Tuesday, October 6, 2020

የአየር አጋንንት እና የአዚም መንፈስ

በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም
አጋንንት በሕይወታችን የሚያደርስብንን ችግር እስክናውቅ እንቸገራለን፣ ውጊያው እስኪገባን ግራ እንጋባለን፣ እውነቱ እስኪገለጥልን እውነቱ ሐሰት ይመስለናል፡፡
ሼር በማድረግ ለወዳጆ አዳርሱ!
ተወዳጆች ሆይ በክፍል ሃያ አምስት የአየር አጋንንት በጸሎት ሰዓት በማዞር፣ በማቅለሽለሽ እና ሌሊት በእንቅልፍ በማስፈራራት እንዴት እንደሚፈትነን አይተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ የአየር አጋንንት እና የአዚም መንፈስ የጸሎት ሕይወታችንንና ሌላውንም እንዴት እንደሚያቃውስ እናያለን፡፡ የቅዱሳን አምላክ ምስጢሩን ይግለጽልን።
ወዳጆቼ የአየር አጋንንት በራሱ በጸሎት ሰዓት ፈታኝ ቢሆንም ከአዚም ወይም ከአፍዝ አደንዝዝ መንፈስ ጋር በማበር በጸሎታችን እንቅፋት ይሆናል፡፡ የአዚም መንፈስ የምንለው የማፍዘዝ፣ የማደንዘዝ፣ ቸልተኛና ግዴለሽ የሚያደርገን መንፈስ ነው፡፡ የዚህ መንፈስ ታላቁ ጥቃት በመላው በመንፈሳዊ ሕይወታችን ላይ ቢሆንም በጸሎት ሰዓት እጅጉን በርትቶ ይታይብናል፡፡ እንዲሁም መንፈሳዊ ተግባራትን ለማከናወን ለምሳሌ ለመስገድ፣ ለማስቀደስ፣ ጉባኤ ሄደን ለመማር፣ ለመመጽወት እና ሌላም በጎ ምግባር ልንሠራ ስንነሳሳ መንፈሱ ክንውናችንን ገና በሐሳብ ደረጃ የማኮላሸት እና ለእኛ አሳማኝ በሚመስል ምክንያት የማበላሸት ሥራን ይሠራል፡፡
ቅዱስ ጳውሎስ በገላትያ የሚኖሩ ሰዎችን አስተምሮ አጥምቆ በጌታችን አሳምኗቸው ነበር፡፡ እነሱም እግዚአብሔርን በሃይማኖት አውቀው ብዙ ታምራት እስከ ማድረግ ደርሰው ነበር፡፡ ግን ቅዱስ ጳውሎስ ከሔደ በኋላ ሐሰተኛ ክርስቲያኖች ገላትያ ገብተው ‹‹ክርስቶስ ዕሩቅ ብእሲ ነው እንጂ የእግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጅ አይደለም›› ብለው ስላሳቷቸው በገላትያ ክታቡ ላይ ‹‹የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፣ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው?›› በማለት ይጠይቃቸዋል፡፡ /ገላ 3÷1/
ወዳጆቼ ከዚህ ከቅዱስ ጳውሎስ መልእክት የምንረዳው አዚም የሚባል እንዳናስተውል የሚያፈዝ፣ አንዳች ነገር እንዳንሠራ የሚያደነዝዝ መንፈስ መኖሩን ነው፡፡ ሌላው ‹‹ማን አደረገባችሁ?›› ያለው የአዚም መንፈስ በሰው ላይም የሚደረግ መንፈስ መሆኑን ያስረዳናል፡፡ ጠንቋዮች የአዚም መንፈስ በመሳብ ሰዎች ፈዘው፣ ደንዝዘው እንዲኖሩ ያቆራኙታል፡፡
የአዚም መንፈስን ካነሳን እስኪ ወደ ኃላ ሂዱና የትምህርት ቤት ጊዜያችሁን አስታውሱ? ትዝ ካላችሁ ትምህርት ቤት እየተማራችሁ ድንገት እንቅልፍ እንቅልፍ የሚል ስሜት፣ መደበት፣ አስተማሪው በሚያስተምረው ግራ ማጋባት ወዘተ ስሜቶች የአዚም መንፈስ ስሜቶች ናቸው፡፡ የአዚም መንፈስ በተማሪዎች ላይ በሦስት መልኩ ይከሰታል፡፡ አንደኛው የሰውን ብሩህ አእምሮ ለመስለብ በሚደረገው በምቀኞች ተስቦ እንዲጠናወተን ይደረጋል፡፡ ይህም አእምሮን እውቀትን ለመስለብ የሚጠቀሙበት ነው፡፡ እንደ መተት አጋንንት ስበው ያስገቡታል፡፡ ሁለተኛው በሰው ብሩህ አእምሮ በመቅናት ተማሪው ጉብዝናውን አጥቶ ፈዞ ደንዝዞ ትምህርት እንዲተው፣ እንዲያስጠላው አልያም ትምህርቱን እርግፍ አድርጎ እንዲተውና ባተሌ ሆኖ እንዲቀር የሚደረግ ነው፡፡ ሦስተኛው እራሱ የአዚም አጋንንቱ በመልካም ብሩህ አእምሮአችን በመቅናት በድንገት ወደ ሕይወታችን በመግባት የትምህርት እድላችንን ለማበላሸት የሚጠቀምበት ነው፡፡
ወዳጆቼ ከላይ ባየናቸው ሦስት ምክንያት ስንቱ ጎበዝ ለሀገር ለወገን፣ ለቤተሰብ የሚጠቅም ተማሪ በአዚም መንፈስ እድለ ቢስ ሆኖ ቀርቷል? ስንቱ ተስፋ የተጣለበት ተማሪ ክፍል ውስጥ እየደበተው፣ እያንቀላፋው ውጤቱ ተበላሽቷል? ይህ ችግር ዛሬም በኢሊመንተሪ፣ በሃይ ስኩል እና በዩኒቨርሲቲ የሚታይ ነው፡፡ 
ወዳጆቼ የአዚም መንፈስ በውስጣችን ያለውን መንፈሳዊ መቀጣጠልን በማጥፋት ወደ መሰላቸት ውስጥ ይከተናል፡፡ የአየር አጋንንት ከአዚም መንፈስ ጋር በመተባበር ቢቻል ገና ጸሎት ሳንጀምር አሰላችቶ ማስተው፣ ሰውነታችንን ማድከም እና ሕሊናችንን ማዛል ይጀምራል፡፡ ይህ ባይሆን ጸሎት ስንጀምር የጀመርነውን ጸሎት አንጨርስም፡፡ የአዚም መንፈስ ሕሊናና ልቦናን እንዲሁም ሙሉ አካልን ስለሚያደክም ተማሪ ከሆንን ያጠናነውን እንዳንይዝ፤ ሠራተኛ፣የቤት እመቤት ከሆንን የተባልነውን፣ ያስቀመጥነውን እንድንረሳ ያደርገናል፡፡
በተለይ በአሁን ሰዓት ብዙ ወጣቶች በአዚም መንፈስ ተይዘው እንዳይሠሩ፣ ባላቸው እውቀት እንዳይጠቀሙ፣ ደንዝዘው ፈዘው የእናት አባት ተጧሪ ሆነዋል፡፡ የት ይደርሳሉ የተባሉት እነሱም በማያውቁት ከጊዜ በኋላ በመጣ መፍዘዝ እና መደንዘዝ ውስጥ ገብተው ተስፋም ቆርጠው ሱሰኛ ሆነዋል፡፡ ይህ ሁሉ የአጋንንቱ ጥቃት ነው፡፡
የአዚም መንፈስ በተለይ በልጆች ላይ የተባሉትን እንዳይሰሙ፣ የተነገራቸውን እንዳያደርጉ የማፍዘዝ ሥራ ይሠራል፡፡ ቤተሰብም የገዛ ልጃቸውን ችግር ባለመረዳት ‹‹ይሄ ፈዛዛ፣ የደነዘዘ፣ የተባለውን የማይሰማ›› እያለ በመስደብ ለአዚም መንፈስ ሽፋን ይሆናል፡፡ ቤተሰብ የልጆችን ችግር ሳይረዱ በዝምታ ካለፉ የአዚም መንፈሱ በልጆች ውስጥ በመደላደል ተቀምጦ የሕይወታቸው መሰናክል ይሆናል፡፡
ተወዳጆች ሆይ የአዚም መንፈስ በጸሎት ጊዜ ድብት በሚያደርግ ከፍተኛ እንቅልፍ በማምጣት እንድናንቀላፋና በጸሎት መጽሐፍ የምናነበውን እንዳናስተውል ፍዝዝ ድንዝዝ በማድረግ ሕሊናችን ውስጥ እንዳይገባ ያደርገናል፡፡ የሚገርመው በአዚም መንፈስ በእንቅልፍ ምክንያት ጸሎታችንን ትተን ብንተኛ የመቃዠት እንጂ የእረፍት እንቅልፍ አንተኛም፡፡ የአዚም መንፈሱ ከእኛ ጋር ያለው ውጊያ ከመደበኛ እንቅልፋችን ጋር ሳይሆን እሱ እያመጣ በጸሎት ሰዓት ከሚቆልልብን እንቅልፍ ጋር ነው፡፡ ተኝተን ተኝተን እንቅልፍ የማንጠግብ እንሆናለን፡፡
አእምሮ በባሕሪው እንቅልፍ ከተጫጫነው መፍዘዝ እና መደንዘዝ እንጂ በንቃት መሥራት አይችልም፡፡ ስለዚህ ይህን የአእምሮ ጠባይ የአዚም መንፈሱ እየተጠቀመ ይጫወትብናል፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ ‹‹ራስ ሁሉ ለሕመም፣ ልብም ሁሉ ለድካም ይሆናል›› እንዳለው የአዚም መንፈስም በጸሎት ሰዓት ራስን ለሕመም፣ ልባችንንም ለድካም ይዳርግና የተለመደ መንፈሳዊ ትሩፋቶችን እንዳንሠራ ያደርገናል፡፡ /ኢሳ 1÷5/
ይህ የአዚም መንፈስ በጸሎት ሰዓት መጫጫን ሲጀምር ጸሎታችንን ለጊዜው በአቡነ ዘበሰማያት በማሰር 41፣ 64 ወይም 105 በመስገድ መንፈሱን ማራቅ ይቻላል፡፡ ግን እንዳንሰግድ የማዳከምና የማሰላቸት ሥራ ስለሚሠራ ይህ ከመሆኑ በፊት በትጋት ስግደት ልንቀድመው ይገባል፡፡ የአዚም መንፈሱ በጸሎት ሰዓት የማፍዘዝ የማደንዘዝ ሥራ ሊሠራ ሲል ወይም ከሠራ እኛም መስገድ ካስለመድን ከእኛ ባስ ወዳለው ይሄዳል እንጂ ከእኛ ጋር በመታገል ጊዜውን አያባክንም፡፡
የአየር አጋንንት ከአዚም መንፈስ ጋር በማበር ውስጣዊ መደንዘዝ ይፈጥርብናል፡፡ በዚህም አቅም እንድናጣ፣ ጉልበታችን እንዲዝል፣ የአእምሮአችንና የአካላችንን ኃይል እንድናጣ ያደርገናል፡፡ ወዳጆቼ የአፍዝዝ አደንዝዝን ክፉ መንፈስ በጸሎት በስግደት ካልተዋጋነው ነገ በመደበኛ ሕይወታችን ውስጥ ያለው አሉታዊ ተጽዕኖው ከፍተኛ ስለሚሆን ልንቋቋመው አንችልም፡፡ በውስጣችን ያለው የአፍዝዝ የአደንዝዝ ክፉ መንፈስ በዘር በተዋርዶ ወደ ትውልዳችን እንዳይተላለፍ፣ የደነዘዙ የፈዘዙ ልጆች እንዳናተርፍ ‹ሳይቃጠል በቅጠል› እንደሚባለው መዘዙ በልጆቻችን ሳይመዘዝ በመንፈሳዊ የጦር ዕቃዎች በጾም በጸሎት በስግደት፣ በጸበል በቅዱስ ቁርባን በእግዚአብሔር እርዳታ ከእኛ ልናርቀው ይገባል፡፡
‹‹ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቶአል›› ት.ሆሴ 4÷6
‹‹ከትውልዱ ማን አስተዋለ?›› ት.ኢሳ 53÷8
ክፍል ሃያ ሰባት
የአየር አጋንንት በልባችን አድሮ እግዚአብሔርን፣ እመቤታችንን እና ቅዱሳንን ይሳደባል!
/ብዙ ወንድሞቼ እና እህቶቼ የሚሰቃዩበት ፈተና/
ይቀጥላል ….
ሰኔ 3-10-12 ዓ.ም
አዲስ አበባ

Tuesday, September 15, 2020

የአየር አጋንንት በልባችን አድሮ እግዚአብሔርን እመቤታችንን እና ቅዱሳኑን ይሳደባል


/ብዙ ወንዶሞቼና እህቶቼ የሚሰቃዩበት ፈተና/
በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም
አጋንንት በሕይወታችን የሚያደርስብንን ችግር እስክናውቅ እንቸገራለን: ውጊያው እስኪገባን ግራ እንጋባለን: እውነቱ እስኪገለጥልን እውነቱ ሐሰት ይመስለናል።
ሼር በማድረግ በዚህ ፈተና ለሚሰቃዩ ወገኖቻችን አዳርሱ!
ተወዳጆች ሆይ በክፍል ሃያ ስድስት የአየር አጋንንት እና የአዚም መንፈስ በመደበኛና በጸሎት ሕይወታችን እንዴት እንደሚፈትነን አይተናል። በዚህ ክፍል ደግሞ ብዙዎች ለሰው የማይነግሩት የማያወያዩት ግን የሚቸገሩበትን እናያለን። የቅዱሳን አምላክ ምስጢሩን ይግለጽልን። ወዳጆቼ የአየር አጋንንት እና ሌሎቹም ርኩሳን መናፍት በውስጣችን ከገቡ ግራ እስኪገባን ድረስ ቅዱሳንን ይሳደባሉ፡፡ እስኪ ብዙዎቻችንን የምንቸገርበትን የራሳችን ሐሳብ እስኪመስለን የምንሰቃይበትን የአጋንንቱን የፈተና ስልት እንመልከት፡፡ አጋንንት በጌታ ሰው መሆን ወይም ሥጋ መልበስ ላይ መጠራጠር የሳድርብሃል፡፡ ሰው መሆኑም እውነት እንዳይመስልህ ያደርግሃል፡፡
እመቤታችንን ‹እውን በድንግልና ነው የወለደችው›› ብሎ ጥርጥር ያጭርብሃል፡፡  ልትቆጣጠረው በማትችለው ሐሳብ ከውስጥህ ሆኖ እግዚአብሔርን ይሳደባል።  አንተም ይህ ውስጣዊ የአጋንንት ስድብ ካንተ ወይም እራስህ ከልብህ አመንጭተህ የተሳደብክ ይመስልህና ከመጨነቅህ የተነሳ ድንግጥ ትላለህ፡፡ አንዳንዱ በድጋጤ ድርቅ ይላል፡፡ በእመቤታችን ላይ ከውስጥህ ጸያፍ ነገር የሚናገር ድምጽ ትሰማለህ። በተለይ ጸሎት ላይ ሆነህ ስዕሏን ስታይ ስታመሰግናት በማትቆጣጠረው መልኩ ከውስጥ ሲሳደብ ብሎም በሥጋ እንድታስብ ያደርግሃል።
ቅዱሳንን አፍ ባያወጣም ከውስጥ ሲሳደብ ትሰማለህ፣ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የማይሆን ነገር በማሳሰብና የሚያስደነግጥህ ነገር ከውስጥ ሲናገር ትሰማለህ፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን አትደናገጥ ቅዱስ ዮሐንስ በራዕዩ ‹‹ታላቅንም ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው›› በማለት አጋንንት በፈጣሪና በቅዱሳኖቹ ላይ የስድብን አፍ እንደሚከፍት ተጽፏል /ራዕ 13÷5/
ስድቡ ያናንተ ስላልሆነ እንዳትጨቅ፣ ነፍስህም ከእግዚአብሔር አንድነት የምትለይ አይደለችምና አትጎዳም፡፡ ሰይጣን ከውስጥ ሲሳደብ ነፍስ ትሰማለች ያኔም ትጨነቃለች ትደነግጣለች፡፡ ወዳጄ ነፍስ ፈጣሪዋን ስለምታውቅ ፈጣሪን አትሳደብም፡፡ ስድብ ቀድሞም ከነፍስ የተገኘ አይደለም፣ነፍስ ለዚህ ዓይነት ግብር አልተፈጠረችምና፡፡ ግን ስድቡን በውስጥ ሆኖ የሚናገረው የአየር አጋንንት እና ሌሎች ርኩሳን መናፍስት ናቸው፡፡ በተለይ የአየር አጋንነት: ዓይነ ጥላ እና ዛር ካለ በማያባራ መልኩ ይሳደባል። እንኳን ካንተ ከሰው መስማት የሚዘገንንህን የስድብ ናዳ በልብህ ጓዳ ሲያዘንብ ትሰማለህ።
ወዳጄ ሰይጣን ወደ እኛ ሕሊናና ልቦና ቀርቦ ይሳደባል፡፡ ያኔ ነው ስድቡ ከአንደበታችን ሳይወጣ በውስጥ የምነሰማው፡፡ በርትተን ከጸለይን እየመጣ ስድቡን የሚተነፍስብንን ስለሚተው እኛም ወደ ንጽሐ ጠባያችን እንመለሳለን፡፡
ወዳጄ ሰይጣን ወደ ሕሊናህ ቀርቦ ሲሳደብ ብትሰማ አንዲት ቃል አትናገር አትማረር ይልቁንም ‹‹ይህ ሐሳብ ያንተ ነው›› በለው፡፡ ሐሳቡ የእሱ እንደሆነ ከነገርከው ሥራውን ያውቃልና ይደነግጣል፡፡ አጋንንቱ ከሰው ጋር እያወራህ ድንገት በውስጥህ እግዚአብሔርን፣ እመቤታችንን ቅዱሳንን ሰድቦ ሊያስደነግጥህንና ትኩረትህን ሊያሳጣህ ይችላል፡፡ ያኔም ‹‹ይህ ሐሳብ ያንተ ነው በለው››
ወዳጄ ሰይጣን የሕሊናውን ያውቃልና ስትነግረው ይሰማል በዛም ያፍራል፡፡ መቼም ‹‹ስነግረው እንዴት ይሰማል?›› ትል ይሆናል፡፡ ባንተ ያደረች ላንተ የተሰጠች ጸጋ እግዚአብሔር ታሰማዋለች፡፡ ‹‹እግዚአብሔር ያሳፍርህ›› በለው፡፡ ሰይጣናት በክፉና ባልባሌ ሐሳብ የሚፈትናችሁ ከሆነ አትጨነቁ፡፡ ሰይጣን ልብ ውስጥ ሆኖ ለመሳደብ የዝሙት አጋንንትም ድረሻው ላቅ ያለ ነው፡፡ ፍትወትን በዓይነ ሥጋ እያሳየ የሚያሰቃየን አጋንንት ለስድብ ሰይጣናዊ ምላሱን መዘርጋት አይከብደውም፡፡
በጸሎት ሰዓት የስድብ ናዳ ከልቡ ጓዳ እያመጣ ሲጭንብህ እራስህ እንዳይመስልህ፡፡ ሰይጣን ነውና፡፡ ነፍስም የሷ መስሏት ትጨነቃለች፡፡ ወዳጄ እንደዚህ ያለን ጽኑ ስድብ አንተ/ቺ/ እንኳን የፈጠራችሁን እግዚአብሔርን ቀርቶ የምታውቁትን ሰው አትሰድቡም፡፡ ‹‹ማረኝ፣ ይቅር በለኝ፣ መንግሥትህን አትንሳኝ›› እያለች የምትጸልይ ነፍስ እንዴት ትሳደባለች? ነገር ግን የዚያ የርጉም ሰይጣንን ስድብ ሰምታ ጭንቅ ይሆንባታል እንጂ፡፡
ይህ ፈተና በጸሎት ጊዜ ይበርታ እንጂ በመደበኛው ሕይወትህ ማለትም ሥራ እየሰራህ እየተዝናናህ ከወዳጅህ ጋር እየተጫወትክ ቁም ነገር እያወራክ ድንገት ከውስጥህ ፈንቅሎ ጸያፍ የስድብ አሎሎ ይጭንብሃል። አንተ በሥጋህም በሕሊናህም ሌላ ስራ ይዘህ ሰይጣን ግን በውስጥህ እግዚአብሔርን እመቤታችንን ቅዱሳንን ይሳደባል አንተንም የሕሊና እረፍት ይነሳሃል። አንዳንዱንማ ጨርቅ መጣል ነው የሚቀረው እንጂ በቁሙ ያሳብደዋል። አንዳንዶች አጋንንት ውስጣቸው ሆኖ እግዚአብሔርን እመቤታችንን ቅዱሳንን የሚሳደበውን መቋቋም አቅቷቸው ለከፋ ሕመም የዳረጋቸው አሉ። የማይፈልጉትን እንደ ገደል ማሚቱ ከውስጣቸው የሚጮኸውን ስድብ ክፉ ሐሳብ መቋቋም አቅቷቸው እየተበሳጩ የሚጎዱ አሉ።
ወዳጄ በግልና በማህበር ጸሎት:በቅዳሴ ወዘተ ጊዜ ከውጥህ ሆኖ ወደ ሰማይ የሚሳደበው ለምንድነው? ካልክ አንደኛ ጸሎትህን እርግፍ አድርገህ እንድትተው ነው። ሁለተኛ እግዚአብሔርን እያሰብክ የፍቅርና አባትነት ስሜት ሳይሆን የፍርሃት ስሜት እንዲሰማህ ለማድረግ ነው። ሦስተኛ እግዚአብሔር ምህረት ሰጪ ሳይሆን ቀጪ ነው የሚለውን ክፉ መርዙን ሊተክልብህ ነው። አራተኛ የተሳደብኩት እኔ ስለሆንኩ እግዚአብሔር አይምረኝም ይቅር አይለኝም እንድትል ነው። አምስተኛ ተስፋ አስቆርጦህ ከመንፈሳዊ ሕይወት ሊያስወጣህ ሲፈልግ ነው። ስድስተኛ ነፍስህ በመንፈስ እንዳትቦርቅ ሥጋህ እንድትጨነቅ ስለሚፈልግ ነው። ሰባተኛ ከውስጥህ በሚሳደበው ስድብ አስጨንቆህ እራስህን ከመጉዳት እስከ ሞት ሊያደርስህ ነው።  ስለዚህ ንቃበት!
ከዚህው ጋር በተያያዘ ሰይጣን በሕሊናችን በጸሎት ሰዓት ስለሚሳደብ እኛ የተሳደብን የሚመስለን ለምንድነው? ካልን ከውስጥ ከሚወጣ ምስጋና ጋር ስድብ ስለሚወጣ ነው ከራሳችን የሚመስለን፡፡ ነገር ግን ምስጋናችን ከሰይጣን ስድብ ጋር አይቆጠርም፡፡ እኛ ፈጣሪ ፊት የቆምነው ለስድብ ሳይሆን ለምስጋናና ለጸሎት እንደሆነ ፈጣሪ ያውቃልና፡፡ እግዚአብሔርን የምትወድ ነፍስ ስለያዝክ የሰይጣንን ስድብ እየናቅህ አመስግን፡፡ ያማረ የተወደደ ምስጋናህን ከከዳተኛና ከተሳዳቢ ከሰይጣን ለይቶ የሚያውቅ አምላክ ነው ያለህ፡፡ ምንም የሰይጣን ስድቡ ካንተ ምስጋናና ጸሎት ጋር አንድ የሆነ ቢመስልህም ምስጋናዎችህ በእግዚአብሔር ዘንድ ከስድቡ ጋር አንድነት ስለሌላቸው ንጹሐን ናቸው፡፡
ወደጄ ሰይጣንን እራሱ ውስጥህ ሆኖ ይሳደብና የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ጠቅሶልህ ‹‹መንፈስ ቅዱስን የሰደበ ኃጢአቱ አይሰረይለትም›› እያለ ይሞግትኃል ያስጨንቅኃል፡፡ ሰይጣን ይህንን ኃይለ ቃል፣ ብዙዎችን ለማታለል ተጠቅሞበታል፡፡ ‹‹መንፈስ ቅዱስን የሰደበ›› ማለት መንፈስ ቅዱስ ሕፁፅ ያለ፣ ከሦስቱ አካላት አንዱ አይደለም ብሎ የካደ ኃጢአቱ አይሰረይም ማለት ነው፡፡ /ማቴ 12÷31/
ስለዚህ የሰይጣንን ስድብ በውስጥህ ተቃቀመው እንጂ ‹እኔ ነኝ፣ እግዚአብሔር ቢቀስፈኝስ፣ በጠራራ ፀሐይ መብረቅ ቢያወርድብኝስ: ጸሎቴን አይሰማኝም›› እያልክ ነፍስህን አታስጨንቃት ነፍሳዊ ሰላሟንም አታሳጠት፡፡ ይህ ፈተና ያንተ ብቻ ሳይሆን የአብዛኛው ምዕመናን ፈተና ስለሆን ሐሳቡን አታዳምጥ ተቃወመው፡፡
"ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቷል" ት.ሆሴ 4÷6
"ከትውልዱ ማን አስተዋለ" ት. ኢሳ 53÷8
ክፍል ሃያ ስምንት
የአጋንንት ፈተና በአጽዋማት ወቅት!
ይቀጥላል .....
ሰኔ 3-10-12
አዲስ አበባ

Tuesday, August 18, 2020

የአየር አጋንንት ፈተና በአጽዋማት ወቅት

/ያላወቅነው ያልነቃነው ግን ብዙ በረከት ያጣንበት/
በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም
አጋንንት በሕይወታችን የሚያደርስብንን ችግር እስክናውቅ እንቸገራለን፣ ውጊያው እስኪገባን ግራ እንጋባለን፣ እውነቱ እስኪገለጥልን እውነቱ ሐሰት ይመስለናል፡፡
ሼር በማድረግ ለወዳጆ አዳርሱ!
ተወዳጆች ሆይ በክፍል ሃያ ሰባት የአየር አጋንንት በልባችን አድሮ እግዚአብሔርን፣ እመቤታችንን እና ቅዱሳንን እንዴት እንደሚሳደብ አይተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ የአየር አጋንንት በአጽዋማት ወቅት እንደሚፈትነን እናያለን፡፡ የቅዱሳን አምላክ ምስጢሩን ይግለጽልን፡፡
ወዳጆቼ የአየር አጋንንት ከመቼውም በበለጠ በተንኮል ሥራ የሚጠመደው በአጽዋማት ወቅት ነው፡፡ እንደ ዓቢይ ፣ ገና፣ ሐዋርያት እና ፍልሰታ ያሉ የአዋጅ አጽዋማት ላይ ከመቼውም በበለጠ በጸሎት ጠንከር ስለምንል አጋንንቱ በፈተና ጠንከር ብሎ ይመጣል፡፡ የአየር አጋንንት በአዋጅ አጽዋማት ወቅት ቤተ ክርስቲያን ሄደን እንዳንጸልይ በማሳነፍ፣ በቤታችን እንዳንጸልይ በማይረባ ምክንያት በማደናቀፍ፣ ጸሎታችንን በማስታጎል የጸሎት በረከታችንን ያሳጣናል፡፡ እንኳን እኛ በገዳም ያሉ አባቶችም የአጋንንት ፈተና የሚበዛባቸው በአጽዋማት ወቅት ነው፡፡
አንዳንዶቻችን የአዋጅ ጾም ሲመጣ በፉከራ ‹‹ይህንን ጾምማ በጾም በጸሎት ነው የማሳልፈው›› ብለን ለራሳችን ቃል እንገባለን፡፡ ግን እንኳን የገባነውን ልንተገብር የባሰ ስንፍናና ኃጢአት ውስጥ ተዘፍቀን ያለ ሰዓት በጠዋት ከጾም እስከ ፍስክ ያሉትን ምግቦች ስልቅጥ አድርገን እንበላለን። መጠጥ የምንጠጣውም ‹‹ይሄን ጾምማ መጠጥ የደረሰበት አልደርስም›› እንላለን፡፡ ከቀናት በኋላ እዛው እንገኛለን፡፡ በሥጋ ፍትወት በዝሙት የምንፈተነውም ‹‹ይሄን ጾም ከዝሙት ርቂ እራሴን ጠብቂ አሳልፋለሁ›› እንላለን ግን ከበፊት የበለጠ በዝሙት ተፈትነን እንወድቃለን፡፡
በተለያዩ ፈተናዎች ጸሎት የተውን ‹‹ጾሙ ብቻ ይግባ ወዳሴ ማርያሙ፣ አርጋኖኑ፣ ሰይፈ ሥላሴው፣ ዳዊቱ ወዘተ አይቀረኝም ተግቼ ጸልያሁ›› እንላለን፡፡ ግን እንኳን ውዳሴ ማርያም፣ ዳዊት ቀርቆ አንድ አቡነ ዘበሰማያት መጸልይ አቅቶች ማታ ስንፍና ተጭኖን ሌሊት እንቅልፍ ጥሎያ ያለ ጸሎት እንውላለን እናድራለን፡፡ ስግደት ለመስገድ በዓለ ሃምሳ ከለከለኝ ይምጣልኝ ጾሙ ብለን የፎከርነው ጾሙ ሲመጣ ስንፍናን እንደ ባርኔጣ እራሳችን ላይ ጭነን፣ የወገብ፣ የጉልበት ችግር አለብኝ ብለን እንኳን የትሩፋት፣ የተጋድሎ ስግደት ልንሰግድ ቀርቶ ጸሎት ከመጀመራችን በፊት ሦስት ጊዜ ለሥላሴ የአምልኮ ስግደት መስገድ የሚያቅተን እንሆናለን፡፡
ንስሐ ለመግባት የስንት ዓመት ቀጠሮ ይዘን ጾሙን ስንጠባበቅ ጾሙ ሲመጣ እንኳን ንስሐ ለንገባ በኃጢአት ተዘፍቀን ግራ ስንጋባ ጾሙ ያልፈናል፡፡ ወሬ ለማውራት ሁለት ሰዓት ብንቆም ጉልበቴን ወገቤን የማንል ጸሎት፣ ስግደት ስንጀምር ሳይሆን ገና ስናስብ እንደ አዛውንት በሕመም መዓት እንያዛለን፡፡ ሌሊት ለጸሎት እነሳለሁ ብለን ማታ በስልካችን አላርም ሞልተን ግን እንደ እከ ለሽሽሽሽ ብለን ተኝተን እኛ ሳንነሳ ነግቶ ወፎ ጩኸት አሰምቶ ይቀድመናል። ወዳጆቼ  ይህ የሚያሳየን በአጽዋማት ወቅት ከፍተኛ የአጋንንት ውጊያ እንዳለብን ነው፡፡ በጾም ወቅት ካሰብነው በባሰ አንዳች መንፈሳዊ ነገር ሳንተገብር ጾሙ ያልፈናል፡፡ እኛም በእጃችን ባለው ጾም ሳንጠቀም ወደ ፊት በሚመጣው ባልጨበጥነው ጾም ተስፋ እናደርጋለን፡፡
አጋንንት የበለጠ የኃጢአት ሕይወት ውስጥ ከትቶ፣ እኛን ከእግዚአብሔር ጋር አለያይቶ ለማስቀርት በአጽዋማት ወቅት በዝሙት፣ በስካር፣ በሱስ ወዘተ ይፈትነናል፡፡ ባለ ትዳሮችንም ከጾሙ በረከት ለማራቅ፣ በፍትወት በማስጨነቅ ይፈትናቸዋል ይጥላቸዋል፡፡ በአዋጅ የታዘዝነውን ጾም በርትተን እንዳንጾም ጥውልውል የሚያደርግ የረሃብ ስሜት እና የተለያየ ሕመም እንዲሰማን በማድረግ ያለ ሰዓት እንድንበላ ብሎም ጾሙን አፍርሰን የፍስግ እንድንበላ ያደርገናል፡፡
አንዳንዶች ሕመማቸው የሚቀሰቀሰው፣ ጨጓራቸውን የሚያማቸው በአጽዋማት ወቅት ነው፡፡ እነዚህ ሕመሞች ለአጋንንቱ ሽፋን ስለሚሆኑ ማንም ጾም በመጣ ቁጥር የሚነሳበትን ሕመም የአጋንንት ፈተና ነው ብሎ ለመቀበል ይቸገራል፡፡ ስለዚህ አጋንንት በደዊያት እየተመሰለ፣በሕመም እያታለለ እንደሚጫወትብን ማሰብ አልቻልንም፡፡ በልቶ እንጂ ጾሞ የሞተ ሰው ስለሌለ ከነችግራችን ልንጾም ይገባል፡፡
ጾም በመጣ ቁጥር አጋንንት የውስጥ ሕመም የሚቀሰቅስብን አንደኛ አጋንንት ጾም ስለማይወድ የእሱን ባሕርይ በቀላሉ ከእኛ ጋር ለማዋሐድ ይመቸዋል፡፡ ሁለተኛ ጾም እንዳንለምድ ያደርገናል፡፡ ሦስተኛ የማንጾም ከሆነ እንበላለን እንጠጣለን ስለዚህ በሥጋ ፍትወት በቀላሉ ለመፈተን ይመቸዋል፡፡ አራተኛ ጾም እግዚአብሔርን የምናገለግልበት በረከት ስለሆነ ከጾም አገልግሎት ለማራቅ ይመቸዋል፡፡ ነቢይት ሐና እግዚአብሔርን በጾም በጸሎት ሰማንያ አራት ዓመታት አገልግላለችና፡፡ /ሉቃ 2÷37/ አምስተኛ በመጾማችን የምናገኘውን በረከት እና መንፈሳዊ ኃይል እንዳይኖረን ያደረጋል፡፡ ስድስተኛ ጾም አጋንንትን ከእኛ የምናርቅበት፣ የምንላቀቅበት መንፈሳዊ የጦር ዕቃ ስለሆነ የማንጾም ከሆነ አጋንንቱ በውስጣችን ተመችቶት ደልቶት ይኖራል፡፡ ሰባተኛ የማንጾም ከሆነ አንጸልይም ስለዚህ እግዚአብሔር እንዳይለመነን ያደርገናል፡፡ ነቢዩ ዕዝራ ‹‹ስለዚህም ነገር ጾምን፣ ወደ እግዚአብሔርም ለመንን፤ እርሱም ተለመነን›› ያለው እግዚአብሔር በጾማችን እንደሚለመነን ያሳየናል፡፡ /ዕዝ 8÷23/
ነቢዩ ዳዊት ‹‹ነፍሴን በጾም አስመረርኳት›› ይላል፡፡ እኛ ግን ነፍሳችንን በጾም ሳይሆን በመብል በመጠጥ ነው የምናስመርራት፡፡ /መዝ 69÷10/ ስለዚህ የአየር አጋንንት እኛ የተለያየ ክፉ መናፍስት በእኛ ሕይወት በመግባት እንዳይፈትነን በጾም መጠንከር አለብን፡፡
‹‹ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቶአል›› ት.ሆሴ 4÷6
‹‹ከትውልዱ ማን አስተዋለ?›› ት.ኢሳ 53÷8
ክፍል ሃያ ዘጠኝ
የአየር አጋንንት ራሳችንን እንድናጠፋ ያደርገናል
ይቀጥላል …….
ሰኔ 6-10-12 ዓ.ም
አዲስ አበባ