Tuesday, July 21, 2020

የአየር አጋንንት የተረጋጋ መንፈስ እንዳይኖረን ያደርጋል

በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም
አጋንንት በሕይወታችን የሚያደርስብንን ችግር እስክናውቅ እንቸገራለን፣ ውጊያው እስኪገባን ግራ እንጋባለን፣ እውነቱ እስኪገለጥልን እውነቱ ሐሰት ይመስለናል፡፡
ሼር በማድረግ ለወዳጆ አዳርሱ!
ተወዳጆች ሆይ በክፍል ሠላሳ የአየር አጋንንት እና የብኩንነት ሕይወትን አይተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ የአየር አጋንንት እንዴት የተረጋጋ መንፈስ እንዳይኖረን እንደሚያደርገን እናያለን፡፡ ወዳጆቼ በዚህ ዘመን የተረጋጋ ሰው የታደለ ነው፡፡ የአየር አጋንነት አንዱ የፈተናው ስልት መረጋጋትን ማሳጣት ነው፡፡ የአየር አጋንንት ሲፈትነን አንድ ቦታ አርፈን አንቀመጥም፣ እንቅበዘበዛለን፣ እንኳን አካላችን ምላሳችንም አይረጋጋም፣ ሰው ሲናገረን ስደበው ተናገረው እያለ ይገፋፋናል፡፡ በተለይ ቤተ ክርስቲያን ስንገባ ውስጣችን ያለው ዓይነ ጥላ ከአየር አጋንንት ጋር በማበር ተረጋግተን እንዳናስቀድስ፣ እንዳንጸልይ፣ እንዳንማር የማስጨነቅ ሥራ በመሥራት ከቤተ ክርስቲያን በሆነ ምክንያት በማሳመን ‹‹ውጣ ውጣ›› ይለናል፡፡ የውሳኔ ሰው መሆን አንችልም፡፡ አንድ ነገር ብንወስንም ልክ ያልሆነ ውሳኔ ነው የምንወስነው፡፡ በስሕተቱ እንጸጸታለን፡፡ በዚህ የተነሳ አጋንንቱ በራስ የመተማመናችንን መንፈስ ያሳጣናል፡፡
የአየር አጋንንት ያለ መረጋጋት ስሜት ሲያሳድርብን ፊታችን የተረበሸ ይመስላል፣ ግራ ይገባናል፣ የደስተኝነት ስሜት አይነበብብንም፣ ያኮረፈ የተቆጣ ፊት እንዲኖር ያደርገናል፡፡ ብዙዎችን የአየር አጋንንት እየፈተናቸው በዓመት አንዴ የስቅለት ስግደት ቀን ጨንቋቸው፣ ሥርዓቱ አላልቅ ብሏቸው ከቤተ ክርስቲያን የሚወጡ አሉ፡፡ ቅዳሴ ለማቋረጥ የሚሞክሩና የሚያቋርጡ አሉ፡፡
ወዳጂቼ የአየር አጋንንተት በጸሎት ጊዜ ሲፈትነን የምናየው ምልክት አሉ፡፡ አንደኛ ጸሎቱ አልገፋ አላልቅ ይለናል፡፡ ሁለተኛ ጸሎቱ ስልችት ይለናል፡፡ ሦስተኛ ልባችንን ሕሊናችንነ ሰውሮ ከተጣላነው ሰው ጋር አንባ ጓሮ አስገጥሞን የጸሎት መጽሐፋችን ገጽ ያስቆጥረናል፡፡ አራተኛ ጸሎት ይዘን መረጋጋት ስንችል እንቁነጠነጣለን፡፡ አምስተኛ ወገባችን፣ ጉልበታችን እግራችን ይብረከረካል መቆም ያቅተናል፡፡ ስድስተኛ ጸሎት እያደረግን ኩንታል እንደተሸከመ ሰው ሰውነታችን ሁለ መናችን ይከብደናል፡፡ ሰባተኛ ጸሎቱ ባለበት ሐሳባችን ልባችን አይኖርም፡፡ ስምንተኛ በጸሎት ሰዓት እግዚአብሔር ፊት ምስጋናችንን አስረስቶ ጸሎታችንን ጭቅጭቅ ያደርግብናል፡፡ ለምሳሌ ‹‹እግዚአብሔር ምን አደረገልህ? ያንቺ ጸሎት ምን አመጣ? እነ እከሌ ጠንቋይ ቤት እየሄዱ ሕይወታቸው ተለወጠ አንቺ ግን እግዚአብሔር ይዘሽ ቤተ ክርስትያን ተመላልሰሽ ይኸው ባዶሽን አለሽ፣ ሥራ የለሽ፣ ትዳር የለሽ፣ ወይ ገዳም አልገባሽ ወይ ሞተሸ አልተገላገልሽ ወዘተ›› እያለ መጸለያችን ሳይታወቀን ጸሎቱን እንጨርሳለን፡፡ ስምንተኛ ሰውነታችን ላይ በተለይ ጀርባችን ላይ የሚርመሰመስ የሚሄድ ስሜት ይሰማናል። ዘጠነኛ ጸልት ይዘን ከፍተኛ የማናውቀው ፍርሃት ይሰማናል። አስረኛ ከፊት ለፊታችን ከጀርባችን ከጉናችን ውልብ ስልብ የሚል የማናውቀው ምስል ይታየናል: ሰው አብሮን የቆመ ሸከክ ክብድ ይለናል።
ለመቀበል የዘገየነው፣ የረሳነው ያበደርነው ገንዘብ ሁሌም ትዝ የሚለን ጸሎት ላይ ነው፡፡ ቀን ስልክ እደውልለታለሁ ያልነው ሰው ትዝ የሚለን ጸሎት ስንጀምር ነው፡፡ ብቻ የረሳነውን ነገር የምናስታውሰው፣ አደርገዋለሁ ብለን ጊዜ ያጣንበት ነገር የሚታወሰን ጸሎት ላይ ነው፡፡ የሚገርመው ቁጭ ብለን የማናስበው የሥራ እቅድ ጸሎት ላይ ሐሳቡ የሚመጣልን፡፡ ነጋዴ ከሆንን ትርፉ ወለል ብሎ የሚታየን፣ ኪሳራውም የሚታወቀን ጸሎት ላይ ነው፡፡ ወዳጆቼ ይህን ሁሉ ሐሳብ የአየር አጋንንት በጸሎት ጊዜ እያመጣ የሚጭንብን የተረጋጋ ጸሎት እና  መንፈስ እንዳይኖረን ለማድረግ ነው፡፡ አጅግ የሚገርመው የመንፈስ እርጋታ እና የነፍስ እፎይታ የምናገኝበት ቤተ ክርስትያን ሄደን የባሰ የምንጨነቅ፣ ስሜታችን ዝብርቅርቅ የሚልብን አለን፡፡ ይህ ሁሉ የእሱ ውጤት ነው፡፡
መረጋጋትን ያጣው የአየር አጋንንቱ እኛን ያለመረጋጋት ስሜት ውስጥ ይከተናል፡፡ እኛን እንዲህ ያድርገን እንጂ መነኮሳትን ከባዕታቸው ከገዳማቸው ሰላም በማሳጣት ያለመረጋጋት ስሜት ወስጥ እየከተታቸው እየረበሻቸው ክፉኛ ይፈትናቸዋል፡፡ እነሱም የአየር አጋንንቱን ያለመረጋጋት ፈተና መቋቋም ሲያቅታቸው በምክንያት ከገዳማቸው ይወጣሉ፡፡
የአየር አጋንንት ሰውን በማንከራተት የተጠመደ ነው፡፡ መነኮሳትን ንቀውና ጥለው የመጡትን ዓለም እንደ ገነት በማሳየት፣ ከገዳም ይልቅ የጽድቅ ሥራ በዓለም እንዳለ በማሳሰብ፣ ከገቡበት ገዳም በማስወጣት በዓለም እንዲንከራተቱ ያደርጋቸዋል፡፡ አጋንንቱ በፈተና ምክንያት ዓለም ውስጥ ከከተታቸው በኋላ ዓለማዊ ሕይወትን በማለማመድ፣ በቁሳዊ ነገር በመጥመድ በተንኮሉ መዳፍ ያስገባቸዋል፡፡ በገዳም ያለውን ፈተና ሳይቋቋሙ አጋንንቱ በሰፈረበት ዓለም ፈተናውን የሚቋቋሙት ምናልባት በእግዚአብሔር ፈቃድ በዓለም እንዲኖሩ የተፈቀደላቸው ብቻ ናቸው፡፡ የአየር አጋንንት ሰፍሮብን ብዙ ነገር ካለማመደን በኋላ ወደ ቀደመ ሕይወታችን ለመመለስ እጅጉን እንቸገራለን፡፡ እያንከራተተ ያኖረናል፡፡
አንድ መንፈሳዊ ሰው የተረጋጋ መንፈስ ከሌለው አንኳን ከሰው ከእግዚአብሔር ጋር አይስማማም፡፡ መረጋጋት የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ የመላበስ ምልክት ነው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወት ያለ መረጋጋት ካለ ለስሕተት እና ለኃጢአት እጅጉን የተጋለጥን ነን፡፡ ስለዚህ በሕይወታችን ያለመረጋጋት ክሥተት ከታየብን ቆም ብለን ራሳችንን መቃኘት፣ወደ ሰማይ አምላክ መመልከት ያስፈልገናል፡፡ የመረጋጋት መንፈስ ልግስና ከሰማይ አምላክ ነውና፡፡
‹‹ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቶአል›› ት.ሆሴ 4÷6
‹‹ከትውልዱ ማን አስተዋለ?›› ት.ኢሳ 53÷8
ክፍል ሠላሳ ሁለት
በአየር አጋንንት እና በሌሎች ሥራችንና ዕቅዳችን ይበላሻል
/ሩቅ አሳቢዎች ቅርብ አዳሪዎች፣አመድ አፋሾች/
ይቀጥላል …..
ሰኔ 8-10-12 ዓ.ም
አዲስ አበባ

Tuesday, July 7, 2020

ለእግዚአብሔር ያልንተንበረከከ፣ በአጋንንት የተማረከ ትውልድ

በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም
አጋንንት በሕይወታችን የሚያደርስብንን ችግር እስክናውቅ እንቸገራለን፣ ውጊያው እስኪገባን ግራ እንጋባለን፣ እውነቱ እስኪገለጥልን እውነቱ ሐሰት ይመስለናል፡፡
ሼር በማድረግ ለወዳጆ አዳርሱ!
ተወዳጆች ሆይ በክፍል ሠላሳ ሦስት የጠንካራ መንፈሳውያን ሰዎችን የአጋንንት ፈተና ተመልክተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ ከላይ የጠቀስኩትን እናያለን፡፡ የቅዱሳን አምላክ ምስጢሩን ይግለጽን፡፡ አሁን ያለነው ትውልድ በአጋንንት ስውር ደባ ስለተማረክን ለእግዚአብሔር ተገዝተን መንበርከክ አልቻልንም፡፡ የእኛ ትውልድ ከፍተኛ የማንነት ቀውስ ውስጥ እና የአጋንንት የተንኮል ውርስ ውስጥ ገብቷል፡፡ ከእግዚብሔር መንገድ ርቀን በራሳችን መንገድ ታንቀን ስለምንሄድ የአጋንንት ሰለባ እየሆንን ነው፡፡
በተለይ ወጣቱ የአጋንንትን የፈተና ስልት ስላላወቀ በሥጋ ፍላጎቱ እንደታነቀ ይኖራል፡፡ የእኛ ትውልድ አዋቂ ነኝ ይላል ግን ማወቁ ከፈተናው ለመላቀቁ ፍንጭ አልሰጠውም፡፡ ዛሬ መቶ መስገድ የዳገት መንገድ የሆነብን ለምንድን ነው? አንድ ሰዓት ቆመን ስናወራ የማይታክተን ለሃያ ደቂና ውዳሴ ማርያም መጸለይ ያቃተን ለምንድን ነው? ጽኑ እምነት አጥተን ሃይማኖትን በእምነት ሳይሆን በሥጋዊ እውቀት የምንመዝነው ለምንድን ነው? ጆሮአችን ቃለ እግዚአብሔር ሳይሆን ሐሜት ለመስማት ለምን ይዳክራል?
ጓደኛችን ለፍቶ ሠርቶ ከሚለወጥ አፈር ከደቼ በልቶ ቢፈጠፈጥ ደስ የሚለን ምቀኝነት ናላችንን ያዞረን ለምንድን ነው? እለት እለት ከአንደበታችን እውነት ሳይሆን ውሸት የሚወጣው፣ ከውሸት አልፈን ቅጥፈት የለመድነው ለምንድን ነው? ወዘተ …
ለእግዚአብሔር መንበርከክ ትተን ለአጋንንት ስንማለር መገለጫችን መንፈሳዊ በረከቶችን መጠራጠር፣ በእምነት መነጽር አለማየት፣ አለማመን፣ መንፈሳዊ ጸጋን በሥጋ እውቀት ማየት፣ ቸልተኛ፣ ግዴለሽነት፣ በሥጋም በነፍስም ተስፋ መቁረጥ፣ በዶግማና በቀኖና መናወጥ፣ በመንፈሳዊ ሕይወት አለማደግ አለመለወጥ ወዘተ ነው፡፡ ይህን ገዳፋ የምናተርፈው በቤሰተባችን የእምነት ደካማነት እና በአጋንንት ተጽዕኖ ነው፡፡ ወዳጆቼ መንፈሳዊ ጸጋ የራቀን የሥጋዊ ዝቅጠት የተጫነን ለእግዚአብሔር ከመንበርከክ ይልቅ እኛን እስከጠቀመን ድረስ ለአጋንንት ስንማረክ ትርፋችን ይህ ነው፡፡
ሱስና መጠጥ ያሠረው ወጣት ለአጋንንት መጫወቻና የአጋንንት ፍላጎት ማስፈጸሚያ ቢሆን አይገርምም፡፡ ይህ ትውልድ አይወቀስም አወቅን ዘመናዊ ሆንን ያሉ በእግዚአብሔር መባረክን ያልወደዱት ወላጆች የዘሩት ውጤት ነው፡፡ ቤተሰብ ልጆችን በሕፃንነታቸው በዕለተ ሰንበተ ቅዱስ ቁርባን ማቁረብ ትተው ወደ መጫወቻ ቦታ ይዘው በመሄዳቸው የእግዚአብሔርን ጸጋ ሳይሆን የዓለምን ዋጋ እንዲያዩ ነው ያደረጉት፡፡ በዕለተ እሑድ ማስቀደስ ሳይሆን መደነስ የለመደ ወጣት የአጋንንት ቁራኛ ቢሆን አይደንቅም፡፡
ትላንት በልጅነቱ እናት ‹‹ቅዳሴ ሂድ›› ስትለው ልጅ የዓይነ ጥላውና የአፍዝዝና የቤተሰብ ዛር ልጁ ላይ እያለቀሰ ‹‹አልሄድም›› ሲል አባት ‹‹ተይው ካልፈለገ አታስገድጅው፣ እንዲ ሆኖ ቢሄድም ምንም አይጠቅመውም›› በማለት ከቅድስናው ደጅ እያራቀ ሲከላከል የነበረው ቤተሰብ በሕፃኑ ላይ የዘራውን የቸልተኝነት፣ የእንቢተኝነት፣ የመብቱ ነው ጥያቄ ሲያድግ በልጁ መከራ ያጭደዋል፡፡
ትላንት ልጆችን የአጋንንት አረም ሲበቅልባቸው አረሙን ከመንቀል፣ መንፈሳዊ ሕይወታቸውን ከመከታተል ይልቅ ለሥጋዊ ደስታቸው እያደላን ሰማያዊ ደስታቸውን እናጨልማለን፡፡ ልጆቻችን በአጋንንት ምትሐታዊ ፍላጎት እየተነዱ በሕፃንነታቸው የአዋቂን ጸያፍ ሥራ ሲሠሩ ‹‹እሷ ፈጣን ናት፣ እሱ ብልጥ ነው፣ የሕፃን አዋቂ ናቸው›› እያልን በሃይማኖት ሳንገራቸው አሳድገን የሕፃንነት የኃጢአት ሕልማቸውን ከመሬት ብቅ እንዳሉ ያሳዩናል፡፡ ያኔ ቤተ እግዚአብሔር ሄደን ብንጮህ አጉልና የማይሰማ ጩኸት ነው፡፡ብቻ በልጅነታቸው ያሳየናቸውን የጥፋት መንገድ፣ አድገው መከራና ፈተና ሲያሳጭዱን እንኖራለን፡፡ እኛ ተባርከን ልጆቻችንን እንዳናስባርክ፣ እኛው ተሰላችተን አጋንንቱ መንገድ ዘግቶብን ለልጆቻችን የእርግማን መናፍስትን እናወርሳቸዋለን፡፡
በቅዳሴው በቁርባኑ፣በቃሉ ስላላስባረክናቸው አጋንንት እንደ ፈጣን ፈረስ እየሰገራቸው ወደ ጥፋት እና ወደ ኃጢአት ሜዳ ይጋልባቸዋል፡፡ ለልጆቻችን ንብረት እንጂ ሃይማኖታችንን ስለ ማውረስ ስላልተጨነቅን ልጆቻችን ንብረት አጥፊ፣ እግዚአብሔር ላይ አሿፊ ትውልድ ይሆናሉ፡፡ ሠርተን ያወረስናቸው እንጂ ተባርከን የሰጠናቸው መንፈሳዊ ስጦታ ስለሌለ አመንዝራና ሱሰኛ ይሆናሉ፡፡ ይህ የእኛ ድክመት ልጆቻችንን የአጋንንት መሥዋዕት እንዲሆኑ በሩን መክፈት ብቻ ሳይሆን የጥፋትንም መንገድ አሳይተናቸዋል፡፡ ዛሬ በየቤታችን የተሸከምናቸው የልጆቻችን ችግሮች መሠረቱ እኛው ነን፡፡ ስለዚህ ስንዴ ካልዘራንበት እርሻ አረማችንን አጭደን በቤታችን ከምረን መኖራችን ግድ ነው፡፡
በኖኅ ዘመን የነበረው አመንዝራ ትውልድ፣ በሎጥ ዘመን የነበረው ግብረ ሰዶማዊው ትውልድ ቤተሰባቸው አረም ሆነው የዘሩት የጥፋት እና የመቅሠፍት ትውልድ በእኛም ዘመን እያየነው ነው፡፡ ስለዚህ ለእግዚአብሔር ያልተንበረከከ ትውልድ፣ ለሰይጣን የጥፋት እንጨት ሆኖ ሲማገድ፣ በኃጢአት ሲነድ ማየት ግድ ብሎናል፡፡
ወላጆች እስኪ ልጆቻችሁ የሚያዩትን የሕፃናት ፊልሞች ተመለከቱ፡ ምዕራባውያን በሕፃናት ፊልም ሰይጣንን እያለማመዷቸው ነው፡፡ በሕፃናት ፊልም ላይ የሚታዩትን ገጸ ባህሪያት ብናያቸው ወጣ ያሉ፣ የሚያስፈሩ፣ የሉሲፈር ገጽታ ያላቸው ወዘተ ናቸው፡፡ የሚጫወቱት ጌሞች ለንቃተ ሕሊና የሚረዱ ሳይሆን አጋንንትን የሚያለማምዱ ናቸው። እነዚህን ምዕራባውያን የራሳቸውን ትውልድ በሚፈልጉት መንገድ አበላሽተዋቸው ሱሰኛ፣ ሺሻ የሚያጨስ፣ በወጣትነቱ የሚገድል የሚደበድብ እናት አባቱም የማያከብር እንዲሆም አድርገዋል፡፡ አሁን የእኛ ነው የቀራቸው እኛንም ልጆቻችንን በፊልማቸው በአሻንጉሊት ትዕይንታቸው እያደነዘዙን እያፈዘዙን ነው፡፡
እባካችሁ ጨቅላ ሕፃናቶቻችንን በልጅነታቸው የአምልኮ፣የጾም፣የጸሎት፣የስግደት ሥርዓት እያስተማርን አሳድገን ከአጋንንት ምርኮ እንታደጋቸው፡፡
‹‹ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቶአል›› ት.ሆሴ 4÷6
‹‹ከትውልዱ ማን አስተዋለ?›› ት.ኢሳ 53÷8
ክፍል ሠላሳ አምስት
በጸሎት የራቀን ዲያብስ፣ ወደ እኛ መመለስ
https://www.facebook.com/memehirhenok