዋታል፡፡
አባ ዳንኤል የልዮንን የክህደት ደብዳቤ ወታደሮቹ አምጥተው በመነኮሳቱ ፊት ሲያነቡ ደብዳቤውን ተቀብሎ በሕዝቡ ፊት ቀዶታል፡፡ ወታደሮቹም አባ ዳንኤልንደብደበው ከገዳሙም አሳደውታል፡፡ ብዙ ሥቃይም አድርሰውበታል፡፡ አባ ዳንኤል በአንዲት ዕለት ከደናል ገዳም ደርሶ ደጁን አንኳኳ፡፡ እነርሱም አባ ዳንኤል መሆኑን ዐውቀው ከፈቱለት፡፡ አንዲት ሴትም ራሷን ዕብድ አስመስላ በደጅ የምትተኛ ሴት ነበረች፡፡ እርሱም ዕብድ መስላ በደጅ ስለተቀበጠችው ሴት አበምነቷን ሲጠይቃት እብድ መሆኗን ነገረችው፡፡ አባ ዳንኤል ግን ዕብድ የመሰለቻቸው ሴት እብድ ሳትሆን በድብቅ በታላቅ ተጋድሎ የምትኖር ቅድስት ሴት መሆኗን ነገራት፡፡ ዕብድ የተባለችውም ሴትም አባ ዳንኤል ምሥጢሯን እንደገለጠባት በስውር ዐውቃ ወዲያው ደብዳቤ ጽፋ ይኸውም ‹‹የተከበራችሁ እኅቶቼ ስላስቀየምኳችሁና ስላሳዘንኳችሁ ይቅር በሉኝ›› ብላ ጽፋ ደብዳቤውን አስቀምጣ ጥላቸው ጠፋች፡፡ እነርሱም ከዚያ በኋላ ዳግመኛ አላዩአትም፡፡ ደናግል ወደሚኖሩበት ገዳም አንድ የወንበዴዎች አለቃ ሰይጣን አነሳስቶት ወደ ገዳሙ በአባ ዳንኤል ተመስሎ ቆቡን ደፍቶ በሩን አንኳኳ፡፡ ደናግላኑም ሊዘርፋቸው መምጣቱን ምንም ባለማወቅ ይልቁንም አባ ዳንኤል መጣ ብለው በሩን ከፈቱለትና አስገቡት፡፡ እግሩንም አጥበው ለበረከት ብለው የእግሮቹን ዕጣቢ በፊታቸው ላይ ረጩት፡፡ ከመካከላቸውም አንዷ ዐይነ ሥውር ነበረችና ዐይኗ ወዲያው በራላት፡፡ በዚህም ደናግሉ እጅግ ተደስተው ‹‹አባ ዳንኤል አንተ ንዑድ ክቡድ ነህ›› ብለው ሰገዱለት፡፡ ይህን ጊዜ የሽፍቶቹ አለቃ በጣም ደንግጦ በመጸጸት ወደ አባ ዳንኤል ዘንድ ሄዶ ያደረገውን ሁሉ በመናገር ንስሓ ገባ፡፡ መንኩሶም በታላቅ ተጋድሎ መኖር ጀመረ፡፡ እርሱም ተአምራት እስከማድረግ ደርሶ በሰላም ዐረፈ፡፡ የአባ ዳንኤልም ተጋድሎና ተአምር ምን ቢጽፉት የሚያልቅ አይደለም፡፡ ዕረፍቱም በደረሰ ጊዜ ጌታችን ታላቅ ቃልኪዳን ሰጥቶት ቅድስት ነፍሱን ወደ እርሱ ወስዷታል፡፡ ዕረፍቱም ግንቦት 8 ቀን በታላቅ ክብር ተፈጽሟል፡፡
በረከቱ ይደርብን! ምልጃው ከይለየን አሜን!!!
ስምን ስም ያነሳዋልና በዚሁ አጋጣሚ ኢትዮጵያዊውን ጻድቅ የትግራይ ገርዓልታውን አቡነ ዳንኤልንም ይወቋቸው፡፡ አቡነ ዳንኤል ዘገርዓልታ አባታቸው መልክአ ሥላሴ እናታቸው ዓመተ ጽዮን ሲባሉ የትውልድ ሀገራቸው ትግራይ ገርዓልታ ነው፡፡ በ7 ዓመታቸው የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ተምረው አጠናቀው በ13 ዓመታቸው መነኮሱ፡፡ ሊቃውንቱ ‹‹ማኅቶተ ገዳም›› እያሉ የሚጠሯቸው ገድለኛ አባት ናቸው፡፡ አስገራሚው ባለ 4 ዓምዱና 40 ያሸበረቁ ሥዕላት ያሉት አስደናቂው ገድላቸው የት እንዳለ አይታወቅም፣ እኛ ሀገር ገድላቸው የለም፡፡ 2ኛውን ገድላቸውን ፖርቹጋሎች ከጠባቂው ገዝተው ወስደው በሀገራቸው አሳትመውታል፡፡ ገድሉን የሸጠው ጠባቂም ሆዱ ተነፍቶ በስብሶ ተልቶ ከቤተ ክርስቲያኑ በራፍ ላይ ወድቆ ሞቷል፡፡ የጻድቁ የዕረፍታቸው ዕለት ኅዳር 6 ቀን ትግራይ በሚገኘው ገዳማቸው በደማቅ ሁኔታ ይከበራል፡፡ ገዳማቸው የሚገኘው እጅግ ከፍተኛ ተራራ ላይ ሲሆን ከላይ ሆነው ወደታች ሲመለከቱ መሬት የሚደረስባት አትመስልም፡፡ እስቲ ከፎቶው ላይ ይመልከቱት!
(ምንጭ፡- የታኅሣሥና የግንቦት ወር ስንክሳር;መለከት 14ኛ ቁ5-1998 ዓ.ም፣ የቅዱሳን ታሪክ-108 &166)