Showing posts with label ድንቅ ተአምር - ሰሜን አሜሪካ ሚኒሶታ. Show all posts
Showing posts with label ድንቅ ተአምር - ሰሜን አሜሪካ ሚኒሶታ. Show all posts

Tuesday, December 22, 2015

ድንቅ ተአምር - ሰሜን አሜሪካ ሚኒሶታ


ትላንት እሁድ ታህሳስ 10/2008 ዓ.ም በጾመ ነቢያትን ግዜ በደብረ ሰላም መድኃኔዓለም የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የተነገረ ተዓምር ላካፍላችሁ።

ቦታው ሰሜን አሜሪካ ሚኒያፖሊስ ሚኒሶታ ውስጥ ነው። እህታችን ዘጠኝ ወር በማሕጸኗ የተሸከመችውን ጽንስ በሰላም ተገላግላ እንደ እናት ወግ ልጇን አቅፋ ስማ ተንከባክባ ለማሳደግ ጊዜዋ ደርሶ ነበርና መያዝ የሚገባትን ነገር ሁሉ አዘጋጅታ ጨርሳ ወደ ሆስፒታል ታመራለች። በዚህ በጭንቅ ሰዓት ታድያ ካዘጋጀችው እቃዎቿ አንዱ የእናታችን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ስዕለ አድኅኖ ነበር። እህታችን ከመግባቷ በፊትም " እመቤቴ በሰላም ተገላግዬ ከቤተሰቦቼ በደስታ እንድገናኝ በሰላምም ወደቤቴ እንድገባ ከልጅሽ ከመድኅኔዓለም አማልጂኝ ጭንቁን አቅልይልኝ" ብላ ጸሎት አደረገች። ከጥቂት ጊዜም በኋላ ሴት ልጅን በሰላም ተገላገለች ሁሉም ነገር ደስታ ሆነ። ነገር ግን ይሄ ደስታ ምንም ያህል ሊቆይ አልቻለም ነበር። ባለቤቷ መታጠቢያ ክፍል ደርሶ እስኪመለስ ድረስ ነገሩ ሁሉ የተገላቢጦሽ ሆነ ያ ሁሉ ደስታ በደቂቃዎች ወደሃዘን ተለወጠ። እህታችን የወለደቻትን ልጅ እያጠባች ባለችበት ሰዓት በድንገት ራሷን ትስታለች። ወዲያው ሃኪሞች ተጠሩ ከፍተኛ እርዳታ ተደረገላት ነገር ግን መንቃት አለቻለችም። በዚህም ምክንያት በከተማዋ አሉ የተባሉ ስፔሻሊስት ዶክተሮች እና ሊሎችም ከፍተኛ የሕክምና ባለሞያዎች ቢሯሯጡም መልሱ ከነሱ አልነበረምና ምንም ሊረዷት አልቻሉም። በዚህ ጊዜ መላው ቤተሰብ በሃዘን ተዋጠ። 

በከተማው ካሉት አቢያተ ክርስቲያናት አንዱ ወደሆነው ታላቁ ደብር ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን በመምጣት ዘወትር በማሕሌት በኪዳን እንዲሁም በቅዳሴ ሰዓት በካሕናት አባቶች ጸሎት እንዲያዝላት ሽና ስሟ እየተጠራ እንዲጸለይላት
ይጠይቃሉ።ካሕናቱም በፍጹም ታዛዥነት ጽሎቱን ይጀምራሉ። እህታችን በዚሁ ሁኔታ ላይ እንዳለች ሳምንታት አለፉ። ካሕናቱም ጽሎቱን ቀጠሉ ነገር ግን አንድ ያልተጠበቀና አስደንጋጭ ነገር ተፈጠረ።የተፈጠረው ነገር ያልተጠበቀና እጅግ ተስፋ አስቆራጭ ነበር ሙሉ የሰውነት ክፍሏ ስራ አቆመ።የልብ ምቷም ቆመ። ሃኪሞቹ ተጠርተው ቢመጡም ከዚህ በላይ ምንም ማድረግ አይችሉም ነበር። ይሄን ጊዜ በሰው እጅ ያለው ተስፋ ሲሟጠጥ ሸክም ሲከብድ ቢዘገይ እንኳን የሚቀድመው የሌለው አምላክ ስራውን የጀመረው። እህታችን በእናቱ ፊት ለምልጃ ያቀረበችው ጸሎት ከዶክተሮቹ እጅ ተቀብሎ ስራውን መስራት ጀመረ። የተገጣጠሙላት መሳርያዎች ሳይነቀሉ ለስድስት ደቂቃዎች ቆሞ የነበረው የልብ ምቷ በድንግል አማላጅነት በመድኃኔዓለም ሐኪምነት ስራውን ጀመረ። ሃኪሞቹ በጣም ደነገጡ ምንም ያደረጉት ነገር ሳይኖር ለስድስት ደቂቃዎች ስራ አቁሞ የነበረው ልብ አሁን ደግሞ መስራት ጀመረ። ይሄ ከሰው ልጅ አእምሮ በላይ ነው። እስከዛሬም ሆኖ የማያውቅ ይሆናል ተብሎም የማይጠበቅ በጣም አስገራሚ ነገር ነው የተደረገው የሚል ብቻ ነበር የነሱ መልስ። ከዚህም በኋላ እህታችን ሙሉ በሙሉ ከበሽታዋ ድና እንደጓጓችለት በእመቤታችንን ምልጃ በመድኃኔዓለምን ምህረት ለዚህች ቀን ደርሳ ልጇን ታቅፋ አምጥታ ክርስትና ለማስነሳት በቃች ልጅቷም ወለተ ኪዳን ተብላ ተሰይማለች። ይህንን በሰው ሃሳብ ሲመዘን እጅግ ከባድና ከአስተሳሰባችን በላይ የሆነን ነገር ሌላ ሰው ቢናገረው እንዴት ይታመናል? በሳይንስ እይታ የልብ ምት አይደለም ለስድስት ደቂቃ ቀርቶ ለጥቂት የደቂቃዎች ሽርፍራፊ እንኳን ስራ ቢያቆም ያ ሰው ሞቷል ማለት ነበር። በሰው የተዘጋውን በር ሳይሆን በእግዚአብሔር እጅ ያለውን ቁልፍ ተመልከት እንዳሉ አቡነ ሺኖዳ ሳልሳዊ እሱ ታሪክን ቀያሪ ነውና የአራት ቀን እሬሳን ያስነሳ አምላክ ሃዘኑን በደስታ ለወጠ። የካሕናቱና የቤተሰቡ ያልተቋረጠ ጸሎት መንበረ ጸባዖት ደረሰ። አዎ በትክክልም ተደርጓል እህታችንም በአውደ ምህራት ቆማ በጸሎት ሲያስቧት የሰነበቱትን ካሕናት እና ምዕመናን አመስግና የጭንቅ ጊዜ ደራሿን ድንግልን ከምንም በላይ ደግሞ እርሱ ሐኪም እርሱ ስፔሻሊስት ሆኖ ለዚህ ያበቃትን ጌታ መድኃኔዓለምን በአንደበቷ አመሰገነች።
"ወመኑ መሐሪ ዘከማከ"
"አቤቱ እንዳንተ ያለ መሐሪ ማነው?" አይደል ያለው ሊቁ!
እህታችንን ያማለደች እመቤታችን ምልጃዋ ጸጋ ረድኤት በረከቷ አይለየን። መሐሪው አምላካችን የያንዳንዳችንን የልቡና መሻት ይፈጽምልን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!