Tuesday, August 11, 2015

ጉዞ ከፕሮቴስታንት ወደ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ (ምስክርነት)

እህታችን የፕሮቴስታንትን ድርጅት ሃይማኖቷ እንዲሆን እና ድርጅቱን እንድትከተል የሆነበት ምክንያቱ እንዲህ ነው….. በእንጀራ አባቷ ጓደኛ ምክንያት በመታለል ሲሆን የኦርቶዶክስ ሃይማኖቷን እንድትክድ እና ወደ ፕሮቴስታንት ድርጅት እንድትቀላቀል፤ የፈለገችውን ገንዘብ ያህል እንደሚሰጧት፤ ልብስ፤ ጫማ፤ ትምህርቷን በሰፊው እየከፈሉ ሊያስተምሯት ቃል ገብተው ነበር። እንደወሰዷትም የኑፋቄን ትምህርት ለሦስት አመታት በተከታታይ አስተማሯት፤ ገንዘብም ሰጧት፤ ማህተቧን ከአንገቷ በጥሳ እንድትጥል እና እንድትረግጥ አደረጉ….መላእክትን እንዳትፈራ እንደተራ ነገር እንድትቆጥር አደረጉ፤ ቅዱሳንን ማቃለል ሥራየ ብላ እንድትይዝ አደረጉ፤ እመቤታችንን መዝለፍን አስተማሯት……እንደ ልጅቱ አገላለጽ ወይም በአንደበቷ እንደመሰከረችው ፓስተር ተብየዎች የፕሮቴስታንትን ድርጅት የሚከተሉ ወጣቶች እና እሷን ጭምር ትዳር ከመያዛችሁ በፊት ሴክስ አርት ስለሆነ ኑና እናስተምራችሁ አያሉ ያስቸግሯቸው እንደነበር እና ሌሎችም የተደበቁ የተሐድሶ አጀንዳዎችን በይፋ ነገረችን ….ያሳዝናል። ከእኛ ወገን መስለው ያሉ ነገር ግን ልባቸው መናፍቅ የሆኑ ስንቶችን ዘረዘረቻቸው……..ብቻ የአቡነ ተክለሃይማኖት አምላክ ይጠብቀን…..አጽራረ ቤተክርስቲያንን ያስታግስልን አሜን። መረጃዎችን ለወደፊቱ ለሚከተለው ክፍል እንደምትሰጥ ቃል ገብታለች። እኛም ለመስማትም ለማየትም እንፈልጋለን እንጠብቃለን። የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ቤተክርስቲያናችንን ይጠብቅልን አሜን።
እግዚአብሔር ፈቅዶ ከዚህች የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ የነበረች እህት ጋር ለተወሰነ ቀናት ተነጋግሬ፤ ስህተቷን አምና ወደ ቀደመችው እና ትክክለኛ ሃይማኖቷ እንድትመለስ ምክንያት ብሆንም ይህን ላደረገ የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይገባዋል። ምስክርነቷን ከተጠመቀች በኋላ ነሐሴ 3 ቀን 2007 ዓ.ም ጎንደር አደባባይ አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን ሰጥታለች።

ተአምር በ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ከርስቲያን /ሽሬ/

Monday, August 3, 2015

አቡነ ዳንኤል ዘገዳመ አስቄጥስ

ግንቦት 8-ዕረፍቱ ለአቡነ ዳንኤል ዘገዳመ አስቄጥስ
አቦ ገድሉ ከማር የሚጣፍጠውን የዚህን ታላቅ ጻድቅ ታሪክ ያንብቡና ነፍስዎትን እርክት ያድርጉ!
አቡነ ዳንኤል በመቃርስ ገዳም በደብረ ሲሐት ይኖር የነበረ ሲሆን እርሱም እጅግ ገድለኛ አባት ነው፡፡ 40 ዓመት በአስቄጥስ ገዳም ሲኖር ከቅጠል በቀር ተመግቦ አያውቅም፡፡ በአስቄጥስ ገዳም ዜናው ሁሉ በዓለም በተሰማ ጊዜ የነገሥታት ልጆችም ወደ እርሱ እየመጡ እየተባረኩ ይሄዱ ነበር፣ ግማሾቹም በዚያው ይመነኩሱ ነበር፡፡ ይህም አባ ዳንኤል ስሟን እንጣልዮስ አስብላ የነበረች ንግሥት የነበረችውን ቅድስት በጥሪቃን የገነዛት ነው፡፡ እርሷም ወንድ የነበረች ሲሆን ይህም የታወቀው ከሞተች በኋላ ነው፡፡ አውሎጊስ የሚባለውን የወፍጮ ድንጋይ እየወቀረ በመሸጥ ለድኆች የሚመጸውትን ጻድቅ ሰው ዋስ እሆነዋለሁ በማለት ከእግዚአብሔር ዘንድ ለምኖ ሥልጣንና ብዙ ወርቅ እንዲያገኝ ያደረገው ይህ አባ ዳንኤል ነው፡፡ በኋላም አውሎጊስ ሀብቱና ንብረቱ ከእግዚአብሔር የሚያርቀው ቢሆን አባ ዳንኤል በጸሎቱ መልሶ ሀብቱን እንዲያጣ አድርጎታል፡፡ አውሎጊስ የሚባል ጻድቅ የወፍጮ ድንጋይ እየወቀረ (እየጠረበ) በመሸት የሚየገኘውን ለድኆችና ጦም አዳሪዎች ይመጸውት ነበር፡፡ አባ ዳንኤልም የአውሎጊስን መልካም ሥራ ተመልክቶ እጅግ ደስ ብሎት ለአውሎጊስ የሀብቱን መጠን እንዲጨምርለትና ይበልጥ እንዲመጸውት በማሰብ ወደ እግዚአብሔር በጸሎት አሳሰበ፡፡ ለአውሎጊስም ዋስ ሆነውና ሀብቱ ተጨመረለት፡፡ አንድ ቀን የሚወቅረውን ድንጋይ ሲፈቅል በሸክላ ዕቃ የተደፈነ ሙሉ ወርቅ አገኘ፡፡ ወደ ቁስጥንጥንያም ከተማ ሄዶ ለንጉሡ አስረከበና የንጉሡ የሠራዊት አለቃ ሆኖ ተሾመ፡፡ ከተሾመም በኋላ የቀድሞውን የጽድቅ ሥራውን ተወ፡፡ አባ ዳንኤልም ስለ እርሱ ሰምቶ ሊያየው ቢሄድ በፈረስ ላይ ተቀምጦ በሠራዊት ታጅቦ በትዕቢት ተመልቶ አገኘው፡፡ ክፉ የትዕቢት መንፈስ አድሮበት ነበር፡፡ አባ ዳንኤልም አውሎጊስ ሀብት እንዲያገኝ በመለመኑ አዘነ፡፡ በሌሊትም የአውሎጊስ ነፍስ በእርሱ ምክንያት እንደጠፋች ራሱ አባ ዳንኤልም ሲሰቀልና እመቤታችን ስለ እርሱ ስትማልድ ራእይ አየ፡፡ ከእንቅልፉም በቃ ጊዜ የአውሎጊስ ሀብት እንዲጠፋና ወደ ቀደመ ግብሩ እንዲመለስ በጾም ጸሎት ሱባኤ ያዘ፡፡ መልአክም ተገልጦለት በእግዚአብሐር የፍርድ ሂደት ውስጥ ጣልቃ በመግባቱ ከገሠጸው በኋላ አውሎጊስም ምሕረት እንደሚያገኝ ነገረው፡፡ አውሎጊስን የሾሸመው ንጉሥም ሞተና ሌላ ንጉሥ ነገሠ፡፡ አውለጊስንም ንብረቱን ሁሉ ቀምቶ ነፍሱንም ለመግደል አሳደደው፡፡

አውሎጊስም ነፍሱን ለማዳን ሽሽቶ ወደ ሀገሩ በመግባት የቀድሞ ሥራውን መሥራት ጀመረ፡፡ ነዳያንንም እንደዱሮም መመገብ ጀመረ፡፡ አባ ዳንኤል ከታለቁ ጻድቅ ንጉሥ ከቅዱስ አኖሬዎስ ጋር የተገናኘ ታሪክ አለው፡፡ ይኸውም አባ ዳንኤል 40 ዓመት ሙሉ በአስቄጥስ ገዳም ሲኖር ከቅጠል በቀር ተመግቦ አያውቅም ነበርና ከጽድቁና ከብቃቱ የተነሣ ከብዙ ዘመን በኋላ የመመካት ክፉ ሀሳብ መጣበት፡፡ ‹‹በገዳም ውስጥ እንደእኔ ትርሕምትን ገንዘብ ያደረገ ይኖር ይሆን?›› ብሎም አሰበ፡፡ ሰውን ወዳድ የሆነ ጌታችንም ይህን ክፉ ሀሳቡን ሊያርቅለት ሽቶ ብርሃናዊ መልአኩን ላከለት፡፡ መልአኩም አባ ዳንኤልን ስለ ትምክህቱ ቢቆጣውም አባ ዳንኤል መልአኩን መልሶ ‹‹ጌታዬ ከእኔ የሚሻል ካለ ንገረኝ፣ ወደ እርሱ ሄጄ አየው ዘንድ እወዳለሁ፣ በመመካቴም ወደ ፈጣሪዬ በልመና እመለስ ዘንድ›› አለው፡፡ መልአኩም ‹‹እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው የሮሜና የቁስጥንጥንያ ንጉሥ አኖሬዎስ በመንግሥተ ሰማያት ባልንጀራህ ነው›› አለው፡፡ ‹‹ንጉሥ አኖሬዎስም የመነኮሳትን ሥራዎች ሁሉ ስለሚሠራ ከልብሰ መንግሥቱ ሥር በሥጋው ላይ ማቅ ይለብስ ነበር›› ተብሎ በስንክሳሩ ላይ የተጻፈለት ጻድቅ ንጉሥ ሲሆን ሰማያውያን የሆኑ ቅዱሳን መላእክትም ቅድስናውን የመሰከሩለት በንግሥና ያለ ታላቅ የእግዚአብሔር አገልጋይ ነው፡፡ አባ ዳንኤልም ይህ በሰማ ጊዜ መሬት ላይ ወድቆ በራሱም ላይ አመድ ነስንሶ የዚህን የሮም ንጉሥ አኖሬዎስን ግብር ያሳየው ዘንድ ጌታችንን ለመነ፡፡ ደመናም መጥታ ነጥቃ ወሰደችውና ንጉሥ አኖሬዎስ ደጅ አደረሰቸውና ንጉሡን በዙፋኑ ላይ ሆኖ ባየው ጊዜ ከግርማው የተነሣ አይቶት በታላቅ ፍርሃት ውስጥ ሆኖ ከእግሩም በታች ሰገደለትና አኗኗሩንም ይነግረው ዘንድ በጌታችን ስም አማፀነው፡፡ ንጉሥ አኖሬዎስም ሰሌን በመታታት በእጅ ሥራው ደክሞ ከሚያገኘው በቀር ምንም ሳይበላና ሳይለብስ 40 ዓመት እንደሆነው፣ ሰሌን ታቶ ሸጦ ካገኘውም ውስጥ ከዕለት ምግቡ መግዣ የሚተርፈውን ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች እንደሚመጸውት፣ ምግቡም እንጀራና ጨው፣ ቅጠል መጻጻም እንደሆነ፣ የማንንም ንብረት ፈጽሞ እንዳልንካ፣ ድንግልናውንም ጠብቆ እንደሚኖር ነገረው፡፡ አባ ዳንኤልም ድጋሚ ከእግሩ ሥር ወድቆ ሰግዶለት ስለ ትምክህቱም ፈጽሞ እያዘኑ ወደ በዓታቱ ተመልሷል፡፡ አባ ዳንኤል አንድ ቀን ከረድኡ ጋር ወደ እስክንድርያ ሲጓዝ ስሙ ምህርካ የሚባል እብድ አገኘ፡፡ ብዙ እብዶችም ይከተሉት ነበር፡፡ እርሱም ለአገሩ ሰዎች ሁሉ በእውነት ያበደ ይመስላቸው ነበር፡፡ አባ ዳንኤልም እጁን ይዞ ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ወስዶ ትሩፋቱን ተጋድሎውን ነገረው፡፡ ከሊቀ ጳጳሳቱም ጋር ሆነው እብዱን ስለራሱ እንዲነግራቸው በእግዚአብሔር ስም ባማሉት ጊዜ ከዝሙት ጦር በመሸሽ ራሱን እብድ እንዳስመሰለ ነገራቸው፡፡
አንድ ቀን አባ ዳንኤል በሌሊት በበረሃ ውስጥ በጨረቃ ብርሃን ሲጓዝ በተራራ ላይ ተቀምጣ ጠጉሯ መላ ሰውነቷን የሸፈናት በዚያም በረሃ ስትኖር በተሰነጠቀ ዓለት ውስጥ 38 ዓመት ብቻዋን ማንም ሳያያት የኖረች ጻድቅ እናት አግኝቶ ምሥጢሯን ሁሉ ነግራዋለች፡፡ እርሷም ቅድስት አመተ ክርስቶስ ናት፡፡ አባ ዳንኤልም 38 ዓመት ሙሉ በዚህ በረሃ ምንም ሰው ሳታይ የኖረችበትን ተገድሎዋን በዝርዝር ነግራቸዋለች፡፡ እርሳቸውም ወደ ገዳማቸው ተመልሰው ለአበ ምኔቱና ለመነኮሳቱ ታሪኳን በመንገር ልብስ ይዘውላት ቢመጡ ዐርፋ አግኝተዋታል፡፡
አባ ዳንኤል የልዮንን የክህደት ደብዳቤ ወታደሮቹ አምጥተው በመነኮሳቱ ፊት ሲያነቡ ደብዳቤውን ተቀብሎ በሕዝቡ ፊት ቀዶታል፡፡ ወታደሮቹም አባ ዳንኤልንደብደበው ከገዳሙም አሳደውታል፡፡ ብዙ ሥቃይም አድርሰውበታል፡፡ አባ ዳንኤል በአንዲት ዕለት ከደናል ገዳም ደርሶ ደጁን አንኳኳ፡፡ እነርሱም አባ ዳንኤል መሆኑን ዐውቀው ከፈቱለት፡፡ አንዲት ሴትም ራሷን ዕብድ አስመስላ በደጅ የምትተኛ ሴት ነበረች፡፡ እርሱም ዕብድ መስላ በደጅ ስለተቀበጠችው ሴት አበምነቷን ሲጠይቃት እብድ መሆኗን ነገረችው፡፡ አባ ዳንኤል ግን ዕብድ የመሰለቻቸው ሴት እብድ ሳትሆን በድብቅ በታላቅ ተጋድሎ የምትኖር ቅድስት ሴት መሆኗን ነገራት፡፡ ዕብድ የተባለችውም ሴትም አባ ዳንኤል ምሥጢሯን እንደገለጠባት በስውር ዐውቃ ወዲያው ደብዳቤ ጽፋ ይኸውም ‹‹የተከበራችሁ እኅቶቼ ስላስቀየምኳችሁና ስላሳዘንኳችሁ ይቅር በሉኝ›› ብላ ጽፋ ደብዳቤውን አስቀምጣ ጥላቸው ጠፋች፡፡ እነርሱም ከዚያ በኋላ ዳግመኛ አላዩአትም፡፡ ደናግል ወደሚኖሩበት ገዳም አንድ የወንበዴዎች አለቃ ሰይጣን አነሳስቶት ወደ ገዳሙ በአባ ዳንኤል ተመስሎ ቆቡን ደፍቶ በሩን አንኳኳ፡፡ ደናግላኑም ሊዘርፋቸው መምጣቱን ምንም ባለማወቅ ይልቁንም አባ ዳንኤል መጣ ብለው በሩን ከፈቱለትና አስገቡት፡፡ እግሩንም አጥበው ለበረከት ብለው የእግሮቹን ዕጣቢ በፊታቸው ላይ ረጩት፡፡ ከመካከላቸውም አንዷ ዐይነ ሥውር ነበረችና ዐይኗ ወዲያው በራላት፡፡ በዚህም ደናግሉ እጅግ ተደስተው ‹‹አባ ዳንኤል አንተ ንዑድ ክቡድ ነህ›› ብለው ሰገዱለት፡፡ ይህን ጊዜ የሽፍቶቹ አለቃ በጣም ደንግጦ በመጸጸት ወደ አባ ዳንኤል ዘንድ ሄዶ ያደረገውን ሁሉ በመናገር ንስሓ ገባ፡፡ መንኩሶም በታላቅ ተጋድሎ መኖር ጀመረ፡፡ እርሱም ተአምራት እስከማድረግ ደርሶ በሰላም ዐረፈ፡፡ የአባ ዳንኤልም ተጋድሎና ተአምር ምን ቢጽፉት የሚያልቅ አይደለም፡፡ ዕረፍቱም በደረሰ ጊዜ ጌታችን ታላቅ ቃልኪዳን ሰጥቶት ቅድስት ነፍሱን ወደ እርሱ ወስዷታል፡፡ ዕረፍቱም ግንቦት 8 ቀን በታላቅ ክብር ተፈጽሟል፡፡
በረከቱ ይደርብን! ምልጃው ከይለየን አሜን!!!
ስምን ስም ያነሳዋልና በዚሁ አጋጣሚ ኢትዮጵያዊውን ጻድቅ የትግራይ ገርዓልታውን አቡነ ዳንኤልንም ይወቋቸው፡፡ አቡነ ዳንኤል ዘገርዓልታ አባታቸው መልክአ ሥላሴ እናታቸው ዓመተ ጽዮን ሲባሉ የትውልድ ሀገራቸው ትግራይ ገርዓልታ ነው፡፡ በ7 ዓመታቸው የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ተምረው አጠናቀው በ13 ዓመታቸው መነኮሱ፡፡ ሊቃውንቱ ‹‹ማኅቶተ ገዳም›› እያሉ የሚጠሯቸው ገድለኛ አባት ናቸው፡፡ አስገራሚው ባለ 4 ዓምዱና 40 ያሸበረቁ ሥዕላት ያሉት አስደናቂው ገድላቸው የት እንዳለ አይታወቅም፣ እኛ ሀገር ገድላቸው የለም፡፡ 2ኛውን ገድላቸውን ፖርቹጋሎች ከጠባቂው ገዝተው ወስደው በሀገራቸው አሳትመውታል፡፡ ገድሉን የሸጠው ጠባቂም ሆዱ ተነፍቶ በስብሶ ተልቶ ከቤተ ክርስቲያኑ በራፍ ላይ ወድቆ ሞቷል፡፡ የጻድቁ የዕረፍታቸው ዕለት ኅዳር 6 ቀን ትግራይ በሚገኘው ገዳማቸው በደማቅ ሁኔታ ይከበራል፡፡ ገዳማቸው የሚገኘው እጅግ ከፍተኛ ተራራ ላይ ሲሆን ከላይ ሆነው ወደታች ሲመለከቱ መሬት የሚደረስባት አትመስልም፡፡ እስቲ ከፎቶው ላይ ይመልከቱት!
(ምንጭ፡- የታኅሣሥና የግንቦት ወር ስንክሳር;መለከት 14ኛ ቁ5-1998 ዓ.ም፣ የቅዱሳን ታሪክ-108 &166)

አባ ዮሐንስ ተስፋ ማርያም - የወንቅሸት ቅዱስ ገብርኤል አንድነት ገዳም

አባ ዮሐንስ ተስፋ ማርያም የወንቅሸት ቅዱስ ገብርኤል አንድነት ገዳም አበምኔት፤፤ አባ ዮሃንስ ተስፋ ማርያምን ማነጋገር ከፈለጉ ፡ከዚህ ዌብሳይት ሂደዉ www.wonkshet.com ኮንታክት አስ ከሚለው ላይ ኢሜይል ያርጉልንና ስልካቸውን እንልክልዎታለን፤፤
This is the testimony at Wonkshet Adame Yordanos Kidus Gabriel Monastery by Aba Yohannes Tesfamaryam. For more information, visit www.wonkshet.com

Wednesday, July 22, 2015

አባ ገዐርጊ

ግንቦት 18-ጌታችን መልአኩን ልኮ ‹‹ተጋድሎህ በመጠን ይሁን›› በማለት ተጋደሎውን እንዲቀንስ ያዘዘው የአባ ገዐርጊ ዕረፍት ነው፡፡
ጻድቁ የክርስቲያን ወገን ሲሆን ወላጆቹም ደጋግ ቅዱሳን ጻድቃን ናቸው፡፡ በአደገም ጊዜ የወላጆቹን በጎች የሚጠብቅ እረኛ ሆነ፡፡ ነገር ግን እርሱ የምንኩስናን ልብስ ይለብስ ዘንድ በልቡ ይመኝ ነበር፡፡ 14 ዓመትም በሆነው ጊዜ የእግዚአብሔር ጸጋ አነሳሳችውና በጎቹን ትቶ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔደ፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣል›› እንዳለው (2ኛ ቆሮ 11፡14) አባ ገዐርጊ ወደ ገዳሙ እየተጓዘ ሳለ በሽማግሌ አምሳል ከይሲ ሰይጣን ተገለጠለትና ከዓላማው ሊያደናቅፈው ፈተነው፡፡ እንዲህም አለው ‹‹ልጄ ሆይ ስለ አንተ አባትህ ልብሱን ቀዶ አየሁት፣ የዱር አውሬ ነጥቆ የበላህ መስሎት አባትህ ያዝናል፣ ያለቅሳል፡፡ ተመልሰህ የአባትህን ልብ ልታጽናና ይገባሃል›› አለው፡፡ አባ ገዐርጊም ደንግጦ አንድ ሰዓት ያህል ሳይንቀሳቀስ ቆመመ፡፡ ከዚህም በኋላ የከበረ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቅዱስ ወንጌሉ ‹‹ከእኔ ይልቅ አባት እናቱን የሚወድ ለእኔ ሊሆን አይባውም ደቀ መዝሙሬም ሊሆን አይችልም›› ብሏል ብሎ አሰበ፡፡ ማቴ 10፡37፡፡ ይህንንም ባሰበ ጊዜ ሰይጣን እንደጢስ ሆኖ ተበትኖ ጠፋ፡፡ አባ ገዐርጊም ሰይጣን እንደሆነ ዐወቀ፡፡ ‹‹በመጠን ኑሩ ንቁም፣ ባላጋራችሁ ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና ለእግዚአብሔር ተገዙ፣ ዲያብሎስን ግን ተቃወሙ ከእናንተም ይሸሻል›› 1ኛ ጴጥ 5፡8፣ ያዕ 4፡7፡፡

በዚያን ጊዜም አስቀድሞም ተገልጦለት የነበረው የብርሃን ምሰሶ ተገለጠለት፣ የእግዚአብሔርም መልአክ በመነኩሴ አምሳል ተገለጠለትና አብሮት ተጓዘ፡፡ መልአኩም አባ ገዐርጊን አባ አርዮን ገዳም አደረሰው፡፡ አባ ገዐርጊም ጽኑ ተጋድሎውን ጀመረ፡፡ በገዳሙ 14 ዓመት በታላቅ ተጋድሎ ሲኖር እህል አይቀምስም ውኃም አይጠጣም ነበር፡፡ ለ14 ዓመትም ከመቀመጥ በቀር ምንም አልተኛም፡፡ ከዚህም በላይ ተጋድሎውን በጨመረ ጊዜ እግዚአብሔር መልአኩን ልኮ ‹‹በመጠን ተጋደል›› ብሎታል፡፡ መልአኩም ተገልጦለት ‹‹‹ሥጋህ እንዳይደክም በመካከለኛ ተጋደል› ብሎሃል ጌታ›› ካለው በኋላ ሊሠራው የሚገባውን ሥርዓት ሠራለት፡፡ ሁልጊዜም እስከሚመሽ እንዲጾም፣ ትንሽም እንጀራን እንዲበላ፣ ከእራት ሰዓት እስከ መንፈቀ ሌሊት ስለሥጋው ዕረፍት እንዲተኛ በቀረው ሌሊት እስቲነጋ ተግቶ እንዲጸልይ ሥርዓት ሠራለት፡፡
መልአኩ በሠራለት በዚህ ሥርዓት ብዙ ዘመን ሲጋደል ከኖረ በኋላ በበረሃ ውስጥ ብቻውን ወሊኖር ወዶ በጫካ ውስጥ እየተመላለሰ ሁለት ዓመት ተቀመጠ፡፡ ነገር ግን ጌታችን ተገልጦለት ወደ ቀደመ ቦታው እንመለስ አዘዘው፡፡ ደብሩም ከከበሩ መክሲሞስ ዱማትዮስ ገዳም አጠገብ ነበር፡፡ ወደ ደብሩም በተመለሰ ጊዜ አብርሃም ከተባለ ደገኛ ቅዱስ ጋር ተገናኙና ሁለቱም በጋራ ለመኖር ተስማምተው ወደ አስቄጥስ ገዳም አበ ምኔት ወደ አባ ዮሐንስ ዘንድ ሄዱ፡፡ እርሱም ቦታ ሰጥቷቸው በውስጧ በተጋድሎ መኖር ጀመሩ፡፡ ያችም ቦታ እስከዛሬ ታውቃ ትኖራለች፡፡ ስሟም በግቢግ ትባላለች፡፡ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጣሪያዋን ሰንጥቆ ወደ እነዚህ ሁለቱ ቅዱሳን የወረደባት ናት፡፡ እነርሱም በክብር ሰገዱለት፡፡ ጌታችንም ባርኳቸውና አጽናንቷቸው ዐረገ፡፡ በዚያችም ጌታችን በወረደባት መስኮት ብርሃን ተመለከቱ፡፡ እስከዛሬም ድረስ የተከፈተች ሆና ትታያለች፡፡ እነዚህም ሁለት ቅዱሳን (አባ ገዐርጊና አባ አብርሃም) ለመኮሳት የሚሆኑ ብዙ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሱ፡፡ ከዚህም በኋላ አባ አብርሃም ጥር 2 ቀን ዐረፈ፡፡ ከእርሱም በኋላ አባ ገዐርጊ በ72 ዓመቱ ግንቦት 18 ቀን ዐረፈ፡፡
የአቡነ ገዐርጊ ምልጃና በረከቱ በምልጃው በምንታመን በሁላችን ላይ ይደርብን! አሜን!!!
(ምንጭ፦ የግንቦት ወር ስንክሳር)