Wednesday, July 1, 2015

ገድለ ቅዱሳን

ግንቦት 19 ዕለት ታስበው የሚውሉ 6 ታላላቅ ዓመታዊ በዓላት አሉ፡፡
፩. ጌታችን 5 ጊዜ ከሞት እያስነሣውና ስለ ስሙ ምስክር የሆነለት የ12 ዓመቱ ሕጻን የቅዱስ ኤስድሮስ ዕረፍት ነው
፪. በወሎ ላስታ ሰውንና ዝንጀሮን በቃልኪዳን ያስተሳሰሩት እና እመቤታችን ዕጣን እየሰጠቻቸው ከ24ቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥላሴን መንበር ያጠኑት የአቡነ ዮሴፍ ዘእጂፋት ዕረፍት ነው
፫. ዳግመኛም ጌታችን ነገልጦ ‹‹ለእናቴ ዓሥራት የሰጠኋት፣ ለወዳጄ ለጊዮርጊስ፣ ለባለሟሌ ለገብረ መንፈስ ቅዱስ ዓሥራት የሰጠኋት ይህችን ቅድስት ሀገር ያሬድንና ጊዮርጊስን ያፈራችውን ኢትዮጵያን በጸሎትህ ጠብቅ›› ብሎ ያዘዛቸው የአቡነ ዮሴፍ ዘአክሱም ዕረፍት ነው
፬. ስመ እግዚአብሔር ሲጠራባቸው ስለ ስሙ ሲሉ ራሳቸውን ለሞት አሳልፈው የሰጡት በጸሎታቸውም ውኃውን ደም ያደረጉት የአቡነ ዓቢየ እግዚእ ዕረፍት ነው
፭. ጸሎታቸውን ሲጀምሩ ሰማያት ተከፍተው የመላእክትን አገልግሎት በግልጽ የሚያዩት እና ሰይጣን ለመጀመሪያ ጊዜ ከጳውሎስ ሳምሳጢን ጀምሮ እስከ ንስጥሮስንና ልዮን ድረስ ያስተማራትን የክህደት ት/ት ከሀገራችን ያጠፉልን የአቡነ ብስጣውሮስ ዘሐይቅ ዕረፍት ነው
፮. ዳግመኛም ቤተ መቅደሱን በባሕር ላይ የሠራውና በምድራዊ ስንዴና ወይን ያይደለ መላእክት ሰማያዊ ኅብስትና ጽዋ እያመጡለት 22 ዓመት ሥጋ ወደሙን ሰፈትት የኖረው የጻድቁ ንጉሥና ካህን የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ልደት ነው፡፡ 

የእነዚህን ቅዱሳን የሁሉንም ሙሉ ገድላቸውን በዝርዝር በደንብ እንመለከታለን በእርጋታ ሆናችሁ በተመስጦ አንብቡት፡፡ መልካም የበረከት ንባብ ይሁንልን!!! 

የጽሑፉ ምንጮች፡-
፩. ገድለ አቡነ ብስጣውሮስ ዘሐይቅ
፪. ገድለ አቡነ ዓቢየ እግዚእ
፫. ገድለ ቅዱስ ላሊበላ
፬. ገድለ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ
፭. ገድለ ቅዱስ ቂርቆስ ወኢየሉጣ
፮. ስንክሳር ዘወርሃ ግንቦት
፯. የቅዱሳን ታሪክ-107፣140
፰. መዝገበ ታሪክ ናቸው፡፡

ሕጻኑ ሰማዕት ቅዱስ ኤስድሮስ፡- ሀገሩ እስክንድርያ ሲሆን አባቱ በድላዖን እናቱ ሶፍያ ከቤተ መንግሥት ወገኖች ናቸው፡፡ አባቱ የዲዮቅልጥያኖስ መኰንን ነበር፡፡ ከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ በክርስቲያኖች ላይ እጅግ አሠቃቂ መከራ ባደረሰ ጊዜ አባቱ በድላዖን ምስፍናውን ትቶ ሚስቱንና ልጆቹን ይዞ ገዳም ገባ፡፡ ዲዮቅልጥያኖስም ጭፍሮቹን ልኮ አስመጣውና እምነቱን እንዲክድ ጠየቀው፡፡ በድላዖንም ‹‹ክርስቶስን በተውከው ሰዓት እኔም አንተን ተውኩህ›› አለው፡፡ ወዲያም አንገቱን በሰይፍ አስቆረጠው፡፡ ቅዱስ ኤስድሮስ የ12 ዓመት ሕፃን ልጅ ነበርና ይመለስ ይሆናል በሚል በእሥር ቤት እንዲቆይ ተደረገ፡፡ በማግሥቱም ‹‹ክርስትናህን ትተህ የንጉሡን ሃይማኖት ተቀበል›› ብለው ሲያባብሉት እምቢ ቢላቸው በንጉሡ ፊት አቅርበው ደሙ እንደ ውኃ እስኪወርድ ድረስ አሠቃቂ ግርፋትን ገረፉት፡፡ እናቱ ሶፍያም የሕፃኑን ልጇን ደም በዲዮቅልጥያኖስ ፊት ላይ እረጭታ እረገመችው፡፡ ዲዮቅልጥያኖስም በንዴት ከሴት ልጇ ጋር ከወገባቸው ላይ ከሁለት አስቆረጣቸውና ሰማዕትነታቸውን ፈጸሙ፡፡
ቅዱስ ኤስድሮስም ተሰቅሎ ሳለ በእናቱና በእኅቱ የሆነውን ነገር ይመለከት ነበር፡፡ ሆዱን ሰንጥቀው በመቅደድ አንጀቱን አውጥተው ወስደው በተራራ ላይ ጣሉት፡፡ ጌታችንም ከሞት አሥተነስቶት እንደ ቀድሞው ሕያውና ፍጹም ጤነኛ አደረገው፡፡ ኤስድሮስም ተመልሶ ሄዶ ከከሃዲው ንጉሥ ፊት ቆመ፡፡ አሁንም በብረት አልጋ ላይ አስተኝተው ከሥር እሳት አነደዱበት፡፡ ሁለተኛም በብረት ላይ አስተኝተው ፈጩት፡፡ ጌታችንም አስነሣው፡፡ ብዙዎችም በኤስድሮስ አምላክ አመኑ፡፡ ዳግመኛም በእርሱ አምላክ ካመኑት ከ800 ነፍሳት ጋር ሰቀሉት፡፡ አሁን ጌታችን አድኖ አሥነሳው፡፡ በሥቃይም ብዛት አልሞት ቢላቸው አንገቱን በሰይፍ ቆረጡት ነገር ግን አሁንም ለ3ኛ ጊዜ ከሞት አሥነሣው፡፡
ትልቅ ድንጋይ በአንገቱ ላይ አስረው ወደ ባሕር ጣሉት፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም ከባሕሩ ውስጥ አውጥቶ በንጉሡ ፊት አቆመው፡፡ ዳግመኛም ወደ ከተማም ወስዶ ሰቅሎ ገደለው፣ ጌታችንም ለ4 ጊዜ አሥነሣው፡፡ ለተራቡ አንበሶች ሲሰጡት እነርሱም ምንም ሳይነኩት ቀሩ ይልቁንም አክብረው ሲሰግዱለት ቢመለከቱ በንዴት ሰውነቱን ቆራርጠው ወደ ባሕር ጣሉት፡፡ ጌታችንም ከቅዱስ ሚካኤልና ከቅዱስ ገብርኤል ጋር ተገልጦለት ለ5ኛ ጊዜ ከሞት አሥነሣው፡፡ ንጉሡም እጅግ አፈረና የሚያደርገው ቢያጣ በግዞት ወደ ሰሎንቅያ ሀገር ላከው፡፡ በዚያም ብዙ ካሠቃዩት በኋላ ወደ ንጉሡ መለሱት፡፡ ንጉሡም በእሥር ቤት በርሀብ እንዲሠቃይ አደረገው፡፡ በመጨረሻም ቅዱስ ኤስድሮስ ግንቦት 19 ቀን የሰማዕትነት ፍጻሜው ሆነና ተሰቅሎ ዐረፈ፡፡ የኖረበት ዘመን 12 ዓመት ነው፡፡ በቅዱስ ኤስድሮስ ምክንያት በጌታችን አምነው ከኤስድሮስ ጋር አብረው በሰማዕትነት የሞቱት ሰዎች ብዛት ከ8 መቶ ሺህ በላይ ናቸው፡፡ ጌታችን ለሕፃኑ ሰማዕት ለቅዱስ ኤስድሮስ አስደናቂ ቃል ኪዳን ገብቶለታል፡፡
አቡነ ዮሴፍ ዘእንጂፋት፡- ተአምረኛው ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ዮሴፍ ዘእንጂፋት አባታቸው ንጉሡ ዐፄ ዳዊት እናታቸው ዳግም ሞገሳ ይባላሉ፡፡ ትውልድ ሀገራቸው ወሎ መቄት እንጂፋ ነው፡፡ ሲወለዱ በርካታ ሙታን ተነሥተዋል፡፡ ጻድቁ ያላዩት የቅዱሳን ቦታ ያልተሳለሙት ገዳም የለም፡፡ በወሎ ላስታ ሰውንና ዝንጀሮን በቃልኪዳን ያስተሳሰሩ ታላቅ አባት ናቸው፡፡
ከዕለታት በአንዱ ቀን ዝንጀሮዎቹ ተሰብስበው መጥተው እጅ ነሷቸው፡፡ አቡነ ዮሴፍም ጌታችንን ‹‹ምን አበላቸዋለሁ?›› ብለው በጸሎት ጠየቁ፡፡ ጌታችንም ‹‹አንተን ያጅቡ፣ ቅጠሉን ቃርሚያውን ይብሉ›› ብሎ አዘዛቸው፡፡ ዝንጀሮዎቹም ጻድቁን ተከትለው ይጓዙ ጀመር፡፡ አንድ ቀን በመንገድ አብረው ሲሄዱ ዝንጀሮዎቹ ‹‹ራበን›› ብለው ለአባታቸን ቢነግሯቸው ድንጋዩን በጸሎታቸው ባርከው ምግባቸው አድርገው መግበዋቸዋል፡፡ አሁንም ድረስ ላስታ ውስጥ በሚገኘው በጻድቁ ገዳም አካባቢ እህሉ በሚትረፈረፍበት ቦታ ዝንጀሮዎች በብዛት ይገኛሉ፡፡ ዝንጀሮዎቹ የሰውን እህል እንዳይበሉ፣ ገበሬውም ቃርሚያውን እንዳያነሳ በአቡነ ዮሴፍ ቃልኪዳንና ግዝት ተይዘዋል፡፡ በዚህም መሠረት አሁንም ድረስ ዝንጀሮዎቹም የሰውን እህል አይበሉም፣ ገበሬውም ቃርሚያውን አያነሳም፡፡ ገበሬው ቃርሚያውን ቢያነሳ ግን ዝንጀሮዎቹ የእሱን እህል ብቻ ለይተው ይበሉበታል፡፡
በአካባቢው አደገኛና መርዛማ እባቦች በብዛት ቢኖሩም በጻድቁ የገዳሙ ክልል ውስጥ ግን በፍጹም ሰውን አይነኩም፡፡ አቡነ ዮሴፍ ለ40 ቀን ከሰው ጋር ሳይገናኙ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም በደመና እየተመላለሱ ጸሎት ያደርጉ ነበር፡፡ አባታችን የተለያዩ ተአምራትን እያደረጉ ባሕር ከፍለው እየተሻገሩ ሙታንን እያስነሱ ወንጌልን ዞረው አስተምረዋል፡፡ ወደ ሰማይም ተነጥቀው እመቤታችን ዕጣን ሰጥታቸው ከ24ቱ ካህናት ጋር አጥነዋል፡፡ ጻድቁ ያመነኮሷቸው መነኮሳት በጣም በርካታ ናቸው፡፡ አቡነ ዮሴፍ ከብዙ ተጋድሏቸው በኋላ ቃልኪዳን ተቀብለው በመጨረሻ ግንቦት 19 ቀን በክብር ዐርፈው በዚያው በገዳማቸው ተቀብረዋል፡፡
አቡነ ዮሴፍ ዘአክሱም፡- የአቡነ ዮሴፍ ዘአክሱም ልደታቸውና ዕረፍታቸው በተመሳሳይ ግንቦት 19 ቀን ነው፡፡ ልጅ ሆነው እየተጫወቱ ሳለ መልአክ መጥቶ ለወላጆቻቸው የዓለም ሰው እንዳልሆነ ስለነገራቸው ወስደው ለሊቀ ጳጳሱ ሰጧቸው፡፡ በአክሱም ሲማሩ አድገው በ22 ዓመታቸው መንኩሰዋል፡፡ አንጋፋ ከተባሉት የኢትዮጵያ ቅዱሳን አንዱና ዋነኛው ናቸው፡፡
ጻድቁ በጸሎት ላይ እንዳሉ ጌታችን ተገልጦላቸው እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹ትወደኛለህን?›› ብሎ ሲጠይቃቸው ‹‹ጌታዬ ባለወድህማ ኖሮ መች ዓለምን ንቄ እከተልህና ገዳም እገባ ነበር›› አሉት፡፡ ቀጥሎም ጌታችን ‹‹ከወደድከኝስ ለእናቴ ዓሥራት የሰጠኋት፣ ለወዳጄ ለጊዮርጊስ ዓሥራት የሰጠኋት፣ ለባለሟሌ ለገብረ መንፈስ ቅዱስ ዓሥራት የሰጠኋት ይህችን ቅድስት ሀገር ያሬድንና ጊዮርጊስን ያፈራችውን ኢትዮጵያን ጠብቅ›› ብሏቸው ተሰወረ፡፡ ጻድቁም ጌታችን ይህን ከነገራቸው በኋላ እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ ስለ ሀገራችን ቆመው ጸልየዋል፡፡ ሸዋ ቡልጋ ፈጠጋር ውስጥ ለሚገኙት ወንድማቸው ለታላቁ ጻድቅ ለአቡነ ዘካርያስም ስለ ኢትዮጵያ አብዝተው እንዲጸልዩ መልእክት ስለላኩባቸው አቡነ ዘካርያስም ዕድሜ ልካቸውን የጸለዩአት ጸሎት ‹‹የኢትዮጵያን ሕዝብ ማር›› የምትል ነበረች፡፡ የአቡነ ዘካርያስ ገዳም ቡልጋ ውስጥ ይገኛል፡፡ አቡነ ዮሴፍ ዘአክሱም የሀገራችንን ሊቃውንትና ሕዝቡንም ለብቻ ሰብስበው የሮማውያን የሀሰት ትምህርት ነፍስን ለሲኦል የሚዳርግ ፍጹም ክህደት መሆኑን አጥብቀው አስተምረዋል፡፡ ጻድቁ በአንድ ወቅት ርሀብ በሆነ ጊዜ የገዳሙን ድንጋዮች ባርከው ዳቦ አድርገው ሕዝቡን የመገቡ ታላቅ አባት ናቸው፡፡
አቡነ ብስጣውሮስ ዘሐይቅ፡- ሙሉ ስማቸው ዓቃቤ ሰዓት አቡነ ብስጣውሮስ ተብለው የሚጠሩ ሲሆን የትውልድ ሀገራቸው መቅደላ ነው፡፡ አባታቸው ፍተ ድንግል እናታቸው ጽዮን ሞገሳ የሚባሉ ደጋግ ቅዱሳን ናቸው፡፡ አቡነ ብስጣውሮስ በ17ኛው ምእት ዓመት የነበሩ ታላቅ ጻድቅ ሲሆኑ የታላቁና የጥንታዊው ትምህርት ቤትና የሥርዓተ ገዳም ተቋም የደብረ ሐይቅ ቅዱስ እስጢፋኖስ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ገዳም አበምኔት ነበሩ፡፡ በልጅነታቸው ትምህርት ቤት ገብተው የሐዋርያትን ሥርዓትና የቅዱሳት መጻሕፍትን ትርጓሜ በሚገባ ተምረዋል፡፡
በዘመናቸው የሃይማኖት ስደት ስለነበር አባታቸው ፍተ ድንግል ስለ ሃይማኖታቸው በዐላውያን ሰማዕት ሆነው ሲገደሉ አቡነ ብስጣውሮስ የአባታቸውን ዐፅም ይዘው በመሸሽ ወደ ላስታ ሄደው በእመቤታችን ስም በተሠራች ገዳም በደብረ ዠመዶ ወስደው ቀበሯቸው፡፡ በኋላ በዐፄ ፋሲል ዘመን ሃይማኖት ሲመለስ ዐፅማቸውን አፍልሰው አምጥተው አገራቸው ቀብረዋቸዋል፡፡ ከዚህም በኋላ እናታቸው በግድ ሚስት አጭተውላቸው የነበረ ቢሆንም ብዙ ሳይቆዩ ሚስታቸው ስለሞተች ቀድሞም የተመኙትን የምንኩስና ሕይወት ለመኖር ወኑ፡፡ አንድ ቀን አንዱ የደብረ ሐይቅ መነኩሴ የገዳሙን ምርት ገበያ ለመሸጥ ይዘው እንደሄዱ አንድ ቀማኛ ወንበዴ አግኝቶ ሊቀማቸው ሲል አቡነ ብስጣውሮስ ደርሰው አዳኑት፡፡ መነኩሴውንም ወደ ቤታቸው ወስደው በመልካም መስተንግዶ አሳደሯቸው፡፡ መነኩሴውም በዚያች ሌሊት ስለ አቡነ ብስጣውሮስ ብዙ ነገር ከተመለከቱ በኋላ አቡነ ብስጣውሮስን ስለ ምንኩስና አስተማሯቸው፡፡ መነኩሴው በማግስቱ ሲሄዱ ወደ ሐይቅ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ገዳም መጥተው እንዲጎበኟቸውና እንዲባረኩ ነግረዋቸው ሄዱ፡፡ አቡነ ብስጣውሮስም እግዚአብሔር መንገዳቸውን ይመራቸው ዘንድ ብዙ ከጸለዩ በኋላ ወደ ሐይቅ ገዳም ገቡ፡፡ በገበያ ያገኘውና በቤቱ ያሳደረውም መነኩሴ ሲያያቸው ደስ ተሰኝነቶ የገዳሙ አበምኔት ዓቃቤ ሰዓት አባ ዘወልደ ክርስቶስ ዘንድ ወሰዳቸው፡፡ አበምነቱም አቡነ ብስጣውሮስን ገና እንዳዩአቸው ጸጋ እግዚአብሔር እንዳደረባቸው አይተው በጣም ደስ ተሰኙ፡፡ አቡነ ብስጣውሮስም መመንኮስ እንደሚፈልጉ ለአበምኔቱ ሲነግሯቸው አበምኔቱ ‹‹የምንኩስና ሥራ ቀላል አይምሰልህ፣ ብዙዎች ወደ እኛ መጡ ነገር ግን መታገስ ተስኗቸዋል…›› በማለት የምንኩስና ሕይወት ከባድ ፈተና እንዳለበት ነገሯቸው፡፡ የእግዚአብሔር ሰው ብስጣውሮስም ‹‹በልዩ ልዩ ዓይነት ፈተናዎች ፈትኑኝና ሥራዬን ካዩ በኋላ ያመነኩሱኛል›› አሏቸው፡፡ ከዚህም በኋላ አቡነ ብስጣውሮስ በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደት እየተጋደሉ ገዳሙን በጉልበት ሥራ ብዙ ካገለገሉ በኋላ ከገዳሙ አበምኔት ከዓቃቤ ሰዓት አባ ዘወልደ ክርስቶስ እጅ ምንኩስናን ተቀበሉ፡፡ ተጋድሎአቸውንም ከበፊቱ ይበልጥ በማብዛት መኖር ጀመሩ፡፡
እናታቸው የልጃቸውን መመንኮስ ሰምተው ወደ ሐይቅ መጡ ነገር ግን አቡነ ብስጣውሮስ እናታቸውን ወጥተው ላለማየት ተሠወሩ፡፡ አበምኔቱም በብዙ ፍለጋ አግኘተዋቸው ‹‹ልጄ እናትህ አንተን ለማየት ከሩቅ ሀገር መጥታለችና ሄደህ አግኛት›› ሲሏቸው አቡነ ብስጣውሮስም ‹‹አባቴ ሆይ ጌታችን በወንጌል ያለውን አያስታውሱምን? ‹እነሆ እናትና ወንድሞችህ በውጭ ቆመዋል ባሉት ጊዜ ጌታችን በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ ከሚፈጽም በቀር እናቴ ማን ናት? ወንድሞቼስ እነማን ናቸው?› ብሎ ተናግሮ የለምን? ስለዚህ ወደ እናቴ አልሄድም›› ብለው ለአበምኔቱ መለሱላቸው፡፡ አበምንቱም ‹‹ከመንገዱ ርቀት የተነሣ እናትህ በብዙ ድካም መጥታለችና ልታያት ይገባል›› ብለው ግድ አሏቸው፡፡ አቡነ ብስጣውሮስም ሄደው እናታቸውን ካገኟቸው በኋላ እናታቸውም በዛው መንኩሰው በባሕሩ ዙሪያ ካለው ከሴቶች ገዳም ገብተው ማገልገል ጀመሩ፡፡
አቡነ ብስጣውሮስ ከመልካም የጉልበት ሥራ ጋር ቀን ቀን የዳዊትን መዝመር፣ የነቢያትን መጻሕፍትና መኅልየ መኅልይን ሲደግሙ ይውላሉ ሌሊት ሌሊት ሐይቁ ውስጥ ገብተው እጅግ አብዝተው ሲጸልዩ የብርሃን ዓምድ ተተክሎ ይታይ ነበር፡፡ ጸሎታቸውንም ሲጀምሩ ሰማያት ይከፈቱ ነበር፡፡ ቅዱሳን መላእክትንም ሲወጡ ሲወርዱ ያዩአቸዋል፡፡ አቡነ ብስጣውሮስ በእንደዚህ ዓይነቱ ተጋድሎ ብዙ ሲያገለግሉ ዜና ትሩፋታቸው በሁሉ ዘንድ በዓለም ተሰማ፡፡ አስተዳዳሪው ዓቃቤ ሰዓቱ አቡነ ዘወልደ ክርስቶስም እርጅና ሲጫናቸው ማኅበሩን ሰብስበው ‹‹በእኔ ቦታ አባት የሚሆናችሁን ምረጡ›› አሏቸው፡፡ እነርሱም ‹‹እግዚአብሔር ያመለከተህን አንተ ሹምልን›› አሏቸው፡፡ አባ ዘወልደ ክርስቶስም በጸሎት ከጠየቁ በኋላ ‹‹እግዚአብሔርና እኔ አባት ይሆኑላችሁ ዘንድ አቡነ ብስጣውሮስን መርጠንላችኋል›› አሏቸው፡፡ ቀጥሎ አበምኔቱ ስለ አቡነ ብስጣውሮስ እንዲህ በማለት ትንቢት ተናገሩ፡- ‹‹እርሱ ሃይማኖቱ የቀና ምግባሩ ያማረ በተጋድሎም የጸና በጸሎቱ ሀገርን ይጠብቃል፣ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን በነገሥታቱና በመኳንንቱ ፊት ያደርጋል›› እያሉ ለማኅበሩ በነገሯቸው ጊዜ እጅግ ደስ ተሰኙ፡፡ አቡነ ብስጣውሮስ ግን ይህን ሲሰሙ የመረረ ልቅሶን አለቀሱ፤ ከእነርሱም ዘንድ ይሸሹ ዘንድ ወጥተው በመርከብ ተጭነው ሄዱ፡፡ ነገር ግን ደርሰው ይዘው በእግዚአብሔር ፈቃድ ይሾሟቸው ዘንድ ይዘው አሰሯቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ከሰማይ ‹‹ብስጣውሮስ የአባትህን የአበምኔቱን ቃል አታስተሐቅር›› የሚል ቃል ተሰማ፡፡ ማኅበሩም ይህንን ከሰማይ የመጣውን ቃል በሰሙ ጊዜ እጅግ ተደስተው እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ ከዚህም በኋላ አቡነ ብስጣውሮስን እንደ ሕጋቸውና እንደ ሥርዓታቸው የሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም አበምኔትና ዓቃቤ ሰዓት በማድረግ ሾሟቸው፡፡
አቡነ ብስጣውሮስም በአቡነ ኢየሱስ ሞዐ ወንበር በተቀመጡ ጊዜ የተሰወረውን ሁሉ የሚያዩ ሆኑ፡፡ ፊታቸውም እንደ ጨረቃ የሚያበራበት ጊዜ ነበር፣ ለአገልግሎትም ወደ ቤተ መቅደስ በገባ ጊዜ ቅዱሳን መላእክት ክንፋቸውን እየጋረዱ ይቀበሉት ነበር፡፡ ጻድቁ ጸሎተ ዕጣን ሲያሳርጉ እያለቅሱ ነበር፤ የጌታችንን መከራ እያሰቡ ሰውነታቸውን በድብቅ ይገርፋሉ፤ ድኆችንና ጦም አዳሪዎችን ሁሉ የሚንከባከቧቸው አባት ሆኗቸው፡፡ ገዳሙንም አፍርሰው ሊዘርፉ የመጡትን ወራሪዎች አባታችን ወደ መቅደስ እየገቡ በጸሎት እያሰሯቸው አሳፍረው ይመልሷቸው ነበር፡፡ አቡነ ብስጣውሮስ በእንዲህ ዓይነት ተጋድሎ ገዳሙንና ሀገራችንን እየጠበቁ ሲኖሩ በመሀል የቅብዐት እምነት ነገር በገዳሙ ተነሣ፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችንን አምላካችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ‹‹ከትስብእት ጋር ከተዋሐደ በኋላ መንፈስ ቅዱስ ተቀባ፣ በዚህም ቅብዐት በጸጋ ልጅ፣ ንጉሥም፣ ነቢይም፣ ሊቀ ካህናትም ተባለ›› የሚሉ ከሃዲያን ተነሡና የእግዚአብሔር ሰው ብፁዕ አባታችን ብስጣውሮስ ይህንን የክሕደት ትምህርት ሰምተው እጅግ እያዘኑና እያለቀሱ የካዱትን ሰዎች በብዙ ምሳሌ እያደረጉ ማስተማር ጀመሩ፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመንፈስ ቅዱስ ቅብዐት በጸጋ ልጅ እንዳልሆነ፣ ነገር ግን በባሕርይው የአብ ልጅ እንደሆነ፣ እርሱ ራሱ ቅብ፣ እርሱም ራሱ ቀቢ፣ እርሱ ራሱ ተቀቢ እንደሆነ በብዙ ምሳሌ እያደረጉ የቀደሙ የአባቶቻችንንም ትምህርት ሁሉ እየጠቀሱ አስተማሯቸው፡፡ ነገር ግን ሰይጣን አንድጊዜ አስክዷቸዋልና አንዳንዶቹ እምቢ አሏቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ሐዋርያት ከመሠረቷት አንዲት ቤተ ክርስቲያን አውግዘው ለዩአቸው፤ ቤተ ክርስቲያንም ሰላም ሆነች፡፡ በዚህም አባታችን ከሃድያንን የሚዘልፉ ዳግማዊ ቄርሎስ ተባሉ፡፡ ይህም ክህደት መጀመሪያ ሰይጣን ለጳውሎስ ሳምሳጢን ያስተማረው ነው፡፡ ጳውሎስ ሳምሳጢን በገዳም ቅጠል እየበላ የሚኖር ተሐራሚ መናኝ ነበር፡፡ በጾም በጸሎት ሲኖር ሰይጣን ራሱን ሰውሮ መጥቶ ተገለጠለትና ‹‹ጸሎትህ በእግዚአብሔር ዘንድ ተሰምቶልሃል፤ ነገር ግን አምላክ ያለሩካቤ በድንግልና የተወለደ አይምሰልህ በሩካቤ ተወለደ እንጂ፤ ይህም ልጅ ደግ ሰው ሆነ፣ በ30 ዘመኑ በዮሐንስ እጅ በዮርዳኖስ ተጠመቀ፣ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል በራ ላይ ተቀመጠ፣ ያን ጊዜም ይህ ሰው በጸጋ የሥላሴ ልጅ ሆነ›› ብሎ አስተማረው፡፡ ጳውሎስ ሳምሰጢንም ሰይጣን የነገረውን ነገር በልቡ አምኖ ለደቀ መዝሙሩ ለተያስሮስ አስተማረው፡፡ ተያስሮስም ለድያድርስ አስተማረው፡፡ ድያድርስም ለንስጥሮስ አስተማረው፡፡ ንስጥሮስም ለስም አጠራሩ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችንን አምላካችንን ‹‹መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ዕሩቅ ብእሲ ነው›› ብሎ ለልዮንና ለመርቅያን አስተማራቸው፡፡
ንስጥሮስ ይህን አዲስ የክህደት ትምህርት እንዳመጣ በሰሙ ጊዜ 200 ኤጲስ ቆጶሳት በቅዱስ ቄርሎስ ዘእስክንድርያ መሪነት በኤፌሶን ተሰብስበው ሲያስተማሩት እምቢ ቢላቸው አውግዘው ለዩት፡፡ ንስጥሮስም ሰውነቱ መግሎ ክፉ አሟሟት ሞተ፡፡ በኋላም መርቅያን ሲነገሠና ልዩንም የሮም ሊቀ ጳጳስ ሲሆን ሁለቱም አባታቸው ንስጥሮስ ያስተማራቸውን ሃይማኖት ማስፋፋት ቻሉ፡፡ እነ ልዮንም ንስጥሮስ በተወገዘበት ጉባዔ ላይ የነበሩትና አሁን ለሥጋቸው የፈሩ አባቶችን ይዘው ከንስጥሮስ ክህደትና ከቅዱስ ቄርሎስ ትምህርት አወጣጥተው የራሳቸውን የረከሰ ሃይማኖታዊ ድንጋጌ አወጡ፡፡ ‹‹ክርስቶስ ሁለት አካል ነው፣ አንዱ የማርያም ልጅ አንዱ የእግዚአብሔር ልጅ በመቀራረብ አንድ ሆኑ ያለውን አውጥተው ከቅዱስ ቄርሎስም ቃልና ከንስጥሮስ ክህደት ቀላቅለው መለኮት የመለኮትን ሥራ ይሠራል፣ ትስብእትም የትስብእትን ሥራ ይሠራል፤ በሁለት መንገድ አንዱ ተአምራትን ያደርጋል ሁለተኛው መከራን ይቀበላል ስለዚህም ትስብእት ከመለኮት ያንሳል›› ብለው ጻፉ፡፡ ይህንንም የክህደት ጽሕፈታቸውን ለቅዱስ ዲዮስቆሮስ ላኩለት፡፡ እርሱም ሄዶ ከክህደታቸው እንዲመለሱ አስተማራቸው፡፡ ‹‹በአንዱ ክርስቶስ ላይ ለምን የሁለትነት ነገር ትናገራላች? ወደ ሠርግ ቤት ተጠርቶ የሄደው ውኃውንም የወይን ጠጅ ያደረገው እርሱ አንዱ ክርስቶስ ነው…›› እያለ በብዙ ምሳሌ ካስተማራቸው በኋላ ልዮንንና መርቅያን የጻፉትን የክህደት ጽሕፈት በፊታቸው ቀደደው፡፡ እነርሱ ግን አንድ ጊዜ ክደዋልና የቅዱስ ዲዮስቆሮስን ፂሙን ነጭተው ጥርሱን አውልቀው ብዙ አሠቃዩት፡፡ እርሱም የነጩትን ፂሙንና ያወለቁትን ጥርሱን ሰብስቦ ‹‹እነሆ የሃይማኖቴን ፍሬ ተቀበሉ›› ብሎ ለእስክንድርያ ክርስቲያኖች ላከላቸው፡፡ ከሃዲያኑም ወደ ጋግራ ደሴት አጋዙትና በዚያው ዐረፈ፡፡
ሰይጣን ለመጀመሪያ ጊዜ ለጳውሎስ ሳምሳጢን ያስተማራትን ያችን ክህደት በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ሰይጣን የሚያድርባቸው ሰዎች እየተቀባበሏት እስከ ንስጥሮስንና እስከ ልዮን ድረስ ከደረሰች በኋላ የልዮን ልጅ በሆነው በአውፍንስ አማካኝነት በዐፄ ሱስንዮስ ዘመን ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሀገራችን ኢትዮጵያ ገባች፡፡ አውፍንስም ክህደቱን ለሁለት የሀገራችንን መነኮሳት አስተማራቸው፡፡ ለአንደኛው ‹‹ወልድ ሦስት ልደት አለው፣ በመጀመሪያ ከአብ ተወለደ ዳግመኛም በመንፈስ ቅዱስ ሥጋ ከድንግል ተወለደ ሦስተኛም በቤቴልሔም ተወለደ›› ብሎ ካስተማረውና ካስካደው በኋላ ስሙን ‹‹ተክለ ሃይማኖት›› ብሎ ጠራው፡፡ ሁለተኛውንም መነኩሴ ለብቻው ጠርቶት ‹‹ልጄ ሆይ ስማኝ ልብ አድገህም ዕወቅ፣ ወልድ በመንፈስ ቅዱስ ቅብዐት የከበረ ነው፣ ይኸውም ሳይዋሃድ ማደር ነው›› ብሎ ካስተማረውና ካስካደው በኋላ ስሙን ‹‹ኤዎስጣቴዎስ›› ብሎ ጠራው፡፡ እነዚህም የካዱ ሁለቱ መነኮሳት በየሀገሩና በየአውራጃው እየዞሩ ሀገራችን ኢትዮጵያን በክህደት ትምህርታቸው አጥፍተዋት ነበር፤ ነገር ግን ብዙ ቅዱሳን አባቶቻችንና እናቶቻችን ይህን ክህደት በትምህርታቸውና በተአምራታቸው እንዲገታ አድርገውታል፡፡ አቡነ ብስጣውሮስም እነዚያን ከሃዲዎች አውግዘው ለዩአቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ከሃዲያኑ አባታችንን ከሰሷቸውና ከጎንደሩ ንጉሥ ጋር አጣሏቸው፡፡ ንጉሡም የእነዚያን ካሃዲዎች እምነት አምኖ ተቀብሎ ነበርና አባታችንን ወደ ጎንደር እንዲያመጧቸው ጭፍሮቹን ላከ፡፡ አቡነ ብስጣውሮስም ነገሩን አውቀው ስለ ቀናች ሃይማኖት ይመሰክሩ ዘንድ አንደበት እንዲሆናቸው ጌታችንን በጸሎት ሲጠይቁ ጌታችንም ‹‹ልጄ ብስጣውሮስ ሆይ አይዞህ እኔ ከአንተ ጋር ነኝ፣ እኔ ስለመሠረትኳት አንዲት ሃይማኖት ጽና›› አላቸው፡፡ አባታችንም ወደ ንጉሡ ዘንድ ሄዱና ንጉሡ ሰዎቹን ስለማውገዙ ጠየቃቸው፡፡ አባታችንም ንጉሡን ስለ ቀናች ሃይማኖት እየመሰከሩለት አስተማሩት፡፡ ንጉሡም በብዙ ስጦታና ሽንገላ ሊያታልላቸው ሞከረ ነገር ግን አባታችን አጥብቀው ተቃወሙት፡፡ ንጉሡም ዕውቀታቸውንና ጽናታቸውን ባየ ጊዜ አባታችንን በእግር ብረት አሳስሮ አሥር ቤት ውስጥ ጣላቸው፡፡ በዚህም ጊዜ የእግር ብረቱ እንደሰም ቀልጠ፡፡ ወታደሮቹም ይህንን ተአምር አይተው ፈርተው ሄደው ለንጉሡ ነገሩት፡፡ ንጉሡም ሰምቶ ደነገጠ፤ እየፈራና እየተንቀጠቀጠ ወደ አባታችን መጥቶ ሰገደና ‹‹አባቴ ሆይ ይቅር በሉኝ የሃይማኖትንም ነገር እንደገና አስተምሩኝ›› አላቸው፡፡ እሳቸውም አስተምረው ባረኩት፡፡ በመከራቸውም ታግሰው ለልጆቻቸውና ለእኛም የሐዋርያትን ሃይማኖት አጸኑልን፡፡ ዕድሜአቸውም 90 ዓመት በሆነው ጊዜ ዕረፍታቸው እንደደረሰ ዐውቀው የቀናች ሃይማኖት በሀገራችን ለዘለዓለም ጸንታ ትኖር ዘንድ ጌታችንን አጥብቀው ለመኑት፡፡ ጌታችንም በደሙ የመሠረታት የቀናች ሃይማኖት በሀገራችን ጸንታ እንደምትኖርና ሌላም የምሕረት ቃልኪዳን ከገባላቸው በኋላ ግንቦት 19 ዐረፉ፡፡
በዚያችም ዕለት ሐይቅ አለቀሰች፤ የሐይቅም ባሕር ሦስት ዓመት በኃይል ስትታወክ አቡነ አላኒቆስ ይህ ሁሉ የሆነው ስለ አባታችን ስለ ብስጣውሮስ ማረፍ መሆኑን ዐውቀው ወደ ንጉሡ ሄደው የአባታችንን ዐፅም እንዲሰጣቸው ጠየቁት፡፡ ንጉሡ ግን ‹‹በረድኤታቸው ይጠብቁኛልና አልሰጥም›› አላቸው፡፡ ንጉሡ ስለከለከላቸው አቡነ አላኒቆስም ቁስቋም ወደምትባል በወርቅና በከበረ ዕንቁ ወደተሸለመች ወደ እመቤታችን ቤተ ክርስቲያን ሄደው በእመቤታችን ሥዕል ሥር ወድቀው አለቀሱ፡፡ ሥዕሏም በሰው አንደበት አናግራ ካጽናናቻቸው በኋላ የአባታችን ዐፅም ከመሠዊያው በስተቀኝ በኩል እንደሚገኝ ነገረቻቸው፡፡ አቡነ አላኒቆስም ዐፅማቸውን አፍልሰው ወደ ሐይቅ በተመለሱ ጊዜ የመዓዛው ሽታ የንጉሡን አገር ሁሉ መላው፤ መቃብሩ በነበረበት ቦታም የብርሃን ዓምድ ተተክሎ ታየ፡፡ ንጉሡም መነኩሴው የአባታችንን ዐፅም እንደወሰዱ ባወቀ ጊዜ መነኩሴውን ይዘው ከአባታችን ዐፅም ጋር ያመጡለት ዘንድ ብዙ ፈረሰኛ ወታደሮቹን ላካቸው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር በጥበቡ ሰውሯቸዋልና አቡነ አላኒቆስን ሊያገኟቸው አልቻሉም፡፡ አቡነ አላኒቆስም የቅዱስ አባታችንን ዐፅም ወስደው በሐይቅ በመሠዊያው በስተቀኝ በኩል በቀበሩት ጊዜ በፊት ያስቸግር የነበረው የበሐሩ ኃይለኛ ንውጽውጽታ በአንድ ጊዜ ጸጥ አለ፡፡ ሌላም ብዙ ተአምራት ተደርገው ታዩ፡፡ ይኸውም ፍልሰተ ዐፅማቸው የካቲት 8 ቀን የተፈጸመ ነው፡፡
የአራቱ ቅዱሳን ነገሥታት፡- ከላስታ (ከዛጉዌ) ነገሥታት መካከል ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ፣ ቅዱስ ገብረ ማርያም፣ ቅዱስ ላሊበላና ቅዱስ ነአኵቶለአብ እነዚህ አራቱ ነገሥታት እንደ መልከጼዴቅ (ዘፍ 14፡18) ክህነትን ከንግሥና፣ ቅድስናን ከንጽሕና ጋር አንድ አድርገው በመያዝ እግዚአብሔርንም ሰውንም በቅድስና አገልግለው አልፈዋል፡፡ በንግሥናቸው ሀገርን በመልካም ሥራና በቅድስና ከማስተዳደራቸው በተጨማሪ ቅዱሳን ጻድቃን ሆነው እግዚአብሔርን በብዙ ድካም በመልካም ተጋድሎአቸው ያገለገሉና አገልግሎታቸውም ሆነ ቅድስናቸው በእግዚአብሔር ዘንድ ስለተመሰከረላቸው ጌታችን የሰጣቸውን ቃልኪዳን መሠረት በማድረግ ቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናችን የቅድስና ማዕረግ ሰጥታ፣ በስማቸው ቤተክርስቲያን አንጻ፣ ጽላት ቀርፃ በዓላቸውን እያከበረች መታሰቢያቸው ተጠብቆ ለዘለዓለም እንዲኖር አድርጋለች፡፡
ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ፡- ግንቦት 19 ቀን ሲወለድ እንደነ ተክለሃይማኖትና እንደነ ዜና ማርቆስ ወደ ምሥራቅ ዞሮ አምላኩን ያመሰገነ ሲሆን ቤቱም በብርሃን ተሞልቶ ታይቶ አዋላጆቹን ሁሉ አስገርሟል፡፡ እርሱ ገና ሳይወለድ በፊት አጎቱ ጠንጠውድም በንግሥና ላይ ሳለ ‹‹ከአንተ በኋላ የሚነግሠው ይምርሃነ ክርስቶስ የሚባል ሰው ነው›› ተብሎ ሲነገረው ‹‹እንዲህ የሚባል ሰው በቤተ መንግሥቴ አለን?›› በማለት ቢጠይቅም እንደነቢዩ ኤርሚያስ ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ የተመረጠ ሕፃን እንደሚወለድ ነግረውታል፡፡ አርባ ዓመት የነገሠው ጠንጠውድም ቀድሞ በትንቢት እንደተነገረው ‹‹ይምርሃነ ክርስቶስ›› የሚባል የወንድሙ ልጅ መወለዱን ሲሰማ ‹‹የወንድሜን ልጅ አየው ዘንድ አምጡልኝ›› ብሎ ላከ፡፡ ባየውም ጊዜ ደም ግባቱ እጅግ ያምር ስለነበር ‹‹ይህስ መንግሥቴን ይውረስ፣ በእውነት ልጄ ነው›› ብሎ ባረከው፡፡ ሆኖም ከእርሱ ጋር ስምንት ቀን ተቀምጦ በወለዳቸው ልጆቹ መካከል በተመለከተው ጊዜ በልቡ ሰይጣን አደረበትና በቅናት ሆኖ ‹‹እርሱ ነግሦ ልጆቼ ወታደሮቹ ሊሆኑ ነው›› በማለት ይገድለው ዘንድ አሰበ፡፡ ሆኖም ግን ‹‹ለጊዜው ምንም አያውቅም ለወደፊቱም የንግሥና ምሥጢር እንዳያውቅ ወደ እናቱና አባቱ ዘንድ መልሰው በዚያ ከብት ሲያግድ ያድጋል እንጂ ሥርዓተ ንግሥናን አያውቅም›› በማለት ስለተመከረ ወደ እናቱ ላከው፡፡ በኋላም በጥበብና በብልሃት አስተዋይ ሆኖ ማደጉን በሰማ ጊዜ ሊገድለው አሽከሮቹን ላከ፡፡ እናቱም ተላኩት አሽከሮች ምግብ አቅርባ እርሷ ግን ነገሩን እንዲገልጽላት እግዚአብሔርን በስውር አልቅሳ ስትለምን የንጉሡ ተንኮል ስለተገለጠላት ልጇን ደበቀችው፡፡ በስውርም ወስዳ ከጳጳሱ ዘንድ ዲቁና እንዲቀበል ካደረገችው በኋላ ‹‹ልጄ ሆይ! አጎትህ ሊገድልህ ይፈልግሃልና በፊቴ ከሚገድልህ ርቀህ ብትሄድ ይሻላል፣ ያዕቆብን ከኤሳው የጠበቀ አንተንም ይጠብቅህ›› ብላ ሸኘችው፡፡ ንጉሡ አጎቱም ‹‹ይምርሃነ ክርስቶስን ፈልጎ ላገኘልኝ የመንግሥቴን እኩሌታ እሰጣለሁ›› ብሎ ቢያውጅም ይምርሃነ ክርስቶስ ግን ወደ ኢየሩሳሌም ተሰደደ፡፡ በዚያም የሌዋውያን ወገን የምትሆን ቅድስት ሕዝባን አግብቶ ቅስናም ተቀብሎ ሥጋዊውንና መንፈሳዊውን ጥበብ ተምሮ ካጠናቀቀ በኋላ ወንጌልን እየሰበከ፣ በተአምራቱም ሕመምተኞችን እየፈወሰ እግዚአብሔር እያገለገለ ኖረ፡፡ እግዚአብሔርም አጎቱ ንጉሥ መሞቱንና በንጉሡም ዙፋን እርሱ እንደሚነግሥ ነግሮት በመልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል መሪነት ወደ ኢትዮጵያ ተመልሶ መጥቶ በላስታ ወረዳ ሳይ (ዛሬ ሸጐላ ማርያም) ከምትባል ሀገር ደርሶ በዚያ ወንጌልን እያስተማረ፣ ድውያንን እየፈወሰ ተቀመጠ፡፡ ትምህርቱንና ተአምራቱን ያዩት የአካባቢው ሰዎች ‹‹ነፃነትና ፍቅር የሚገኝብህ የእግዚአብሔር ሰው ሆይ! እኛ ሰላማዊ ብርሃናዊ ብለን ስም አወጣንልህ፣ ያንተ ግን ስምህ ማን ይባላል ንገረን›› አሉት፡፡ እርሱም ‹‹ስሜ ይምርሃነ ክርስቶስ ነው›› ባላቸው ሰዓት ሕዝቡ ሁሉ በሹክሹክታ ‹‹ይምርሃነ ክርስቶስ የሚባል ሲነግሥ ሃይማኖት ይቀናል፣ ፍርድ ይስተካከላል፣ በዘመኑም የሮም ሰዎች ለኢትዮጵያ ይገዛሉ›› ሲሉ አባቶቻችን ሰምተናል አሉ፡፡ ከጠንጠውድምም ሞት በኋላ ማንም እንዳልነገሠ ሲያረጋግጡ የማን ልጅ እንደሆነ እንዲነግራቸው በእግዚአብሔር ስም ለመኑትና ‹‹የጠንጠውድም የታናሽ ወንድምና የዣን ስዩም ታላቅ ወንድም የሆነው የግርማ ስዩም ልጅ ነኝ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹የተነገረው ትንቢት ደርሷልና ሳንዘገይ እናንግሠው›› ብለው ሥርዓተ መንግሥቱን ፈጽመው በዙፋን ላይ አስቀመጡት፡፡
ለቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ መስቀል ከሰማይ እንደወረደለት፡- ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ በትረ መንግሥቱንም ከያዘ በኋላ ሁሉም ሰው እንደወንጌሉ ቃል በአንድ ለአንድ ጋብቻ ብቻ ተወስኖ እንዲኖር በግዛቱ ሁሉ አወጀ፡፡ እግዚአብሔርም የሚመሰገንበት ቤት መሥራት አሰበና የተፈቀደለትን ቦታ እንኪያገኝ ድረስ ዛዚያ በምትባል ልዩ በሆነች ስፍራ ድንኳን ተክሎ እንደሙሴ እግዚአብሔርን ማገልገል ጀመረ፡፡ ዘጸ 33፡7፡፡ ሰኔ 21 ቀንም ቀድሶ ሕዝቡን ከማቁረቡ በፊት ኅብስቱንና ጽዋውን የእግዚአብሔር መልአክ ሕዝቡን ከሚባርክበት ሰማያዊ መስቀል ጋር ከሰማይ አምጥቶለታል፡፡ በዚህ ዓይነት ሁኔታ ሕዝቡን ከሰማይ በወረደለት መስቀል እየባረከና ሰማያዊውን ኅብስትና ጽዋ እያቆረበ ለ22 ዓመት በድንኳኗ ውስጥ ኖሯል፡፡ ዛሬም ድረስ ያንን ሰማያዊው መስቀል በቤተመቅደሱ የሚያገለግሉት ካህናት አባቶች ቤተመቅደሱን ለመሳለም የሚመጣውን ሕዝበ ክርስቲያን በበዓል ቀን ይባርኩበታል፡፡
መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለይምርሃነ ክርስቶስ ተገልጦለት ቤተመቅደሱን ሥራ ብሎ እንደነገረውና ቃልኪዳን እንደሰጠው፡- ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ሰማያዊ ኅብስትና ጽዋ እየወረደለት ለ22 ዓመት በድንኳኗ ውስጥ ካገለገለ በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በክብር ተገልጦለት እንዲህ አለው፡- ‹‹ወዳጄ ይምርሃነ ክርስቶስ ይህን ሥፍራ (ዛዚያን) ልቀቅ፣ ከእንግዲህ ወዲህ በዚህ ቦታ ሰማያዊ ኅብስትና ሰማያዊ ጽዋ አይወርድልህም፡፡ ወደማሳይህ ቦታ ተነሥተህ ሂድ፣ በዚያም እስከ ዕረፍትህ ቀን ድረስ ሰማያዊ ኅብስትና ሰማያዊ ጽዋ ይወርድልሀል፡፡ ይህን ዓለም ለማሳለፍ እስከምመጣበት እስከ ዕለተ ምፅዓት ድረስ የእኔ ጌትነት የአንተም የቅድስና ሕይወት የሚነገርበት፣ የሥጋህ የዕረፍት ቦታ የሚሆንበት፣ ለምትሠራው መቅደስ ክዳን የሚሆን ሣር የማይፈልግ ሰፊ ዋሻ አለ፣ በዚያ ቤተ መቅደሴን ሥራ፣ እኔም በምትሠራው ቤተ መቅደስ ከአንተ ጋር ለዘለዓለም ቃልኪዳኔን አቆማለሁ፡፡ በምታንጸው ቤተ መቅደስ ውስጥ ‹አቤቱ የይምርሃነ ክርስቶስ አምላክ ሆይ! ስለወዳጅህ ስለ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ብለህ ይቅር በለኝ› እያለ ‹አባታችን ሆይ!› የሚለውን ጸሎት የሚጸልይ ዕለቱን እንደተጠመቀ አደርገዋለሁ፡፡ ወደ አንተ በእምነት ከኃጢአቴ እነፃለሁ ብሎ በእምነት የሚመጣውን ሁሉ ከእናትቱ ማኅፀን እንደተወለደ ሕፃን ልጅ አድርገዋለሁ፤ ኃጢአቱንም ይቅር እለዋለሁ፣ ኃጢአቱ ከባድ ጭነት እንደያዘች መርከብ ቢከብድም እንደገለባ አቀልለታለሁ፣ እንደቀይ ግምጃ ቢሆንም እንደነጭ ፀምር (ግምጃ) እንደጥቁር በርኖስ ቢሆንም እንደበረዶ አነፃዋለሁ፤ በስምህ የለመነኝን ሁሉ እሰጠዋሁ፣ ወደ መቃብርህም ቦታ እኔና የባሕርይ አባቴ አብ የባሕርይ ሕይወቴ መንፈስ ቅዱስ በፍቅር ካልሳብነውና በረድኤት ካላቀረብነው በቀር ሊመጣ የሚችል የለም፡፡ በመቃብርህ እየዞረ ‹የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ አምላክ ሆይ! ስለወዳጅህ ስለ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ብለህ ይቅር በለኝ፣ ይምርሃነ ክርስቶስ ሆይ በቃልኪዳንህ ጠብቀኝ (ይምርሃ ፍታኝ)› እያለ የሚጸልየውን አንተ በከበርክበት ክብር አከብረዋለሁ፡፡ የእኔን ጌትነት፣ የአንተን የቅድስና ሕይወት የሚንቅ የሚያቃልል ግን ንስሐ ካልገባ በቀር ከሰማያዊ ክብር የተለየ ይሆናል፡፡ የዕረፍትህን መታሰቢያ የሚያደርግ፣ በአማላጅነትህ ለሚታመን፣ ገድልህን የሚጽፍና የሚያጽፍ የዘላለም ክብርን አጐናጽፈዋለሁ፤ ገድልህን የሚያነብ በአንዷ ቃል ሰባት እጥፍ ክብር በመንግሥተ ሰማያት እሰጠዋለሁ፤ ወደዚህች ቦታ አንተን ብሎ የመጣውን እንግዳ ሁሉ ካላሰበበት ቦታ አላሳድርብህም፤ በምታንጸው ቤተ መቅደስ በዕረፍትህ መታሰቢያ ቀን ከጠዋት እስከ ማታ ተግቶ የሚጸልይ በስሜ ከሞቱ ከ144,440 የቤቴልሔም ሕፃናት ጋር እቆጥረዋለሁ፤ ለቤተ መቅደስህ ዕጣን ያገባ ሥጋዬ እንደተገነዘበት እንደ ኒቆዲሞስ ሽቱ እቀበለዋለሁ፣ አልባሳት የሚያገባ ኒቆዲሞስና ዮሴፍ ሥጋዬን እንገነዙበት መግነዝ አደርግለታለሁ፤ ለመሥዋዕት የሚሆን ንጹሕ የግብር ስንዴ፣ ወይን (ዘቢብ) የሚያመጣውን እንደ መልከጼዴቅ እቀበለዋለሁ፤ ለመብራት የሚሆን ጧፍ፣ ሰም ሌላም የቤተ መቅደስ መገልገያዎችን ሁሉ ለቤተ መቅደስህ የሚያገባ በሰማያዊ ክብር አከብረዋለሁ፡፡ ነገ ማለዳ ተነሥተህ ወግረ ስሂን ወደሚባለው የዕረፍትህ ቦታ ወደሚሆነው ዋሻ ሕዝብህን አስከትለህ ሂድ፤ በዚያም ቤተ መቅደሴን ሥራ›› ብሎ ጌታችን ቃልኪዳን ከሰጠው በኋላ ሰላምታ ሰጥቶት በክብር ወደ ሰማይ ዐርገ፡፡ ቤተመቅደሱንም አንጾ ሲጨርስና በዕረፍቱም ቀን በድጋሚ ተገልጦለት ይህንን ቃልኪዳን ደግሞለታል፡፡
ይምርሃነ ክርስቶስ ቤተ መቅደሱን የሚሠራበትን ቦታ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል እንዳሳየው፡- ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ከመድኃኔዓለም ክርስቶስ ቃልኪዳን ከተቀበለ በኋላ አገልጋዮቹን አስከትሎ ሲጓዝ ቀድሞ ግፃት ትባል ከነበረችው ዛሬ ግን ወግረ ስሂን ከምትባለው ሰፊ ዋሻ ሲደርስ ቅዱስ ሩፋኤል ‹‹እግዚአብሔር ያዘዘህ ቦታ ይህ ነው፣ በዚህ ቤተ መቅደሱን ሥራ›› አለው፡፡ ዙሪያው በደን የተሸፈነ ስለነበር የዋሻውን መግቢያ እያስቆረጠ ሲሄድ የአካባቢው ሰዎች ደም እያፈሰሱ ለአጋንንት መሥዋዕት የሚያቀርቡበት አንድ ወይራ ነበርና አገልጋዩ ክርስቶስብነ ያንን ዛፍ ሲቆርጠው በውስጡ ያደረው ሰይጣን ክርስቶስብነን አንቆ ጣለው፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ሩፋኤል አዛፍ ከሚባል ሀገር ወስዶ ጣለው፡፡ የቅድስት ኢየሉጣ ልጅ ሰማዕቱ ቅዱስ ቂርቆስም በአፀደ ነፍስ ብፁዕ ይምርሃነ ክርስቶስን ረድቶታል፡፡ ይህም ታሪክ በገድለ ቅዱስ ቂርቆስ 3ኛ ተአምር ላይ በሰፊው ተጠቅሷል፡፡ ይህንንም ቀጥሎ ባለው ርዕስ ላይ እናየዋለን፡-
በቅዱስ ቂርቆስ ገድል ላይ ሕፃኑ ቂርቆስ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስን እንደረዳው ተጽፏል፡- ‹‹በቅድስት ሀገር በሮሐ ከአምላኩ ዘንድ የክህነትን ሥልጣን የተቀበለ የዓለምን ተድላ ደስታ ንቆ መንግሥቱን ከተወ በኋላ በገዳም ሲኖር ለ40 ዓመት ያህል በበዓላትና በየሰንበቱ ከሰማይ ኅብስትና ወይን የወረደለት አንድ ጻድቅና ካህን ነበር፡፡ የጽድቁም ምልክት እስካሁን ክቡር ሥጋው ካረፈበት ሥፍራ አለ፡፡በመንግሥቱ ሳለ በእግዚአብሔር ፈቃድ መንፈስ ቅዱስ ባመለከተው ቦታ በባሕር ላይ ቤተ ክርስቲያን ሊያንጽ ተነሣ፡፡ ንጉሥ ይምርሃነ ክርስቶስን የቤተ ክርስቲያኑን መሠረት ለማሳመር ሁሉ እያንዳንዱ ደንጊያና ሸክላ አንጨትም እንዲሸከም ትእዛዙን ይነግር ዘንድ በግዛቱ ዓዋጅ ነጋሪ አዞረ፡፡ ንጉሡም ከባሕር ዳርቻ ቆሞ አገልጋዩ በባሕሩ ላይ ለቤተክርስቲያኑ መሠረት ርብራብ ሊያደርግ ከባሕሩ ገባ፡፡ ይህንንም ሲያደርግ የባሕር ጋኔን ወጥቶ መታው፣ ፈጥኖም ሞተ፡፡ ንጉሥ ይምርሃነ ክርስቶስ የሰይጣንን መተነኳኮል አይቶ አብዝቶ አዘነ፡፡ በዚህ ጋኔን ስለሞተ አገልጋዩ ስለ ቤተክርስቲያንም መታነጽ የሚያደርገውን ሲያስብ ስለጽድቅ የተጋደለ ማር ቂርቆስ ድንገት በታላቅ ክብር ተገልጦ ‹የተቀባህ ንጉሥ የከበርህም ካህን ሆይ! በአምላኬ ሥልጣን የሞተ አገልጋይህን እኔ አስነሣልሃለሁ፣ ጋኔኑንም እበቀለዋለሁ፣ አንተም ኃይል በተደረገልህ ሥፍራ በምትሠራት መቅደስ ውሰጥ በስሜ የተሠየመ ታቦት ታኖራለህ› አለው፡፡ ንጉሡም ‹የክርስቶስ ሰማዕት ሆይ! እንዳልኸው አደርጋለሁ› ብለ መለሰ፡፡ ያንጊዜም ማር ቂርቆስ እጁን ዘርግቶ የጋኔኑን የራስ ጠጉር ይዞ ከባሕር ውስጥ አወጣው፡፡ ቁመቱ ፈጽሞ ረጅም፣ ሁለንተናውም በእሳት እንዳቃጠሉት የእንጨት ግንድ ጥቁር ነበር፡፡ ከቅድስት ሀገር ከሮሐ ወደ ጎጃም ምዕራባዊ ክፍል እንደ ድንጊያ ወረወረው፣ በዚያም ሞተ፤ የሞተው የንጉሡ አገልጋይ ግን ከሞት ተነሣ፡፡ ንጉሡም ፈጽሞ ደስ ተሰኘ፡፡ አምስት ጊዜ ከሩቅ የዞጴ እንጨት እየተሸከመ ያችን መቅደስ ሠራት፡፡ ከአገልጋየቹም ጋር ሲሠራ ይውል ነበር፡፡ ጌታ ኢየሱስም የመቅደስ ሥራዋን እያመለከተው ከእርሱ ጋር ነበረ፡፡ የመቅደስ መታነጽም ከተፈጸመ በኋላ ንጉሥ ይምርሃነ ክርስቶስ በከበረ ሕፃን ቂርቆስ ስም የተሠየመ ታቦት በውስጧ አኖረ፡፡ ኅብራቸው ባማረ የከበሩ ጌጦችና ልብሶችም አስጌጣት፡፡ በውስጧም በጥቅምት 19 ቀን ቀደሰ፡፡›› (ገድለ ቅዱስ ቂርቆስ ወኢየሉጣ ገጽ 98-100)
ወደ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ገድል እንመለስና ጻዲቁ ንጉሥ ጌታችን እንዳዘዘው ቤተመቅደሱን ሊሠራ መንገዱን አስመንጥሮ ወደ ዋሻው ሲደርስ ትልቅ ባሕር አገኘ፡፡ ‹‹በዚህ ላይ እንዴት ቤተመቅደስ ልሠራ እችላለሁ?›› ብሎ ሲጨነቅ ከሰማይ ‹‹በባሕሩ ላይ እንጨት፣ በእንጨቱ ላይ ሣር፣ በሣሩ ላይ ጭቃ፣ በጭቃው ላይ ደረቅ አፈር አድርገህ ደልድለህ ቤተ መቅደሴን ሥራ›› የሚል ቃል መጣለት፡፡ ቀድሞውንም በነቢዩ ዳዊት ላይ አድሮ ‹‹ምድርን በውኃ ላይ ያጸና ምሕረቱ ለዘለዓለም ነውና›› (መዝ 135፡6) እንደተባለ አሁን ደግሞ በዚህ ጻዲቅ ንጉሥ እጅ ቤቱን በባሕር ላይ እንዲሠራ ፈቀደ፡፡ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስም በታዘዘው መሠረት መሥሪያዎቹን ሲሰበስብ የቅድስና ሕይወቱን የሰሙ የግብፅና የሮም ሰዎች ለመስኮት የሚሆኑ የከበሩ ድንጋዮችን (ዕምነ በረዶችን) አመጡለት፡፡ ውድ የሆኑና የከበሩ ዓለቶችንና እንጨቶችን አምጥቶ በኪነጥበባዊ ቅርጻ ቅርጾችና በሥነ ሥዕል እጅግ ውብ አድርጎ በተፈጥሮአዊ አቀማመጡ ፍጹም አስደናቂ የሆነውን ቤተመቅደሱን ሠርቶ እንደጨረሰ ሲራዳው የነበረውን የቅዱስ ቂርቆስን ታቦት አስገብቶ ከሰማይ በወረደለት መስቀሉ ሕዝቡን እየባረከ፣ ሰማያዊ ኅብስትና ሰማያዊ ጽዋ እየወረደለት እግዚአብሔርንና ሰውን ሲያገለግል ኖረ፡፡ ቅዱስ ሩፋኤልም በዘመኑ ሁሉ ይራዳው ነበር፡፡
ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ያሳነጸውን ቤተመቅደስ እንደገና በወርቅና በብር አክብሮ ለማነጽ ወደ እግዚአብሔር በጸሎት ቢጠይቅ ጌታችን ተገልጦለት ‹‹ቤተ መቅደስህ የታጸበትን የከበረ ድንጋይ ከወርቅና ከብር ከዕንቁም ይልቅ አከበርኩልህ፣ በወርቅና በብር ያነጸከው እንደሆነ የኋላ ሰዎች ወርቅና ብሩን ሲሉ ቤተክርስቲያንህን ያፈርሱብሃል›› ብሎታል፡፡ ቤተመቅደሱ የተሠራው በባሕር ላይ ለመሆኑ ማሳያ ይሆን ዘንድ ከቤተ መቅደሱ ሰሜናዊ ጫፍ በኩል ወደ ታች ወደ ምድር ውስጥ የምትከፈት ትንሽ መስኮት አለች፣ እርሷ ስትከፈት ውኃው ከሥር ይታያል፡፡ ይህን ግን ማሳየት የሚችሉት አባቶች ብቻ ናቸው፡፡ በዋሻው በቤተልሔሙ በኩል ውስጥ ለውስጥ እስከ አቡነ ዮሴፍ ተራራ ድረስ የሚወስድ ፍጻሜው ያልተገኘ መንገድ አለ፡፡ የቤተክርስቲያኑ አገልጋዮች በዋሸው ውስጥ ለውስጥ የ4፡30 መንገድ ያህል በመብራት ከተጓዙ በኋላ የያዙት መብራት ስላለቀባቸውና ፍርሃትም ስለያዛቸው የመንገዱን ፍጻሜ ሳያገኑት ተመልሰዋል፡፡
ቁጥራቸው ከ5ሺህ በላይ የሆኑ የሮምና የግብፅ ጳጳሳት የይምርሃነ ክርስቶስን በረከት ሊቀበሉ እንደመጡ፡- ከዚህ በኋላ የእግዚአብሔርን ጌትነትና የይምርሃነ ክርስቶስ የቅድስና ሕይወት በዓለም ሁሉ መሰማት ጀመረና የሮም ሰዎችም ወደ እርሱ መጥተው 55 ውድ መስቀሎችን በስጦታ ገበሩለት፡፡ እግዚአብሔር በእርሱ ላይ የሚያደርገውን ተአምርና ቅድስናውን የሰሙ ቁጥራቸው 5740 የሆኑ የግብፅና የሮም ጳጳሳትና ኤጲስቆጶሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት እንዲሁ መነኮሳት ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ የሚወርድለትን ሰማያዊ ኅብስትና ሰማያዊ ጽዋ በእጁ ለመቀበልና በመስቀሉ ለመባረክ መጡ፡፡ የግብፁ ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ አትናቴዎስም ‹‹ከዚህ ቅዱስ የእግዚአብሔር አገልጋይ እጅ በረከትን መቀበል እሻለሁ›› ብሎ ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ከቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ጋር ተገናኝቶ ሁለቱም በረከትን አንዳቸው ከአንዳቸው ተቀብለዋል፡፡ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስም ወደ እርሱ ለመጡት 5740 ደጋግ ጳጳሳትና ኤጲስቆጶሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት እንዲሁ መነኮሳት ሁሉ ቀድሶ ሰማያዊውን ሥጋ ወደሙን አቀብሏቸዋል፡፡ እነርሱም ሰማያዊውን ሥጋና ሰማያዊውን ደሙን ከተቀበሉ በኋላ ‹‹ይህን ባየንበትና በቀመስንበት ሌላ አናይም አንቀምስም ብለው የተወሰኑት ወደሌላ የሀገራችን ገዳማት የሔዱ ሲሆን ብዙዎቹ ደግሞ ከእርሱው ጋር አብረው በዚያው ዐርፈው ተቀብረዋል፡፡ ዛሬም ድረስ የእነዚህ ቅዱሳን አፅም ቤተ መቅደሱ ካለበት ጀርባ በኩል በሚገኘው ትልቅ ዋሻ ውስጥ በክብር ተቀምጦ ይገኛል፡፡
የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ መካነ መቃብር፡- ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስን ዕረፍቱ እንደደረሰ ነግሮት ታላቅ ቃልኪዳን ከሰጠው በኋላ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ጥቅምት 19 በታላቅ ክብር ዐርፏል፡፡ የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ መካነ መቃብር የሚገኘው ራሱ ባሳነጸው መቅደስ በስተ ደቡብ አቅጣጫ ሲሆን በግምጃ የተሸፈ ነው፡፡ ለጻዲቁ ንጉሥ በተሰጠው ቃልኪዳን መሠረት አማኞች መእመናን መቃብሩን እየዞሩ ‹‹የቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ አምላክ ሆይ! ስለወዳጅህ ስለ ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ብለህ ይቅር በለኝ፣ ይምርሃነ ክርስቶስ ሆይ በቃልኪዳንህ ጠብቀኝ (ይምርሃ ፍታኝ)›› እያሉ በመዞርና አባታችን ሆይ የሚለውን ጸሎት እየጸለዩ ከቃልኪዳኑ በረከት ይሳተፋሉ፡፡
የአቡነ ዓቢየ እግዚእን ገድል ደግሞ አንዴ ለራሴ ልዝለቀው እመለስበታለሁ፡፡ ደሞ እየጻፍኩት ሳለ መብራት ጠፋ....እይይ...ምቀኛ!
መብራት ሄዶ ቆይቶ አሁን ስለመጣ የአቡነ ዓቢየ እግዚእን ገድል አሁን አካትቼዋለሁ፡፡
አቡነ ዓቢየ እግዚእ፡- አባታቸው ያፍቅረነ እግዚእ እናታቸው ጽርሐ ቅዱሳን ይባላሉ፡፡ ሁለቱም ሃይማኖታቸው የቀና ምግባራቸው ያማረ በእግዚአብሔር የተወዱ ናቸው፡፡ በወርቅ በብር የከበሩ ቢሆኑም ልጅ ግን አልነበራቸውም፡፡ በእመቤታችን ስም ለተቸገሩ ምጽዋትን በመስጠት ዘወትር ይማጸኑ ነበር፡፡
አንድ ቀን ድንቅ የሆነ ራእይ አየና ፈቃደ እግዚአብሔርን ሲጠባበቁ ነሐሴ 7 ቀን ጽርሐ ቅዱሳን ፀነሰችና ግንቦት አንድ ቀን እንደ ፀሐይ የሚያበራ ልጅ ወለደችና በ40 ቀኑ ሲጠመቅ ስሙን ዓቢየ እግዚእ አሉት፡፡ ያጠመቁትም የአክሱሙ ሊቀ ጳጳስ መተርጉም ሰላማ ሲሆኑ እሳቸውን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ሕጻኑን እንዲያጠምቁት በማዘዝ በክንፎቹ ተሸክሞ ከአክሱም ወደ ተንቤትን ምድረ መረታ አመጣቸውና አጠመቁት፡፡ እርሳቸውም ‹‹ይህ ሕጻን ድውይ የሚፈውስ ሙታንን የሚያነሣ ቅዱስ ይሆናል›› ብለው ትንቢት ተናግረዋል፡፡ ያፍቅረነ እግዚእ እና ጽርሐ ቅዱሳን እንግዳን መቀበል ልማዳቸው ነበርና አንድ ቀን ሦስት አጋንንት በሽማግሌ አምሳል ሆነው በእንግድነት እቤታቸው ገቡና ‹‹ልጃችሁን የሐዋርያትን መጻሕፍትን መዝሙረ ዳዊትንና አርጋኖንን እንድናስተምርላችሁ ስጡን›› አሏቸው፡፡ ወላጆቹም ገና ሕጻን መሆኑን በመናገር ሲከራከሩ ቅዱስ ሚካኤል ደርሶ እነዚያን አጋንንት አጠፋቸው፡፡ አጋንንቱም ይህንን ዘዴ ተጠቅመው ሕጻኑን ዓቢየ እግዚእ ወስደው ሊገድሉት ነበር ምክንያቱም በእርሱ ምክንያት ነፍሳት እንደሚድኑ ዐውቀዋልና፡፡
ገና ከልጅነታቸው ጀምሮ የእግዚአብሔርን ከጠሩበት ምንም ነገር ከማድረግ ወደኋላ አይልም ነበር፡፡ ከልጆችም ጋር ሲጫወቱ ልጆቹ ‹‹ስለ እግዚአብሔር ብለህ ይህን አድርግልን…›› ሲሉት ያደርግላቸዋል፡፡ በእረኝነት ሳሉ ምሳውንም ሆነ እራቱን ለምስኪኖች ይሰጣል፡፡ ለእግዚአብሔር ስም እጅግ ቀናተኛ ስለነበሩ ስሙን ይፈሩ ስለነበር ስመ እግዚአብሔርን ጠርተው ‹‹ይህን ክፉ ነገር በራስህ ላይ አድርግ›› ባሏቸው ሰዓት እንኳን በራሳቸው ላይ አንዳች ክፉ ነገር ወይም አደጋ ለማድረስ ወደኋላ አይሉም ነበር፡፡ ይህንን ሊፈትኗቸው ብለው አንድ ቀን ስለታማ ጦር አምጥተው ‹‹ስለ እግዚአብሔር ብለህ እስቲ ራስህን በዚህ ስለታማ ጦር ትወጋ ዘንድ ና›› ባሏቸው ጊዜ አብርሃም ልጁን ይስሃቅን ሊሠዋ በኅሊናው እንደወሰነ እርሳቸውም በቁርጥ ኅሊና ሆነው ራሳቸውን በጦሩ ሊወጉ ሲሉ ዘለው ያዟቸው፡፡ በሌላም ጊዜ እንዲሁ ሊፈትኑት በጭነት ምክንያት ጀርባው የቆሰለ አህያ አምጥተው ‹‹ዓቢየ እግዚእ ስለ እግዚአብሔር ብለህ የዚያችን አህያ ቁስሏን ላስ›› አሉት፡፡ እርሱም ያን ጊዜ ‹‹ርኩስን ብስም ኃጢአት ይሆንብኛል፣ አይሆንም ካልኳቸው ደግሞ ስመ እግዚአብሔርን ጠርተንበት እምቢ አለ ስለሚሉ የፈጣሪዬን ስም መዳፈር ይሆንብኛል ብሎ በልቡ አሰበና ያን ጊዜ ይስም ዘንድ ተመለሰ፡፡ ባልንጀሮቹም በቁርጥ ኅሊናው እንደወሰነ ባወቁ ጊዜ ሊያደርገውም ሲሄድ ተመልከተው ቶሎ ብለው ሮጠው ከኋላው ያዙት፡፡ እርሱም ‹‹እኔስ የፈጣሪዬን ስም እፈራለሁ ስሙን ተደፋፍሬ በምድር በሕይወት ከምኖር ሞት ይሻለኛል›› አላቸው፡፡
ከዚህም በኋላ ወላጆቹ ለመምህር ዘርዐ ሚካኤል ሰጡትና ብሉያት ሐዲሳት መጻሕፍትን ሌሎችንም አስተማረው፡፡ ከዚህም በኋላ መምህሩንና ዓቢየ እግዚእን ቅዱስ ሚካኤል ነጥቆ ወስዶ አክሱም አደረሳቸውና ዓቢየ እግዚእ ከአባ ሰላማ መተርጉም እጅ ዲቁናና ቅስና ተቀበሉ፡፡ ከብዙ ዘመንም በኋላ የሃሌ ሉያው አባ ሳሙኤል ቆብንና አስኬማን ሰጠው፡፡ ለአባታችን አንበሶችና ነብሮች አራዊትም ሁሉ እንደ ጓደኛ ሆነው ታዘዙለት፡፡ ቶራዎችም በሰው አንደበት ያናግሩታል፡፡ ቶራዎቹም ከነብሮች ጋር ተስማምተው እንዲኖሩ ያደርጋቸዋል፡፡ እርሱም እህልን ሳይቀምስ በቤት ጣሪያም ውስጥ ገብቶ ሳይቀመጥ ተጋድሎውን በማብዛት ብዙ ደከመ፡፡ የመላእክት ክንፍ ተሰጥቶት በሦስት ሰዓት ውስጥ የሕያዋንን መኖሪያ አይቶ ይመለሳል፡፡ በዋልድባ ገዳም ስውር ቤተ ክርስቲያን አለ ነገር ግን የሚያገኘው አልነበረም፡፡ አባታችን ዓቢየ እግዚእ ግን 40 ቀንና 40 ሌሊት ከጾመ ከጸለየ በኋላ አራዊት ተሸክመውትና አጅበውት እዚያች ስውር ቤተ ክርስቲያን ዘንድ ደረሰ፡፡ በውስጧም የሚንቀሳቀስ ብርሃን አየ ይኸውም የዚህ ዓለም ብርሃን አይደለም፡፡ በውስጧ ያሉ ስውራን ቅዱሳንንም አገኛቸውና ከእነርሱ ተባረከ፡፡ ከዚህም በኋላ የተለያዩ አስደናቂ ተአምራትን እየሠራ ወንጌልን በመስበክ ብዙ አገለገለ፡፡ የተከዜን ባሕር ለሁለት ከፍሎ በመሻገር በአካባቢው ያሉ ኢስላሞችን በተአምራቱ አሳመናቸው፡፡ ከደረቅ ጭንጫም ላይ ውኃን አፈለቀ፡፡ በተሰሰጠውም ክንፍ ብሔረ ሕያዋንና የጌታችን መካነ መቃብር ዘንድ እየሄደ ከቅዱሳን ጋር ጸሎት ያደርጋል፡፡ ደቀ መዛሙርቶቹም ‹‹እገሌ ሞቷልና የት እንቅበረው? ባሉት ጊዜ እርሱ ግን ከጸለየ በኋላ ከሞት ያስነሣዋል፡፡ የሐማሴኑ መስፍንም እንዲሁ በጦርነት ወቅት ሞቶ ባለሟሎቹ አስክሬኑን ተሸክመው ወደ ሀገሩ ሲወስዱት ሰላምጌ ከምትባል የላስታ ምድር ደረሱና በመንገድ አባታችንን አገኛቸውና ‹‹ይህን በድን ወዴት ትወስዱታላችሁ?›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹ሐማሴን ይባላል በንጉሡ ትእዛዝ ወደ ጦርነት ዘምተን ሳለ እርሱ ሞቶ ወደ ሀገሩ እየወሰድነው ነው›› አሉት፡፡ አባታችንም ያስቀምጡት ዘንድ አዘዛቸውና ውኃ አምጡልኝ አላቸው፡፡ ስመ እግዚአብሔርንም ጠርቶ ከጸለየና በውኃው ካጠመቀው በኋላ ሐማሴንን ከሞት አስነሣው፡፡ ሐማሴንንም ስለ አሟሟቱ ሲጠይቁት ‹‹መልአከ ሞት ወስዶ ለፍርድ ሳያቆመው በፊት ይህ ጻዲቅ መነኩሴ ስለ እኔ ሲለምን አየሁት፤ በጸሎቱም እግዚአብሔር ማረኝና ነፍሴን ወደ ሥጋዬ እንድትገባ አዘዘ›› ብሎ የሆነውን ሁሉ በዝርዝር ነገራቸው፡፡ አባታችንም ሐማሴንን ‹‹በሰላም ወደ ሀገርህ ሂድ›› ብሎ አሰናበተው፡፡ ያ ሹም ግን ገንዘቡን ሁሉ ለድኆች መጽውቶ ወደ አባታቸን ዘንድ መጣ፡፡ የአባታችንን ጽድቁንና ትሩፋቱን የሰሙ ሁለት ሺህ ሰዎችም አብረውት ከሹሙ ጋር መጡና አባታችንን ‹የምንኩስና ልብስ ልንለብስ እንወዳለን›› ባሉት ከፈተናቸው በኋላ አመነኮሳቸው፡፡ ያንንም መስፍን ፍኖተ ሕይወት-የሕይወት መንገድ ብሎ ሰየመው፡፡ የአባታችንም ያችን ደብር ሰጠውና አበ ምኔት ሆኖ ብዙ አገልግሎ ዘመኑን ጨረሰ፡፡ ዳግመኛም አባታችንን በደብረ መድኃኒት በምትባል ደብር ሳለ ስሟ ቡሩክት ማርያም የምትባል ልጁ ሞታ አባታችን አለቀሰላት፡፡ ተነሥቶም ወደ ዋሻ ገብቶ በሩን ዘግቶ አመድ ነስንሶ ደረቱን እየደቃ እየጸለየ ሳለ ቡሩክት ማርያም ከሞት መነሣቷን ደቀ መዛሙርቱ ሮጠው መጥተው ነገሩትና ሄዶ አገኛት፡፡ ‹‹ምን አየሽ?›› ቢላት እርሷም ‹‹‹ስለአገልጋዬ ዓቢየ እግዚእ ልቅሶና መቃተት ይህች ነፍስ ወደ ሥጋዋ ትመለስና እስከምታረጅ ትኑር› የሚል ቃል ሰማሁ›› አለችው፡፡ እርሷም አባታችን ካረፉ በኋላ በምድረ ዠመዶ ኖራ በኋላ በሰላም ዐረፈች፡፡ ከዕለታትም በአንደኛው ቀን ብፁዕ አባታችን ከ6 መነኮሳት ልጆቻቸው ጋር ይሰግዱ ዘንድ ሲሄዱ ርዝመቱ 120 ስፋቱ 12 ክንድ የሆነ ዐይኖቹ እንደሚነድ እሳት የሆኑ ከአፉም ነበልባል የሚወጣ እንደንስርም ክንፍ ያለው ከዚህ በፊት ታይቶ የማይታወቅ መጠኑም ተራራ የሚያክል አውሬ በቁጣ ሊውጣቸው አፉን ከፈተ ምላሱን አውለበለበ፡፡ መነኮሳቱም እጅግ ደንግጠው ሳለ አባታችን ግን በስመ ሥላሴ አማትበው በአውሬው ላይ የተገለጠውን ያንን ከይሲ ለሁለት ሰነጠቁት፡፡ አንዲት እናት ወደ አባታችን መጥታ ‹‹የአንተን የጸሎት ውኃ ስጠኝ?›› አለችው፡፡ አባታችንም ‹‹ምን ልታደርጊው ነው?›› ሲላት ‹‹ልጠጣው ነው›› አለችው፡፡ እርሱም ስመ እግዚአብሔርን ጠርቶ ‹‹…አቤቱ ይህንን የጸሎት ውኃ ለሚጠጣው ሁሉ የሚያድን አድገው…›› ብሎ ጸልዮ በስመ ሥላሴ አማትቦ ሰጣት፡፡ እርሷም ወደቤቷ ወስዳ ሌላኛዋን ሴት ‹‹ይህንን የጸሎት ውኃ እጠመቅ ዘንድ በላየ ላይ አፍሽልኝ›› አለቻት፡፡ ሁለተኛዋም ሴት በላይዋ ልታፈስ ውኃውን አነሣች፣ ከፍም አደረገችው፡፡ ነገር ግን ውኃው የረጋ ደም ሆነ፣ አልፈሰሰምም፡፡ እነዚያም መበለታት እጅግ ደንግጠው ‹‹በኃጢአታችን ውኃው ደም ሆነ፣ ወደ አባታችን ሄደን አንንገረው›› ተባብለው ሄደው ነገሩት፡፡ አባታችንም ‹‹ያደረጋችሁት ምንድነው?›› ሲላቸው ሴቷ ‹‹በራሴ ላይ አፍስሽልኝ ከማለቴ በስተቀር ምንም ያደረግነው የለም›› አለችው፡፡ አባታችንም ‹‹ቃልን ከመለወጥ በላይ ሌላ ኃጢአት ምን የለም፣ ቃልሽን ስለለወጥሽ ደም ሆነ፣ እኔን ‹የምጠጣው የጸሎት ውኃ ስጠኝ› አልሽኝ እኔም እንዳልሽኝ ሰጠሁሽ›› አላት፡፡ እርሱም ‹‹አምጭው›› አላትና ሰጠችው፡፡ ተቀብሎ በስመ ሥላሴ ሦስት ጊዜ ቢባርከው ያንጊዜ እንደቀደሞው ንጹሕ ውኃ ሆነ፡፡ ያችንም መበለት ‹‹ልትጠጪ ከወደድሽ ውሰጂ›› አላት፡፡ እነዚያም መበለታት ከምድር ላይ ወድቀው ‹‹ይቅር በለን›› ሲሉት እርሱም እጁን አንሥቶ ባረካቸው፡፡ አባታችን አንድ ቀን ደብረ ሊባኖስ ገዳም ገብቶ ሳለ ገዳማውያኑ ‹‹አንድ መነኮስ ብናገኝ ሥጋወደሙ በተቀበልን…›› ሲባባሉ አገኛቸውና ባረካቸውና ‹‹ዛሬ የተዘጋጀ ቁርባን አለን?›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹አዎን›› አባሉት ጊዜ አዘጋጂተው እንዲያመጡ አዘዛቸው፡፡ አዘጋጅተው አመጡና አባታችንን ‹‹ገብተህ ቀድስ›› አሉት፡፡ እሱም ‹‹ባርኩኝ›› አላቸውና ‹‹እንደ መልከጼዴቅ፣ እንደ አቤል መሥዋዕትህን ይቀበልልህ…›› ባሉት ጊዜ ሚመጠን አለ፡፡ ይህንንም ባለ ጊዜ ኅብስትና ጽዋ ከፃሕል ጋር ተዘጋጅቶ ከላይ ከሰማይ ወረደ፡፡ ይህንንም ያዩና ከእርሱ ጋር የነበሩ ሁሉ ‹‹ይህ ኅብስትና ጽዋ ከየት መጣ›› እያሉ አደነቁ፡፡ አባታችንም የሐዋርያትን ቅዳሴ ቀድሶ አቆረባቸው፡፡ አባታችንም ወጣና ደመናውን ጠቅሶ በደመና ተጫነ፡፡ እነርሱም ‹‹አቤቱ ስለ እግዚአብሔር ብለህ ስምህን ንገረን›› አሉት፡፡ እርሱም ‹‹ስሜ ዓቢየ እግዚእ ይባላል የምንኩስና ስሜ የመረታ ሀገር እንጦንስ ነኝ›› አላቸውና ባረኳቸው ሄደ፡፡ ያም ፃሕልና ጽዋ ዛሬም ድረስ አለ፡፡ ቅዱስ አባታችን በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ የተለያዩ አስደናቂ ተአምራትን እየሠራ ወንጌልን በመስበክ እገዚአብሔርን ካገለገለ በኋላ ከፈጣሪው ታላቅ ቃልኪዳን ተቀብሎ በዛሬዋ ዕለት በክብር ዐርፏል፡፡
የቅዱሳኑ ምልጃቸውና በረከታቸው በአማላጅነታቸው በምንታመን በሁላችን ላይ ይደርብን! አሜን!!!

የእግዚአብሔር መንግሥት መውረሻ ብቸኛ መንገድ በሆነችው በመጀመሪያዋ ንጽሕት ቅድስት በሆነችው በአባቶቻችን ሃይማኖት ያጽናን በእውነት!!! ተዋሕዶ ብቸኛና ፍጽምት ነሽ!

Wednesday, June 24, 2015

ተናገሩ ድንቅ ስራዉንም መስክሩ

"ተናገሩ ድንቅ ስራዉንም መስክሩ"
ከአዲስ አበባ 650 ኪሎ ሜትር መጓዝ ግድ ይላል ታላላቅ የገጠር ከተሞች አሉ በተለይ ከጊቤ በረሃ እንደተሻገርን ግራና ቀኝ አይናችንን እንዲንከራተት ፈቀድንለት ወሊሶ፣ ወልቂጤ፣ ጅማ፣ በደሌ፣መቱን እንዳለፍናት ጎሬ ስንደርስ አንድ ሐውልት ከቤተክርስቲያኑ በር አካባቢ በግርማ ሞገስ ተሸፍኖ ቆሟል፡፡




"ብጹዕ አቡነ ሚካኤል"
ይባላሉ ፋሽስት ኢትዮጵያን በወረራት ጊዜ ልክ እንደ አቡነ ጴጥሮስ በተመሳሳይ ጊዜ ህዝቤም መሬቱም አይገዛልህ ብለው በማውገዛቸው በግፍ በመትረየስ ተረሽነዋል ተገድለዋል፡፡ሰኔ23
ከፓትሪያርኩ ጀምሮ ብጹአን ሊቃነ ጳጳሳት ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት በተገኙበት የሐውልት
ምርቃትና የሰማዕትነትን ስም ያገኛሉ፡፡
ይህንን በረከት ለመሳተፍ ከመላው ኢትዮጵያ በርካታ ህዝብ ከየአካባቢው ይጎርፋል፡
እኛም ተገኝተን ሰፊውን ታሪክ ያኔ እናቀርባለን፡፡
የኢሉባቡር ሀገረ ስብከት ይህንን ታላቅ በዓል
ሐይማኖቱንና ታሪኩን የሚወድ ኢትዮጵያዊ ሁሉ
እንዲገኝ ጥሪ አቅርበዋል፤ይኸው ይድረሳችሁ፡፡

በተለይ ጅማን ይዛችሁ የኢሉባቡር ክልል በግራና
በቀኝዎት ጥቅጥቅ ያለው ደን የተለያዩ የዕጽዋት
ዘር ያለበት ሲሆን በተለይ አመቱን መሉ በአረንጓዴ የተሸፈነው እጅግ ውብና ማራኪ ስፍራ፦ ቀረሮ፣ሰሳ፣ዋንዛ፣ማንጎ፣አቡካዶ፣ቡና፣በቆሎ የመሳሰሉት ተክሎች ይገኙበታል፤
አንዳንዴም እንደው የራበው
መንገደኛ ጫካ ውስጥ ገባ ብሎ ቢወጣ የእለት ጉርሱን አያጣም ይባላል፡፡
አሁን ትንሽ ጉዞ ነው የቀረን ጉመሮ ሻይ ቅጠል ሰፊ የእርሻ መሬት ላይ ደርሰናል
"የመስሊሟ ታሪክ ጀመረ"
፦የዛሬ 3ወር እዚህ ቦታ ላይ
14ሰው የተፈቀደለት ዶልፊን መኪና የዛን ዕለት ግን
27ሰው ጠቅጥቆ ከመቱ ወደ ኡካ ከተማ ጉዞ ጀመረ ፀሐይ ለጨረቃ ፈረቃዋን ቀይራለች ጭለማው በርትቷል የመኪናው ከፍተኛ ፍጥነት ቀጥሏል ከምሽቱ 1ሰዓት ግን ፊለፊቱ ቢራ የጫነ የጭነት መኪና ጋር ፊት ለፊት ተገናኙ ያኔ ነበር እጅግ የአመቱ ዘግናኝ አደጋ ነው የተከሰተው 11ሰዎች ወድያው ላይመለሱ አንቀላፉ ፤ከባድ ጉዳት የደረሰባቸውም አካላቸውን አተዋል ታዲያ "አዋጉ ሠኢድ ኢመማ"
አምቡላንስ እስኪመጣ ከ11አስክሬን ጋር ቅጠል
አልብሰዋት ከሞቱት ጋር ተቆጠረች፤በቆይታ በኋላ
ፊቷ በደም ቢሸፈንም የተረፈው አንድ አይኗ እንደመንቀሳቀስ ሲል የአምፑላንሱ ሹፌር ድንገት
አይቷት ከሞቱት መካከል ለያት ወደ መቱ ሆስፒታል
ሄደች አልተቻለም በኮንትራት መኪና አዲስ አበባ
ጥቁር አምበሳ ሆስፒታል ታከመች፤ እንደ እድል ሆኖ
የተሰበረው እግሯን ሳይጠግኑላት በሚያሳዝን ሁኔታ
ወደ መንደሯ ተመለሰች፡፡
3ወር ሙሉ አትናገርም አትጋገርም ተኝታ ብቻ ማቃሰት መወራጨት ብቻ በሙስሊሞች ባህል ሁሉን አረጉላት መፍትሔ የለም፡፡
አንድ ነገር ቤተሰብ ተማከሩ ይሄ ነገር አንደበቷን የቆለፋት ሰይጣን ሳይሆን አይቀርም ብለው ወደ ቤተክርስቲያን አመሩ አባቶችንም አናግረው ወደ
ቤታቸው ጸሎት እንዲደረግላቸው ተማጸኑ
የቅዱስ ገብርኤልን ጸበል ቤተሰቦቿ በጀሪካን ይዘው
ቀሲስ ትህትና ደግሞ ዳዊታቸውን ሸክፈው አመሩ፡፡
እንግዲህ ሂዱና አህዛብን ሁሉ "በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃቹኃቸው" ያዘዝኳችሁን ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራቹኃቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፡፡
እነሆ እኔ እስከ ዓለም ፍፃሜ ድረስ ሁል ጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ፡(ማቴ 28፥28)
እንደ ስርዓተ ቤተክርስቲያን ከዳዊት፣ውዳሴ ማርያም፣ ኪዳንና ትምህርተ ኀቡአት ካዳረሱ በኋላ
ጸበል እረጯት ጆሮዋም እየተከፈተ መጣ ለካ ከመኪናው በወደቀችበት ሰዓት አጅሬ ሰይጣን አግኝቷታል፡፡
ቀሲስ በሥላሴ ስም በድንግል ማርያም
ልጅ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እያሉ በመስቀል ይዳብሷታል ኡኡኡ እለቃለሁ አጋንንት ነኝ ጂኒ ነኝ መስቀሉ አቃጠለኝ,,,,,,ቄሱም እግዚአብሔርን አመሰገኑት ቤተሰብ "አንደበቷ መከፈቱ "ለነሱ እንደ ተአምር ነው በልባቸው ለገብርኤል ተስለዋል::
አሁን ልቀቅ አታሰቃያት ይሉታል ለቅቄ ወዴት እሄዳለሁ? በተረፈው አንድ ዓይኗ ወደ ቄሱ እያፈጠጠ
እያጓራ አንተላይ ወጥቼ ልምጣ እያለ መፎከር ጀመረ መሪጌታ ቀሲስ ትህትና፡ የእሷን ሰላም ማግኘት
እንጂ የአጋንንቱ ዛቻ አላስፈራቸዉም፤ግድ የለም
በእግዚአብሔር ቃል አሸንፍካለው ና!እያሉ ያናዝዙታል
ዳዊታቸውን ትራስጌዋ ላይ አድርገውላት 4ሰዓት ተኩል ላይ አረፍ ትበል ብለው ወደ ባለቤታቸው
ሱቅ ሄዱ፡፡
ከሱቃቸው ጎን ካለው ሻይ ቤት አረፍ እንዳሉ ኬት
መጣ ሳይባል ትልቅ እባብ ይጠመጠምባቸዋል
እስቲ ለአንድ አፍታ እግራችሁን አስቡት ለዛውም መርዘኛ እባብ ግማሽ አካሉ መሬት ሆኖ የተጠመጠመው አንገቱ ጉልበታቸው ላይ ደርሷል፡፡
" እንደ እግዚአብሔር ሐሳብ ለተጠሩት ነገር ሁሉ ለበጎ እንደሚል" ያ ልጅቷ ላይ ሆኖ የፎከረዉ አጋንንት ለካ ተከትሏቸዋል፡፡
"እነሆ እባብና ጊንጡን ትረግጡ ዘንድ በጠላትም ኃይል ሁሉ ላይ ሥልጣን ሰጥቻችኃለሁ የሚጎዳችሁም ምንም የለም" (ሉቃ 10፥19)
እንዲህ ስገልጽላቹ ቀላል ይመስላል ቀሲስ እንደ ሰዉ ደካማ ናቸውና እየዘለሉ ለማስለቀቅ ብዙ ታግለው ከሳቸው ለቆ ወደ ሚስታቸው ሱቅ እንደተላከ ህፃን የተሳበ ሲገባ አንድ የሻይ ቤቱ ባለቤት ሙስሊም በዱላ ጨፍጭፎ ገደለው፡፡
ወድያው ለሙስሊሞቹ ተነገራቸው በስልክ
(ማሽ አላህ ማሽ አላህ) ተመስገን ለፈጣሪ ምስጋና ይገባው እያሉ የቄሱን እምነት አደነቁ
እኔም ይህ ተአምር ከተከሰተ ከ3ቀን በኋላ ለቅድስት ድንግል ማርያም ልደት በዓል እዛ ከተማ ተገኝቼ ስለነበር ሁሉንም ታሪክ ከሙስሊሞቹ ሰምቻለሁ፡፡
አንደበቷ የተከፈተውንም አውርቻታለው የምታዩትን ፎቶ አነሽቻታለው በመስቀል በቅባ ቅዱስ ቀሲስ እየጸለዩላት፡፡
ባለፈው የፉጡማ ጂብሪል አዲስ የኦርቶዶክስ እንግዳ ብያቹ ነበር፤ ልክ ነኝ
፨አሚራ የምትባለው ከSISI ነፍሰ በላዎችን መርጣ ወደ ሞት መንገድ ሄደች(ተቀላቀለች)ልብ ይስጥልን፤
፨ፋጡማ ጂብሪል ደግሞ በጥምቀት ወደ ዘላለም ህይወት ሰላምን መርጣ የሥላሴ ልጅነት አገኘች ህይወት የሆነውን የኢየሱስ የክርስቶስን አማናዊ ቅዱስ ስጋውንና አማናዊ ክቡር ደሙን ተቀበለች ዛሬ ማንም የማይቀማትን በጎ እድልን መርጣለችና ለእግዚአብሔር ምርጥ ዕቃ ሆነች፡፡በፎቶ ላይ እንዳያችሁት በሰንበት ትምህርት ቤት መዘመር ጀምራለች፡፡ ሁለቱ ወንድምና እህቶችም ከፉጡማ
ቀደም ብለው ወደ ክርስትናው ገብተዋል፦እንድሪስ መሐመድና አይሻ መሐመድ ናቸው፡፡ እግዚአብሔር ይመስገን ቀጣይ አንግዶቼ ይሆናሉ፡፡
የፋጡማ አዲስ ስሞ" ናርዶስ ጂብሪል"
"ስመ ክርስትናዋ ወለተ ሰማዕት"
ምስጋና ፦በአገልግሎት አብረውኝ የነበሩ ቀሲስ ታምራት
መ/ር ኤርምያስ አሰፉ፡ መ/ር መላኩ፣ለሰበካ ጉባኤ
ለሰንበት ትምህር ቤተ መዘምራን ለማህበረ ቅዱሳን፣
ለግርማና ለኡካ ነዋሪዎች ይሁን፡፡አሜን!!!
share በማድረግ ሐይማኖቶን ይመስክሩ፡፡
ለማንኛውም መረጃ ወይም አስተያየት በ Viber- what'sup ቁጥር 0911652083 መልእክት ማስቀመጥ ይችላሉ፡፡ቸር እንሰንብት,,,,

Wednesday, June 10, 2015

የወሊሶ ቤተ ሳይዳ ደብረ ምጥማቅ ቅድስት ማርያም ገዳም

በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ምእመናን የተፈወሱባት የወሊሶ ቤተ ሳይዳ ደብረ ምጥማቅ ቅድስት ማርያም ገዳም ቅዳሴ ቤት ይከበራል አትም ኢሜይል
ግንቦት 8 ቀን 2007 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ
01w
በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት በወሊሶ ከተማ የምትገኘው የቤተ ሳይዳ ደብረ ምጥማቅ ቅድስት ማርያም ገዳም ሕንፃ ግንባታ ተጠናቅቆ ቅዳሴ ቤቱ ግንቦት 20 እና 21 ቀን 2007 ዓ.ም. ቅዱስ ፓትርያርኩ፤ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ምእመናን በተገኙበት በድምቀት እንደሚከበር የገዳሙ አስተዳደር ገለጸ፡፡
የወሊሶ ቤተ ሳይዳ ደብረ ምጥማቅ ቅድስት ማርያም ገዳም በ1971 ዓ.ም. በብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የተመሠረተች ሲሆን፤ በ1996 ዓ.ም. በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ የመሠረት ድንጋይ ተቀምጦ የሕንፃ አሰሪ ኮሚቴ በማዋቀር ግንባታው ቢጀመርም በተለያዩ ምክንያቶች ግንባታው ዘግይቶ በዐሥር ዓመቱ ሊጠናቀቅ እንደቻለ አስተዳሩና የሕንፃ አሰሪ ኮሚቴው ገልጸዋል፡፡

የቤተ ክርስቲያኑን ዲዛይን በማኅበረ ቅዱሳን ባለሙያዎች ተሰርቶ ቀድሞ የነበረውን ዲዛይን በድጋሚ ማስተካከያ በማድረግ የወረዳ ማእከሉ ባለሙያዎች በቅርበት እየተከታተሉት ለሁለተኛ ጊዜ በተዋቀረው ሕንፃ አስሪ ኮሚቴ አማካይነት ሊጠናቀቅ ችሏል፡፡

01ww01wy
የገዳሙ መሥራች የሆኑት ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ /መምህር ወልደ ትንሣኤ ግዛው/ የሕይወት ታሪካቸው እንደሚያስረዳው መጋቢት 21 ቀን 1911 ዓ.ም. በቀድሞው በተጉለትና ቡልጋ አውራጃ ኢቲሳ ደብረ ጽላልሽ የተወለዱ ሲሆን፤ በ1921 ዓ.ም. ከግብፃዊው ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ዲቁና፤ ነሐሴ 24 ቀን 1933 ዓ.ም. በደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳም ምንኩስናን፤ በ1940 ዓ.ም. በታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም ከኢትዮጵያዊው ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ ቁምስና፤ ግንቦት 30 ቀን 1979 ዓ.ም. በብፁዕ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ኤጲስ ቆጶስ ሆነው ተሹመዋል፡፡
በአዲስ አበባ በቀጨኔ መድኃኔዓለም፤ በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም፤ በመናገሻ ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ፤ በድሬደዋ ቅዱስ ሚካኤል፤ በሐረርጌ ሀገረ ስብከት ጅጅጋ፤ ኦጋዴን እና አሰበ ተፈሪ ካገለገሉባቸው አድባራትና ገዳማት ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡ በ1946 ዓ.ም. ወደ ቀድሞው ጨቦና ጉራጌ አውራጃ፤ በአሁኑ ደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ወሊሶ /ግዮን/ ከተማ በመምጣት አሁን ገዳሙ በሚገኝበት ቦታ ላይ መሬት በመግዛት አዳራሽ ሠርተው ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ጸጋ በአጋንንትን የተያዙ ሕሙማን እየፈወሱ ቆይተዋል፡፡ አገልግሎታቸው ወደ ቀድሞው ንጉሥ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ በመድረሱ የያዙትን ቦታ አስፍተው እንዲያገለግሉ መሬት እንዲሰጣቸው አድርገዋል፡፡

በ1971 ዓ.ም. የሚያገለግሉበት አዳራሽና ሰፊውን ቦታ በደርግ እንደሚነጠቁ የተረዱት ብፁዕነታቸው በሚያገለግሉበት አዳራሽ ጽላት በማስገባት ቤተ ክርስቲያኗ ተመሠረተች፡፡

01www01wwww
ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ ከ10 ሚሊዮን በላይ ከኢትዮጵያ እና ከመላው ዓለም በአጋንንት የተያዙ ሕሙማንን ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ሀብተ ፈውስ እንደፈወሱ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡

ብፁዕነታቸው ጥር 18 ቀን 1989 ዓ.ም. ዐርፈዋል፡፡
ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ ግንቦት 20 እና 21 ቀን 2007 ዓ.ም. በቅዱስ ፓትርያርኩ ተባርኮ ጽላቱ የሚገባ ሲሆን፤ ዓመታዊ የእመቤታችን የንግስ በዓል በድምቀት እንደሚከበር ኮሚቴው አስታውቋል፡፡
ምእመናን በዚህ ታሪካዊና የእግዚአብሔር ድንቅ ሥራ ሲከናወንበት በነበረው ገዳም ተገኝተው የበረከቱ ተሳታፊ እንዲሆኑ የገዳሙ አስተዳደርና ሕንፃ አስሪ ኮሚቴ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

Monday, June 8, 2015

እሙሀይ ብርሐን - ዲማ ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም

በዲማ ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም 【በቤተክርስታን ቅፅር ግቢ ውስጥ የሚኖሩት 】እሙሀይ ብርሐን እናታችን የተሰጣቸው ፀጋ በጣም ለሰሚው ጆሮ በጣም ሊከብድ ይቻላል እናታች በቤተክርስታን ቅፅር ጊቢ መኖር ከጀመሩ ከ30 ዘመናት በላይ ሆኗቸዋል በነዚህ ዘመናት ባዶ ሜዳ ላይ ተቀምጠው ☞ ዝናብ ሲዘንብ እሳቸው የተቀመጡበት ቦታ ደረቅ ሆኖ እሳቸውንም ሆነ የተቀመጡባትን አካባቢ ዝናብ አያገኘውም እሙሀይ በዚህ ሲኖሩ የሚመገቡት ቱልት የተባለውን ቅጠል ሲሆን እናታችን ብዙ ተማዕራትን በተለያየ ግዜ ሲያደርጉ በአካባበው ምዕመናን ታይተዋል ከዚህ አልፎ በዋልድባ ገዳም የሚኖሩ አባቶች ከሰማይ በቀስተደመና አምሳል ከሰማይ ብርሐን ሲወርድላቸው አይተው መጥተው የእሙሀይን በረከት በረከትዎ ይድረስብን እናታችን ብለው እጅ ነስተዋል የእናታችን በረከት በጣም አስገራሚ እና አስደናቂ ነው እሰኪ ሁላችንም የእሙሀይ ብርሐን በረከት በየአለንበት ይድረሰን እሙሀይንም በቦታው ተገኝተን የበረከቷ ተካፍይ ያድርገን።