Thursday, August 20, 2015

ፖርት ሳይድ ማርያም በግብጽ

ከስዕልዋ ዘይት የሚፈልቅበት ተአምር አድራጊዋ የእመቤታችን ስዕል ፖርት ሳይድ ማርያም በግብጽ; በረከትዋ ይደርብን:: መጋቢ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ




ከእጇ ዘይት የሚፈልቅ የቅድስት ኤልሳቤጥ አስገራሚ ታሪክ

Tuesday, August 18, 2015

አቡነ ሐራ ድንግል ገድል



ከሁሉ አስቀድመን የአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንልጆች የሆን እኛ የክርስቶስ ወገኖች ሰዎች ነገርን ከማብዛት በማሳነስ ነገርን ከማስረዘም በማሳጠር ክቡርና ልኡል ትሩፋቱ ፍፁም ገድሉም ብዙ የሆነ ምስራቃዊ የክብር ኮከብ አርያማዊ የፅድቅ ጸሀይ የኦርቶዶክሳዊ ሀይማኖት ዓምድ የመንፈሳዊ ምግባርማደሪያ የሆነየአባታችን ሐራ ድንግልን ገድሉንና ትሩፋቱን የፅድቁንም ስራ እንጽፍ ዘንድ ህይወትን ሰጪ በሚሆን በባታዊ አድሮ በሚኖር ገዳማዊውን በሚጎበኝ የአለማዊውንም ሰው በደል በመለኮታዊ ስልጣኑ በሚያስተሰርይ በአምላክ ፈቃድ ለመጀመር ተግተን ተመኘን፡፡ ለሁላችንም የጥምቀት ልጆች ከኦሪታዊው ከሙሴና ከወንጌላዊው ከዮሀንስ ጋር አሸናፊ እግዚአብሄርን በቀናች ሀይማኖትና በመልካም ምግባር ካገለገሉት ከጻድቃንና ከመነኮሳትም ጋር ሰማያዊ የነፍስ ደስታ እድልን ያድለን ክብር ምስጋና ለእርሱ ይሁን ለዘላለሙ አሜን፡፡ አቡነ ሐራ ድንግል አስቀድመን በመጻፋችን የጠራነው የዚህ ጻድቅ አባቱና እናቱ በላጉና ምድር ይኖሩ ነበር ፡፡ እርስዋም ከደራ ምድር አንድ ክፍል ናት:: አባቱም ዮሐንስ የሚባል የሬማ ቄስ ነበር:: እናቱም ወለተ ጊዮርጊስ ትባል ነበር ሁለቱምበወገን ከከበሩ ቤተሰቦች ነበሩ እነርሱም ጻድቃንና ደጋግ ሰዎች እግዚአብሄርን የሚፈሩ ነበሩ ከክፋትም ስራም ሁሉ የራቁ ነበሩ በበጎ ምግባርም ሁሉ የጸኑ ነበሩ ሶስት ወንዶች ልጆች ነበሯቸው ከእነርሱም አንዱ የአለም መብራት የኢትዮጵያ ብርሀን ሐራ ድንግል ነበር ይህንም ገድለኛ ልጃቸውን ከመውለዳቸው አስቀድሞ ገንዘባቸውን ለድሆችና ለጦም አዳሪዎች ለባልቴቶችና ለሙት ልጆች ለካህናትና ለምእመናን ለህዝበ ክርስቲያኑ ሁሉ ይሰጡ ነበር :;ይህንም ያደርጉ ነበር ስጡ ይሰጣችኋል ዳግመኛም ለሌለው ይስጥ የሚለውን የወንጌል ቃልና ሌላውም መጽሀፍ ካለህ ስጥ ከሌለህም እዘን የሚለውን ቃል አስበው ነው:: በዚህም ነገር ላይ እንዲህ እያሉ ይጸልዩ ነበር አንተን ደስ የሚያሰኝ ፈቃድህንም ሁሉ የሚያደርግ በደግነቱም ለፍጥረትህም ሁሉ የሚጠቅም ሰሎሞን:-ብልህልጅ አባቱን ደስ ያሰኛል ሰነፍ ልጅ ግን እናቱን ያሳዝናል ብሎ እንደተናገረ የእኛንም ልብ ደስ የሚያሰኝ ጠቃሚ ልጅ ስጠን ጸሎትም እንደሚጠቅም ከቅዱሳት መጻህፍት ምሳሌ አግኝተው ይህን ሁሉ ጸሎት ጸለዩ:: ሀና በአንደኛ መጽሀፈ ነገስት ለሚጸልይ የጸሎትን መልስ ይሰጠዋል የጻድቃኑንም እድሜ ያረዝማል ብላለች ዳዊትም:-66 መዝሙር መንገድህን ለእግዚአብሄር ግለጥ በእርሱ ታመን እርሱም ያደርግልሀል ብሏል፡፡

ከዚህም በኋላ እግዚአብሄር ጽሎታቸውን ልመናቸውንና እንደ ጣፋጭ ዕጣንና እንደ ንጹህ መሥዋዕት በተቀበላቸው ጊዜ በዚያች ዕለት በጋብቻ ስርአት ተገናኙ ሁለቱም በንጽህና ሐብል የታሰሩ ነበሩና ዝሙትንና ሀጢያትንም አያውቁም ነበርና ነገር ግን :-ወንድ ሁሉ በሚስቱ ጸንቶይኑር ሚስትም በባልዋ ጸንታ ትኑር በሚለው የመጽሀፍ ስርዓት እርስ በርሳቸው ይጠባበቁ ነበር፡፡ በዚያችም በተገናኙባት እለትም ወለተ ጊዮርጊስ መልካም ስራው እንደጸሀይ አወጣጥ የሚያበራ የኢትዮጵያ ብርሀን ሐራ ድንግልን ጸነሰችው ከጸነሰችውም በኋላ በዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በንጉስ አጽናፍ ሰገድ ወለደችው:እርሱንም በወለደች ጊዜ እጅግ ደስ አላት አባቱና ዘመዶቹም እጅግ ደስ አላቸው ሀሴትም አደረጉ ሃጥአንን በእግዚአብሄር ዘንድ በጸሎቱ የሚያስምራቸውና ዳዊት በ111ኛው መዝሙሩ :-መልካም ዛፍ መልካም ፍሬ ያፈራል ክፉ ዛፍ ግን ክፉ ፍሬን ያፈራል ዛፍ ከፍሬው ይታወቃልና ብሎ እንደ ተናገረ ወላጆቹን በምእመናን ሁሉ አንደበት የሚያመሰግናቸው የተባረክ ልጅ ተወልዶላቸዋልና በአርባኛው ቀንም ይህን ልጃቸውን ሐዋርያት በኢየሩሳሌም አንድ ሆነ እንደ አዘዙትሥርዓት የዚያች ቤተክርስቲያን ወሰዱት ያንጊዜም በጥምቀት ፀጋ የወለደው ስሙን ሐራ ድንግል ብሎ ሰየመው:: ከዝያም በኋላ አባቱና እናቱ ተቅብለው ወደ ቤታቸው ወሰዱት በህግና በሥርዓትም አሳደጉት የሰሎሞንን ቃል አውቀው ቅዱሳት መጽሀፍትን ብሉይ እስክ ሀዲስ የዳዊትንም መዝሙር ለሚያስተምር መምህር ሰጡት ያም ህፃን ቅዱሳት መጽሀፍትን ይሚሉትን አውቆ ስላስተዋለ እስኪያድግና አቅመ አዳም እስኪደርስ ድረስ ለትምህርት የተጋ ሆነ በመምህሩ ፈቃድ የድቁና ሹመት ከጳጳሱ ይቀበል ዘንድ በዚያ ወራት ሄደ የድቁና ሹመትም ተቀብሎ በደስታና በሀሴት በሰላምና በህይወት ወደ መንደሩ ተመልሶ ገባ
የጥበባት ባህርና የቋንቋ ባለቤት ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም የትምህርት ምንጭ ለሆነው ለደቀ መዝሙሩ ለጢሞቴዎስ በላከው መልእክቱ:-የዲያቆናት ንጹሓን ይሁኑ ለጸሎትም የነቁና የተጉ ይሁኑ ብሎ እንደተናገረ በንጽህናና በቅድስና በጸሎትና በጭምተኝነት በፍቅርና በትህትና እግዚአብሄርን ያገለገለው ጀመር፡፡ አባታችን ሐራ ድንግልም በእነዚህ የብሉይና የሐዲስ መጽሀፍት ቃላት ጸንቶ ሲኖር ክቡር ዳዊት 88 መዝሙር ሞትን ሳያይ በህይወት የሚኖር ማነው? ዳግመኛም 143 መዝሙር ሰውስ ከንቱ ይመስላል ዘመኑም እንደ ጥላ ያልፋል ብሎ እንደተናገረ:: በአቤልና በሴት ከተጀመረው ከዚህ ሞት የሚድን ስለሌለ አባቱና እናቱ ከዚህ ዓለም ድካም ዓረፉ ወደ ዘላለም ህይወትም ሄዱ አባታችን ሐራ ድንግልም በወላጆቹ ሞት የመረረ ልቅሶን አለቀሰ አዘነም፡፡ አባታችን ሐራ ድንግልም ከአባቱና እናቱ ሞት በኋላ ሬማ በምትባል ደሴት እየተመለለሰ በቤታቸው ውስጥ ለጥቂት ወራት ተቀመጠ ከሬማም ወደ ዘጌ ይሄድ ነበር ከዘጌም ወደዚያው ወደ ሬማ ይመለስ ነበር እንደዚህ አለም ሰዎችም ሚስት ሊያገባ አልወደደም ነገር ግን በድንግልና ኖረ::ልብሰ ምንኩስናም ሳይለብስ አርባ ዓመት ሆነው ከዚህም በኋላ በጽኑዕ ደዌ ታመመ የንዳድ በሽታም ያዛው ክደዌው ጽናት የተነሳም በስጋውና በነፍሱ ከእግዚአብሄር ፈውስን ያገኝ ዘንድ ልብሰ ምንኩስናን ለመልበስ ወደደ መዓዛ ድንግል የተባለውን የሬማ መምህር ልብሰ ምንኩስናን ይሰጠው ዘንድ ለምኖ ነገረው እርሱም ልብሰ ምንኩስናን አለበሰው ለወጣንያን ለማእከላውያንና ለፍፁማንም መነክኮሳት የሚገባቸውን የምንኩስናን ህግ ሁሉ ሰጠው ከዚህም በኋላ እግዚአብሄርን ከሞት ስላዳነው ከደዌው ተፈወሰ::ከዚህም በኋላ የቅስና ማረግን ከዚያ ጳጳስ ከተቀበለ በኋላ በዚሁ ደስ እያለውናሀሴት እያደረገ ከመንገዱ ተመልሶ ወደ ቤቱ ገባ እግዚአብሄር እርሱ የተመኘውንና የፈለገውን አድርጎለታልና በዚህ ሁኔታ እያለ ወደ አለም መመልስ አልፈለገም ተመልሶ ከዘመዶቹና ከሀገሩ ሰዎች ተሰውሮ ወደ ሸዋ ሊሄድ ወደደ ወደ አሰበበት ለምድረስ በመንገድ ላ ሲሄ ዘመዶቹ ወደ ሀገራቸው ሲመለሱ ያገኙትና ከ እነርሱም አንዱ የወንድሙ ልጅና የልቡ ወዳጅ ስለንበር ሁሉንም ያነሳሳቸው አርከ መርዓዊ ይባላል እነርሱም ግራርያ በተባለ ሀገር ያዙትና ወዴት ትሄዳለህ አሉት እባክህ ወደ ሀገርህ ተመለስ ለሀገርና ለዘመዶችህ የሚቀርብ ገዳም እንፈልግልሃለን አንተም እንዳዘዝከን እንደርጋለን እንጂ ከፈቃድህ አንወጣም አንተ አባታችን ጽድቀህ እኛንም በጽድቅህ እንድታጸድቀን ትሉ ከማያንቀላፋ እሳቱም ከማይጠፋ ከገሀነም እሳት እንድታድነንም እንወዳለንና እንደማንሸነግልህ ም በአምላካችን በ እግዚአብሄር ስም እንምልልሀለን ይሄን ቃላቸውን ከሰማ በኋላ እሺ አላቸው::እንሱም 7 ምሳሮች ይዘው ከቁስቋም ጀምረው ገዳም እስካደረገው ድረስ መንገዱን ይጠርጉ ዛፎችንም ይቆርጡ ጀመሩ ወደ ገዳሙ በደረሱ ጊዜ ማረፊያዬ ይህች ናት በድካሜም ጊዜ የማርፍበት ትንሽ ቤት ስሩልኝ እንጂ ከዚህ ወደ ሌላ አትሂዱ እስከሞቴ ድረስ በ እርሷ እንድኖር እግዚአብሄር አዞኛልናየስጋዬንም በድን እስከ ሙታን ትንሳኤ ድረስ በውስጧ ይኖራል አላቸው በዚያችም ቀን ዕንጨቱን ቆርጠው መሬቱን ቆፍረው አጥር አጠሩለት እርሱንም በገዳሙ ትተውት ወደ ቤታቸው ሄዱ አባታችን ሐራ ድንግልም በተራበ ጊዜ እንጀራ አይበላ ነበር ጥቂት ምስር አተርና አደንጓሬ ይበላ ነበር ብትንሽ ጽዋ መክደኛ ጽዋ ሰፍሮ በትንሽ ድስት ይቀቅለው ነበር ያም በጽዋው መክደኛ ሰባት መስፈሪያ ነበር በሶስት አንድ ቀን ይመገበው ነበር ከምድርም ፍራፍሬም በበላ ጊዜ እሼ የሚባል ፍሬ ይመገብ ነበር ከምናኔው በኋላ ግን ከውሃ በቀር ሌሎች መጠጦችን አልጠጣም ነበር::ያንጊዜም ብዙዎች አራዊት አንበሶች ነብሮች ዝሆኖች ተኩላዎችና ጅቦች የዱር እንስሳዎች ያስፈራሩት ዘን ወደ እርሱ መጡ እርሱ ግን እግዚአብሄር ከእርሱ ጋር ስለነበር ከፊቱ እንዲሸሹ አስፈራርቶ አስደነገጣቸው እንጂ አልፈራቸውም ይህም ነገር ከሆነም በኋላ የቅል ዓይነት ተክልና ወይን ሎሚና ኮክ ተከለ እነዚህንም ተክሎች ከሩቅ ወንዝ ውሃ በእጁ ቀድቶ በትከሻው ተሸክሞ ያጠጣቸው ነበር መንገዱም ሩቅ ስለነበር አባታችን ሐራ ድንግል እንዲህ ብሎ ጸለየ ከ እናቴ ማህጸን ያወጣሀኝ እስከ እዚች ሰአት ያደረስከኝ ፈጣሪዬ እግዚአብሄር ሆይ እስራኤል ከግብጽ በወጡ ጊዜ ሙሴ ከዓለት ውሃን እንዳወጣ ከዚህ ምድር ውሃን አውጣ ዘንድ ጸሎቴንና ልመናዬን ስማኝ ይህን ብሎ በሁለት ረድፎች ምድሩን ቆፈረ በመስቀልም ምልክት ባረካቸው ወዲያውኑ ከሁለቱም ረድፎች ውሃዎች ፈሰሱ በፈለቁት ውሃዎች በየጊዜው እንዲያፈሩና ሊያዩት ወደ እርሱ ለሚመጡት ሰዎች ምግብ እንዲሆኑ እንዚህን ተክሎች አጠጣቸው ለሚልውምኑትም ድሆችም ቅጠሉ ፍሬ ያፈራውን አይነት በገበያ አሽጦምጽዋት ይሰጣቸው ነበር::በዚያ ጊዜም የበጎ ነገር ጠላት ሰይጣን በሴት አምሳል በንጭ ሀር በወርቅበብር በጉትቻዎችና በቀለበቶች አጊጦ መጣና እንዲህ አለው ለምን ብቻህን ትኖራለህ ? ሁለት ሆነው መኖር ሰዎች ልማዳቸው ነውና ከ እኔ ጋር ብትኖር አይሻልህምን? አባታችንም ትቆጣ የ እግዚአብሄርን ቃል በሚጸልይበት በጠበል እቃ የነበረውን ውሃ በሰይጣ ረጨበት ሰይጣንም ድንግጦ ሸሸ በባህርም ስጠመ አባታችን እስኪሰማ ድረስ ባህሩን አወከው አባታችንን ለማሳት ሰባት ጊዜ መጣ ነገር ግን በ እግዚአብሄር ሀይል ድል ተደረገ::
አንዲት ሚዳቆ ነብር እያባረራት መጣች ወደ አባታችን ሐራ ድንግል ቤትም ገብታ በእርሱ ተመአጥና ከ እግሩ በታች ተጋደመች አባታችንም ወደ ፈጣሪው ወደ እግዚአብሄር እየጸለየና እየለመነ ተቀምጦ ነበር ያቺን ሚዳቆ የሚያባርራት ነብርም መጣ አባታችን ወዳለበት ደርሶ በደጁ ቆመ አባታችንንም ባየው ጊዜ ጊዜው ቀን ስለ ነበረ ፈርቶ ወደ ውስጥ አልገባም ያም ነብር ተቆጥቶ በዚያው ቦታ ተፍገመገመ አባታችን ነብሩን ገድለህ ትበላት ዘንድ እግዚአብሄር አልሰጠህም ነብሩም ይህን ነገር ከአባታችን ቃል ሰምቶ ሳይገድላት ሄደ በዚያች ሌሊት በእርሱ ዘንድ አደረች በማግስቱም ከቤቱ ወጥታ በደጅ ስትመላለስ አባታችን ባያት ጊዜ እንዲህ ብሎ አሰናበታት ከቦታሽ አባርሮ ያሳደደሽ ወደ እኔም ያደረሰሽ ያ ነብር ትናንት ስለሄደ ወደ ቦታሽ ሂጂ ይህንም ሰምታ ወደ ቦታዋ ተመለሰች:;
አባታችንም ሁለት ደቀመዝሙሮች ነበሩት ወንዱ እሱን ያዘዘውን የሚፈጽም ነበር ተስፋዬ እና አመተ እግዚእ አለምን ንቃወደ ገዳብ የገባች ነበረች እርሳውም ከአባታችን ቤት ትንሽ በሚርቀው ቤት ተቀምጣ ከምናኔዋ ጀሮ በሞት እስከ ተለየች ድረስ ረዳትና አገልጋይ ሆና ራሷን ለአባታችን ሰጠች እርስዋም በስጋ ዝምድና ከሚቀርቡት አንድዋ ነበረች እርሷም በአገልግሎቷና በታዛዥነቷ እንደዚህ ይሁን የሚለውን ፈቃዱን በመፈጸም እጅግ ደስ አሰኘችው በምግባርዋ ደግ በነገሯም እውነተኛ በልቡናዋም ብልህ ነበረች::
ከዚህም በሃላየአንዲት ታቅ ሴት አሽከሮች ወደ አባታችን መጡ ሊጣሉትም ወደቤቱ ገቡ አንተ ከንጉሱ ፈቃድ ወጥተህ በአመጽ የምትኖር የንጉስ ከዳተኛ አይደለህምን እያልይ ፈጽመው ሰደቡት ከገቡበትም ወጥተው የ አባታችን የወይን ዘለላም ምንም ሳያስቀሩለት ቆረጠው ወሰዱ አባታችንም ምንም አልተናገራቸውም የወሰዱትንም ወይን ለእመቤታቸው የወይኑ ዘለላ ሰጡ እመቤታቸውም ይሀ ወይን ከማን አመጣችሁ ሐራ ድንግል ከሚባለው መንኮስ ነው አላት አንዱንም የሆድ በሽታ ይዞ አንጀቱን ቆረጠው እመቤታቸውም እነዚህን አንተን ያስቀየሙ የበደሉና ማርልኝ ብላ አሽከሮችን ላከች እግዚአብሄር ይቅር የሚላቸውና በደላቸውና የሚተውላቸው ከሆነ ይቅር እላቸዋለሁ አሽከርም በተመለሰ ጊዜ ሆዱን የቆረጠው ሞተ ጻድቁ አባታችንን ስለተሳደበ እግዚአብሄር ትቆጥቶታልና ይህ የሰሙትን የተደረገውን ባዩ ጊዜ አደነቁ:: ይህ ድንቅ ነገር ከሆነ ረዥም ወራት በሃላ አመተ ወልድ የተባለች አንዲት ሴት ታመመች እርስዋም በዚሁ በሽታ ሞተች መላእክተም ሞትም ነፍስ ወሰዱ ያችንም ነፍስ እያጣደፉና እያዳፉ ወደ ፈጣሪዋ አደረሳት በዚች ሰአትም አባታችን ሐራ ድንግል ወደ ፈጣሪው ወደ እግዚአብሄር እንዲህ እያለ ጸለየ አለቀሰም ይህችን ዛሬ የሞተችውን ሥጋዋም በመሬት ተጥሎ በነፍስዋ ወደ አንተ የመጣችውን ማርልኝና አንሳልኝ ነፍሴንና ስጋዬን በአንተ ላይ ጥያለሁ ብላ በእኔ ላይ እንደ ተማጠነች አቤቱ አንተ ራስህ ታውቃለህና በህይወት ሳለችም እንዳገለገችኝ አንተ ራስህ ታውቃለህ አባታችንም ይህን ጸሎት ጸልዮ ዝም አለ እግዚአብሄርም ይህችን ነፍስ ለምን ወደ እኔ አመጣችሃት የሕራ ድንግል አደለች የ እርሱ ስለሆነች ወደ እርሱ መልሳት እርሳም በስማይ ሳለች ከፈጣሪዋ አንደበት ከሰማች በኋላ የመላእክት ቅዱስ ገብርኤልን ለወዳጄ ሐራ ድንግል ሶስት ጊዜ እንዲህ ብለህ አዋጅ ንገር ሲለ ከዚያ ከፈጣሪ አንደበት ሰማች:: ሐራ ድንግል ሆይ በ እጅህ የተባረከውንና በቃልህ የተጽናናውን ስምህን የጠራውንና መታሰቢያህን ያደረገውን ለተራቡትም ለተጠሙትም እህልና ውሃ በመስጠት በዓልህን ያከበረውን ሀጢአተኛና በደለኛ ሳለም በጸሎትህና በቃል ኪዳንህ የታመነውን የገድልህንም መጽሀፍ ያጻፈውን ያነበበውንና የተረጎመውን የሰማውንና ለሰዎች ያሰማውን አጽምህንም እየጠበቀ በገዳምህ የተቀመጠውን አንተን ወድዶ ከሩቅ ወይም ከቅርብ ሀገር በመምጣት ገዳምህን የጎበኘውን ወንድ ልጁንና ሴት ልጁንም በስምህ የጠራውን እነዚህ ሁሉ በየወገናቸው ከስጋና ከነፍስ ባርነት ነጻ የወጡ ይሆኑ ዘንድ እስከ ሰባት ትውልድ ምሬልሃለሁ አንተ አገልግለሃልና ከህፃንነትህም ጀምረህ እስከዚች ሰአት ፈቃዴን ፈጽመሃልና:: በሞት ከሥጋዋ የተለየች ያች ነፍስም ይህን ነገር በሰማች በኋላ ከሰማይ ተመለሰች ከሥጋዋ ጋር ተዋህዳ በአባታችን ጸሎት ተነሳች ለወዳጄ ሐራ ድንግል ሂድና አዋጅ ንገር ብሎ መላኩ ገብርኤልን ሲያዝዘውከ እግዚአብሄር የሰማችውን ቃል ኪዳን ለሰዋች ተናገርች አባታችን ሐራ ድንግልም በጸጋ አወቀ የእግዚአብሄር ምስጢር ባየችው በዚች ሴት መነሳት ደስ አለው::እግዚአብሄርም ለአባታችን ሁለት ቃል ኪዳን ሰጠው አንደኛው ያቺ ሴት ናት ሁለተኛውም ከዚህ አለም በሞት ተለይቶ ወደ ዘላአለም ህይወት በሄደ ጊዜ እግዚአብሄር የሰጠው ነው:: የአባታችን ሐራ ድንግልም የእረፍቱ ቀን በደረሰ ጊዜ እግዚአብሄር የምህረትና የይቅርታ ቃል ኪዳንን ይሰጠው ዘንድ ከሰማይወደ እርሱ መጥቶ ወዳጄ ሐራ ድንግል ሆይ ስለ እኔ ብዙ አመታትን ደክመሃል እኔም እንዲህ ብዬ ቃልኪዳ እስትሃለሁ:: ሐራ ድንግል ሆይ በ እጅህ የተባረከውንና በቃልህ የተጽናናውን ስምህን የጠራውንና መታሰቢያህን ያደረገውን ለተራቡትም ለተጠሙትም እህልና ውሃ በመስጠት በዓልህን ያከበረውን ሀጢአተኛና በደለኛ ሳለም በጸሎትህና በቃል ኪዳንህ የታመነውን የገድልህንም መጽሀፍ ያጻፈውን ያነበበውንና የተረጎመውን የሰማውንና ለሰዎች ያሰማውን አጽምህንም እየጠበቀ በገዳምህ የተቀመጠውን አንተን ወድዶ ከሩቅ ወይም ከቅርብ ሀገር በመምጣት ገዳምህን የጎበኘውን ወንድ ልጁንና ሴት ልጁንም በስምህ የጠራውን እነዚህ ሁሉ በየወገናቸው ከስጋና ከነፍስ ባርነት ነጻ የወጡ ይሆኑ ዘንድ እስከ ሰባት ትውልድ ምሬልሃለሁ አንተ አገልግለሃልና ከህፃንነትህም ጀምረህ እስከዚች ሰአት ፈቃዴን ፈጽመሃልና::
አባታችን ሀራ ድንግል ይህን ቃል በሰማ ጊዜ እግዚአብሄርን ሲያመሰግን እንዲህ አለ አምላኬ ሆይ ከፍ ከፍ አደርግሃለሁ ቅዱስ ስምህንም ለዘላለም አከብራለሁ ሁልጊዜ አመሰግንሃለሁ ስምህንም ለዘላለም ዓለም አከብራለሁ ደግ ወይም ክፉ ቢሆን በእኔ የተማጠነ ሰው ሁይድን ዘንድ ይህን ቃል ኪዳን ሰጥተሀኛል እግዚአብሄርም ይህን ምስጋና ከእርሱ ከተቀበለ በኋላ ከእርሱ ዘንድ ሄደ:: ገዳሙንም እንዲህ እያለ ባረካት የአብና የወልድ የመንፈስ ቅዱስም በረከት በገዳሜና ስሜን በሚተሩ ሁሉ ላይ ይደር አምላክን በወለደች የ እመቤታችን የማርያም በረከትም በገዳሜና እኔን በሚወድዱ ሁሉ ላይ ይደር የሚካኤልና የገብርኤል በረከት የማያንቀላፉ ትጉሃን ዝም የማይሉና አመስጋኞች የሆኑ የሱራፍኤልና የኪሩቤል በረከት በገዳሜና በእኔ በሚማጸኑ ሁሉ ላይ ይደር የ እስጢፋኖስ የጊዮርጊስ የመርቆርዮስ የፋሲለደስ የቴዎድሮስና የገላውዴዎስ የድል አድራጊዎች ሰማእታት ሁሉ በረከት በገዳሜና ፈቃዴን በሚፈጽሙት ሁሉ ላይ ይደር የ አባታችን አቡነተክለሀይማኖትና የ አባታችን አዎስጣቴዎስ የ አባታችን የገብረ መንፈስ ቅዱስና በኢትዮጵያ ውስጥ በገዳማትና በአድባራት በደሴቶችም የሚኖሩት ሁሉ በረከት በገዳሜና በውስጥዋ ሆነው አስከሬኔን በሚጠብቋት ሁሉ ላይ ይደር የሀይማኖት አምድና የቸርነት መዝገብ የሆነው እንደ መላእክትም በንጽህና የተሸለመው አባታችን ሐራ ድንግል ይህን ቃለ ቡራኬ ከተናገረ በኋላ በኢያቄምና በሐና በፋሲለደስና በገላውዴዎስ በፊቅጦርም በዓል ጥር አስራ አንድ ቀን ከዚህ ከሀላፊው ዓለም ድካም አረፈ:: በአሉም ጥር 11 ቀን በታላቅ ድምቀት በባህርዳር ይከበራል፡፡
ምንጭ ገድለ አቡነ ሐራ ድንግል ጽሎቱና በረከቱ ከሁላችን ከህዝበ ክርስቲያን ጋር ይኑር ለዘለዓለሙ አሜን!

Tuesday, August 11, 2015

ጉዞ ከፕሮቴስታንት ወደ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ (ምስክርነት)

እህታችን የፕሮቴስታንትን ድርጅት ሃይማኖቷ እንዲሆን እና ድርጅቱን እንድትከተል የሆነበት ምክንያቱ እንዲህ ነው….. በእንጀራ አባቷ ጓደኛ ምክንያት በመታለል ሲሆን የኦርቶዶክስ ሃይማኖቷን እንድትክድ እና ወደ ፕሮቴስታንት ድርጅት እንድትቀላቀል፤ የፈለገችውን ገንዘብ ያህል እንደሚሰጧት፤ ልብስ፤ ጫማ፤ ትምህርቷን በሰፊው እየከፈሉ ሊያስተምሯት ቃል ገብተው ነበር። እንደወሰዷትም የኑፋቄን ትምህርት ለሦስት አመታት በተከታታይ አስተማሯት፤ ገንዘብም ሰጧት፤ ማህተቧን ከአንገቷ በጥሳ እንድትጥል እና እንድትረግጥ አደረጉ….መላእክትን እንዳትፈራ እንደተራ ነገር እንድትቆጥር አደረጉ፤ ቅዱሳንን ማቃለል ሥራየ ብላ እንድትይዝ አደረጉ፤ እመቤታችንን መዝለፍን አስተማሯት……እንደ ልጅቱ አገላለጽ ወይም በአንደበቷ እንደመሰከረችው ፓስተር ተብየዎች የፕሮቴስታንትን ድርጅት የሚከተሉ ወጣቶች እና እሷን ጭምር ትዳር ከመያዛችሁ በፊት ሴክስ አርት ስለሆነ ኑና እናስተምራችሁ አያሉ ያስቸግሯቸው እንደነበር እና ሌሎችም የተደበቁ የተሐድሶ አጀንዳዎችን በይፋ ነገረችን ….ያሳዝናል። ከእኛ ወገን መስለው ያሉ ነገር ግን ልባቸው መናፍቅ የሆኑ ስንቶችን ዘረዘረቻቸው……..ብቻ የአቡነ ተክለሃይማኖት አምላክ ይጠብቀን…..አጽራረ ቤተክርስቲያንን ያስታግስልን አሜን። መረጃዎችን ለወደፊቱ ለሚከተለው ክፍል እንደምትሰጥ ቃል ገብታለች። እኛም ለመስማትም ለማየትም እንፈልጋለን እንጠብቃለን። የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ቤተክርስቲያናችንን ይጠብቅልን አሜን።
እግዚአብሔር ፈቅዶ ከዚህች የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ የነበረች እህት ጋር ለተወሰነ ቀናት ተነጋግሬ፤ ስህተቷን አምና ወደ ቀደመችው እና ትክክለኛ ሃይማኖቷ እንድትመለስ ምክንያት ብሆንም ይህን ላደረገ የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይገባዋል። ምስክርነቷን ከተጠመቀች በኋላ ነሐሴ 3 ቀን 2007 ዓ.ም ጎንደር አደባባይ አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን ሰጥታለች።

ተአምር በ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ከርስቲያን /ሽሬ/

Monday, August 3, 2015

አቡነ ዳንኤል ዘገዳመ አስቄጥስ

ግንቦት 8-ዕረፍቱ ለአቡነ ዳንኤል ዘገዳመ አስቄጥስ
አቦ ገድሉ ከማር የሚጣፍጠውን የዚህን ታላቅ ጻድቅ ታሪክ ያንብቡና ነፍስዎትን እርክት ያድርጉ!
አቡነ ዳንኤል በመቃርስ ገዳም በደብረ ሲሐት ይኖር የነበረ ሲሆን እርሱም እጅግ ገድለኛ አባት ነው፡፡ 40 ዓመት በአስቄጥስ ገዳም ሲኖር ከቅጠል በቀር ተመግቦ አያውቅም፡፡ በአስቄጥስ ገዳም ዜናው ሁሉ በዓለም በተሰማ ጊዜ የነገሥታት ልጆችም ወደ እርሱ እየመጡ እየተባረኩ ይሄዱ ነበር፣ ግማሾቹም በዚያው ይመነኩሱ ነበር፡፡ ይህም አባ ዳንኤል ስሟን እንጣልዮስ አስብላ የነበረች ንግሥት የነበረችውን ቅድስት በጥሪቃን የገነዛት ነው፡፡ እርሷም ወንድ የነበረች ሲሆን ይህም የታወቀው ከሞተች በኋላ ነው፡፡ አውሎጊስ የሚባለውን የወፍጮ ድንጋይ እየወቀረ በመሸጥ ለድኆች የሚመጸውትን ጻድቅ ሰው ዋስ እሆነዋለሁ በማለት ከእግዚአብሔር ዘንድ ለምኖ ሥልጣንና ብዙ ወርቅ እንዲያገኝ ያደረገው ይህ አባ ዳንኤል ነው፡፡ በኋላም አውሎጊስ ሀብቱና ንብረቱ ከእግዚአብሔር የሚያርቀው ቢሆን አባ ዳንኤል በጸሎቱ መልሶ ሀብቱን እንዲያጣ አድርጎታል፡፡ አውሎጊስ የሚባል ጻድቅ የወፍጮ ድንጋይ እየወቀረ (እየጠረበ) በመሸት የሚየገኘውን ለድኆችና ጦም አዳሪዎች ይመጸውት ነበር፡፡ አባ ዳንኤልም የአውሎጊስን መልካም ሥራ ተመልክቶ እጅግ ደስ ብሎት ለአውሎጊስ የሀብቱን መጠን እንዲጨምርለትና ይበልጥ እንዲመጸውት በማሰብ ወደ እግዚአብሔር በጸሎት አሳሰበ፡፡ ለአውሎጊስም ዋስ ሆነውና ሀብቱ ተጨመረለት፡፡ አንድ ቀን የሚወቅረውን ድንጋይ ሲፈቅል በሸክላ ዕቃ የተደፈነ ሙሉ ወርቅ አገኘ፡፡ ወደ ቁስጥንጥንያም ከተማ ሄዶ ለንጉሡ አስረከበና የንጉሡ የሠራዊት አለቃ ሆኖ ተሾመ፡፡ ከተሾመም በኋላ የቀድሞውን የጽድቅ ሥራውን ተወ፡፡ አባ ዳንኤልም ስለ እርሱ ሰምቶ ሊያየው ቢሄድ በፈረስ ላይ ተቀምጦ በሠራዊት ታጅቦ በትዕቢት ተመልቶ አገኘው፡፡ ክፉ የትዕቢት መንፈስ አድሮበት ነበር፡፡ አባ ዳንኤልም አውሎጊስ ሀብት እንዲያገኝ በመለመኑ አዘነ፡፡ በሌሊትም የአውሎጊስ ነፍስ በእርሱ ምክንያት እንደጠፋች ራሱ አባ ዳንኤልም ሲሰቀልና እመቤታችን ስለ እርሱ ስትማልድ ራእይ አየ፡፡ ከእንቅልፉም በቃ ጊዜ የአውሎጊስ ሀብት እንዲጠፋና ወደ ቀደመ ግብሩ እንዲመለስ በጾም ጸሎት ሱባኤ ያዘ፡፡ መልአክም ተገልጦለት በእግዚአብሐር የፍርድ ሂደት ውስጥ ጣልቃ በመግባቱ ከገሠጸው በኋላ አውሎጊስም ምሕረት እንደሚያገኝ ነገረው፡፡ አውሎጊስን የሾሸመው ንጉሥም ሞተና ሌላ ንጉሥ ነገሠ፡፡ አውለጊስንም ንብረቱን ሁሉ ቀምቶ ነፍሱንም ለመግደል አሳደደው፡፡

አውሎጊስም ነፍሱን ለማዳን ሽሽቶ ወደ ሀገሩ በመግባት የቀድሞ ሥራውን መሥራት ጀመረ፡፡ ነዳያንንም እንደዱሮም መመገብ ጀመረ፡፡ አባ ዳንኤል ከታለቁ ጻድቅ ንጉሥ ከቅዱስ አኖሬዎስ ጋር የተገናኘ ታሪክ አለው፡፡ ይኸውም አባ ዳንኤል 40 ዓመት ሙሉ በአስቄጥስ ገዳም ሲኖር ከቅጠል በቀር ተመግቦ አያውቅም ነበርና ከጽድቁና ከብቃቱ የተነሣ ከብዙ ዘመን በኋላ የመመካት ክፉ ሀሳብ መጣበት፡፡ ‹‹በገዳም ውስጥ እንደእኔ ትርሕምትን ገንዘብ ያደረገ ይኖር ይሆን?›› ብሎም አሰበ፡፡ ሰውን ወዳድ የሆነ ጌታችንም ይህን ክፉ ሀሳቡን ሊያርቅለት ሽቶ ብርሃናዊ መልአኩን ላከለት፡፡ መልአኩም አባ ዳንኤልን ስለ ትምክህቱ ቢቆጣውም አባ ዳንኤል መልአኩን መልሶ ‹‹ጌታዬ ከእኔ የሚሻል ካለ ንገረኝ፣ ወደ እርሱ ሄጄ አየው ዘንድ እወዳለሁ፣ በመመካቴም ወደ ፈጣሪዬ በልመና እመለስ ዘንድ›› አለው፡፡ መልአኩም ‹‹እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው የሮሜና የቁስጥንጥንያ ንጉሥ አኖሬዎስ በመንግሥተ ሰማያት ባልንጀራህ ነው›› አለው፡፡ ‹‹ንጉሥ አኖሬዎስም የመነኮሳትን ሥራዎች ሁሉ ስለሚሠራ ከልብሰ መንግሥቱ ሥር በሥጋው ላይ ማቅ ይለብስ ነበር›› ተብሎ በስንክሳሩ ላይ የተጻፈለት ጻድቅ ንጉሥ ሲሆን ሰማያውያን የሆኑ ቅዱሳን መላእክትም ቅድስናውን የመሰከሩለት በንግሥና ያለ ታላቅ የእግዚአብሔር አገልጋይ ነው፡፡ አባ ዳንኤልም ይህ በሰማ ጊዜ መሬት ላይ ወድቆ በራሱም ላይ አመድ ነስንሶ የዚህን የሮም ንጉሥ አኖሬዎስን ግብር ያሳየው ዘንድ ጌታችንን ለመነ፡፡ ደመናም መጥታ ነጥቃ ወሰደችውና ንጉሥ አኖሬዎስ ደጅ አደረሰቸውና ንጉሡን በዙፋኑ ላይ ሆኖ ባየው ጊዜ ከግርማው የተነሣ አይቶት በታላቅ ፍርሃት ውስጥ ሆኖ ከእግሩም በታች ሰገደለትና አኗኗሩንም ይነግረው ዘንድ በጌታችን ስም አማፀነው፡፡ ንጉሥ አኖሬዎስም ሰሌን በመታታት በእጅ ሥራው ደክሞ ከሚያገኘው በቀር ምንም ሳይበላና ሳይለብስ 40 ዓመት እንደሆነው፣ ሰሌን ታቶ ሸጦ ካገኘውም ውስጥ ከዕለት ምግቡ መግዣ የሚተርፈውን ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች እንደሚመጸውት፣ ምግቡም እንጀራና ጨው፣ ቅጠል መጻጻም እንደሆነ፣ የማንንም ንብረት ፈጽሞ እንዳልንካ፣ ድንግልናውንም ጠብቆ እንደሚኖር ነገረው፡፡ አባ ዳንኤልም ድጋሚ ከእግሩ ሥር ወድቆ ሰግዶለት ስለ ትምክህቱም ፈጽሞ እያዘኑ ወደ በዓታቱ ተመልሷል፡፡ አባ ዳንኤል አንድ ቀን ከረድኡ ጋር ወደ እስክንድርያ ሲጓዝ ስሙ ምህርካ የሚባል እብድ አገኘ፡፡ ብዙ እብዶችም ይከተሉት ነበር፡፡ እርሱም ለአገሩ ሰዎች ሁሉ በእውነት ያበደ ይመስላቸው ነበር፡፡ አባ ዳንኤልም እጁን ይዞ ወደ ሊቀ ጳጳሳቱ ወስዶ ትሩፋቱን ተጋድሎውን ነገረው፡፡ ከሊቀ ጳጳሳቱም ጋር ሆነው እብዱን ስለራሱ እንዲነግራቸው በእግዚአብሔር ስም ባማሉት ጊዜ ከዝሙት ጦር በመሸሽ ራሱን እብድ እንዳስመሰለ ነገራቸው፡፡
አንድ ቀን አባ ዳንኤል በሌሊት በበረሃ ውስጥ በጨረቃ ብርሃን ሲጓዝ በተራራ ላይ ተቀምጣ ጠጉሯ መላ ሰውነቷን የሸፈናት በዚያም በረሃ ስትኖር በተሰነጠቀ ዓለት ውስጥ 38 ዓመት ብቻዋን ማንም ሳያያት የኖረች ጻድቅ እናት አግኝቶ ምሥጢሯን ሁሉ ነግራዋለች፡፡ እርሷም ቅድስት አመተ ክርስቶስ ናት፡፡ አባ ዳንኤልም 38 ዓመት ሙሉ በዚህ በረሃ ምንም ሰው ሳታይ የኖረችበትን ተገድሎዋን በዝርዝር ነግራቸዋለች፡፡ እርሳቸውም ወደ ገዳማቸው ተመልሰው ለአበ ምኔቱና ለመነኮሳቱ ታሪኳን በመንገር ልብስ ይዘውላት ቢመጡ ዐርፋ አግኝተዋታል፡፡
አባ ዳንኤል የልዮንን የክህደት ደብዳቤ ወታደሮቹ አምጥተው በመነኮሳቱ ፊት ሲያነቡ ደብዳቤውን ተቀብሎ በሕዝቡ ፊት ቀዶታል፡፡ ወታደሮቹም አባ ዳንኤልንደብደበው ከገዳሙም አሳደውታል፡፡ ብዙ ሥቃይም አድርሰውበታል፡፡ አባ ዳንኤል በአንዲት ዕለት ከደናል ገዳም ደርሶ ደጁን አንኳኳ፡፡ እነርሱም አባ ዳንኤል መሆኑን ዐውቀው ከፈቱለት፡፡ አንዲት ሴትም ራሷን ዕብድ አስመስላ በደጅ የምትተኛ ሴት ነበረች፡፡ እርሱም ዕብድ መስላ በደጅ ስለተቀበጠችው ሴት አበምነቷን ሲጠይቃት እብድ መሆኗን ነገረችው፡፡ አባ ዳንኤል ግን ዕብድ የመሰለቻቸው ሴት እብድ ሳትሆን በድብቅ በታላቅ ተጋድሎ የምትኖር ቅድስት ሴት መሆኗን ነገራት፡፡ ዕብድ የተባለችውም ሴትም አባ ዳንኤል ምሥጢሯን እንደገለጠባት በስውር ዐውቃ ወዲያው ደብዳቤ ጽፋ ይኸውም ‹‹የተከበራችሁ እኅቶቼ ስላስቀየምኳችሁና ስላሳዘንኳችሁ ይቅር በሉኝ›› ብላ ጽፋ ደብዳቤውን አስቀምጣ ጥላቸው ጠፋች፡፡ እነርሱም ከዚያ በኋላ ዳግመኛ አላዩአትም፡፡ ደናግል ወደሚኖሩበት ገዳም አንድ የወንበዴዎች አለቃ ሰይጣን አነሳስቶት ወደ ገዳሙ በአባ ዳንኤል ተመስሎ ቆቡን ደፍቶ በሩን አንኳኳ፡፡ ደናግላኑም ሊዘርፋቸው መምጣቱን ምንም ባለማወቅ ይልቁንም አባ ዳንኤል መጣ ብለው በሩን ከፈቱለትና አስገቡት፡፡ እግሩንም አጥበው ለበረከት ብለው የእግሮቹን ዕጣቢ በፊታቸው ላይ ረጩት፡፡ ከመካከላቸውም አንዷ ዐይነ ሥውር ነበረችና ዐይኗ ወዲያው በራላት፡፡ በዚህም ደናግሉ እጅግ ተደስተው ‹‹አባ ዳንኤል አንተ ንዑድ ክቡድ ነህ›› ብለው ሰገዱለት፡፡ ይህን ጊዜ የሽፍቶቹ አለቃ በጣም ደንግጦ በመጸጸት ወደ አባ ዳንኤል ዘንድ ሄዶ ያደረገውን ሁሉ በመናገር ንስሓ ገባ፡፡ መንኩሶም በታላቅ ተጋድሎ መኖር ጀመረ፡፡ እርሱም ተአምራት እስከማድረግ ደርሶ በሰላም ዐረፈ፡፡ የአባ ዳንኤልም ተጋድሎና ተአምር ምን ቢጽፉት የሚያልቅ አይደለም፡፡ ዕረፍቱም በደረሰ ጊዜ ጌታችን ታላቅ ቃልኪዳን ሰጥቶት ቅድስት ነፍሱን ወደ እርሱ ወስዷታል፡፡ ዕረፍቱም ግንቦት 8 ቀን በታላቅ ክብር ተፈጽሟል፡፡
በረከቱ ይደርብን! ምልጃው ከይለየን አሜን!!!
ስምን ስም ያነሳዋልና በዚሁ አጋጣሚ ኢትዮጵያዊውን ጻድቅ የትግራይ ገርዓልታውን አቡነ ዳንኤልንም ይወቋቸው፡፡ አቡነ ዳንኤል ዘገርዓልታ አባታቸው መልክአ ሥላሴ እናታቸው ዓመተ ጽዮን ሲባሉ የትውልድ ሀገራቸው ትግራይ ገርዓልታ ነው፡፡ በ7 ዓመታቸው የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ተምረው አጠናቀው በ13 ዓመታቸው መነኮሱ፡፡ ሊቃውንቱ ‹‹ማኅቶተ ገዳም›› እያሉ የሚጠሯቸው ገድለኛ አባት ናቸው፡፡ አስገራሚው ባለ 4 ዓምዱና 40 ያሸበረቁ ሥዕላት ያሉት አስደናቂው ገድላቸው የት እንዳለ አይታወቅም፣ እኛ ሀገር ገድላቸው የለም፡፡ 2ኛውን ገድላቸውን ፖርቹጋሎች ከጠባቂው ገዝተው ወስደው በሀገራቸው አሳትመውታል፡፡ ገድሉን የሸጠው ጠባቂም ሆዱ ተነፍቶ በስብሶ ተልቶ ከቤተ ክርስቲያኑ በራፍ ላይ ወድቆ ሞቷል፡፡ የጻድቁ የዕረፍታቸው ዕለት ኅዳር 6 ቀን ትግራይ በሚገኘው ገዳማቸው በደማቅ ሁኔታ ይከበራል፡፡ ገዳማቸው የሚገኘው እጅግ ከፍተኛ ተራራ ላይ ሲሆን ከላይ ሆነው ወደታች ሲመለከቱ መሬት የሚደረስባት አትመስልም፡፡ እስቲ ከፎቶው ላይ ይመልከቱት!
(ምንጭ፡- የታኅሣሥና የግንቦት ወር ስንክሳር;መለከት 14ኛ ቁ5-1998 ዓ.ም፣ የቅዱሳን ታሪክ-108 &166)

አባ ዮሐንስ ተስፋ ማርያም - የወንቅሸት ቅዱስ ገብርኤል አንድነት ገዳም

አባ ዮሐንስ ተስፋ ማርያም የወንቅሸት ቅዱስ ገብርኤል አንድነት ገዳም አበምኔት፤፤ አባ ዮሃንስ ተስፋ ማርያምን ማነጋገር ከፈለጉ ፡ከዚህ ዌብሳይት ሂደዉ www.wonkshet.com ኮንታክት አስ ከሚለው ላይ ኢሜይል ያርጉልንና ስልካቸውን እንልክልዎታለን፤፤
This is the testimony at Wonkshet Adame Yordanos Kidus Gabriel Monastery by Aba Yohannes Tesfamaryam. For more information, visit www.wonkshet.com

Wednesday, July 22, 2015

አባ ገዐርጊ

ግንቦት 18-ጌታችን መልአኩን ልኮ ‹‹ተጋድሎህ በመጠን ይሁን›› በማለት ተጋደሎውን እንዲቀንስ ያዘዘው የአባ ገዐርጊ ዕረፍት ነው፡፡
ጻድቁ የክርስቲያን ወገን ሲሆን ወላጆቹም ደጋግ ቅዱሳን ጻድቃን ናቸው፡፡ በአደገም ጊዜ የወላጆቹን በጎች የሚጠብቅ እረኛ ሆነ፡፡ ነገር ግን እርሱ የምንኩስናን ልብስ ይለብስ ዘንድ በልቡ ይመኝ ነበር፡፡ 14 ዓመትም በሆነው ጊዜ የእግዚአብሔር ጸጋ አነሳሳችውና በጎቹን ትቶ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔደ፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣል›› እንዳለው (2ኛ ቆሮ 11፡14) አባ ገዐርጊ ወደ ገዳሙ እየተጓዘ ሳለ በሽማግሌ አምሳል ከይሲ ሰይጣን ተገለጠለትና ከዓላማው ሊያደናቅፈው ፈተነው፡፡ እንዲህም አለው ‹‹ልጄ ሆይ ስለ አንተ አባትህ ልብሱን ቀዶ አየሁት፣ የዱር አውሬ ነጥቆ የበላህ መስሎት አባትህ ያዝናል፣ ያለቅሳል፡፡ ተመልሰህ የአባትህን ልብ ልታጽናና ይገባሃል›› አለው፡፡ አባ ገዐርጊም ደንግጦ አንድ ሰዓት ያህል ሳይንቀሳቀስ ቆመመ፡፡ ከዚህም በኋላ የከበረ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቅዱስ ወንጌሉ ‹‹ከእኔ ይልቅ አባት እናቱን የሚወድ ለእኔ ሊሆን አይባውም ደቀ መዝሙሬም ሊሆን አይችልም›› ብሏል ብሎ አሰበ፡፡ ማቴ 10፡37፡፡ ይህንንም ባሰበ ጊዜ ሰይጣን እንደጢስ ሆኖ ተበትኖ ጠፋ፡፡ አባ ገዐርጊም ሰይጣን እንደሆነ ዐወቀ፡፡ ‹‹በመጠን ኑሩ ንቁም፣ ባላጋራችሁ ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና ለእግዚአብሔር ተገዙ፣ ዲያብሎስን ግን ተቃወሙ ከእናንተም ይሸሻል›› 1ኛ ጴጥ 5፡8፣ ያዕ 4፡7፡፡

በዚያን ጊዜም አስቀድሞም ተገልጦለት የነበረው የብርሃን ምሰሶ ተገለጠለት፣ የእግዚአብሔርም መልአክ በመነኩሴ አምሳል ተገለጠለትና አብሮት ተጓዘ፡፡ መልአኩም አባ ገዐርጊን አባ አርዮን ገዳም አደረሰው፡፡ አባ ገዐርጊም ጽኑ ተጋድሎውን ጀመረ፡፡ በገዳሙ 14 ዓመት በታላቅ ተጋድሎ ሲኖር እህል አይቀምስም ውኃም አይጠጣም ነበር፡፡ ለ14 ዓመትም ከመቀመጥ በቀር ምንም አልተኛም፡፡ ከዚህም በላይ ተጋድሎውን በጨመረ ጊዜ እግዚአብሔር መልአኩን ልኮ ‹‹በመጠን ተጋደል›› ብሎታል፡፡ መልአኩም ተገልጦለት ‹‹‹ሥጋህ እንዳይደክም በመካከለኛ ተጋደል› ብሎሃል ጌታ›› ካለው በኋላ ሊሠራው የሚገባውን ሥርዓት ሠራለት፡፡ ሁልጊዜም እስከሚመሽ እንዲጾም፣ ትንሽም እንጀራን እንዲበላ፣ ከእራት ሰዓት እስከ መንፈቀ ሌሊት ስለሥጋው ዕረፍት እንዲተኛ በቀረው ሌሊት እስቲነጋ ተግቶ እንዲጸልይ ሥርዓት ሠራለት፡፡
መልአኩ በሠራለት በዚህ ሥርዓት ብዙ ዘመን ሲጋደል ከኖረ በኋላ በበረሃ ውስጥ ብቻውን ወሊኖር ወዶ በጫካ ውስጥ እየተመላለሰ ሁለት ዓመት ተቀመጠ፡፡ ነገር ግን ጌታችን ተገልጦለት ወደ ቀደመ ቦታው እንመለስ አዘዘው፡፡ ደብሩም ከከበሩ መክሲሞስ ዱማትዮስ ገዳም አጠገብ ነበር፡፡ ወደ ደብሩም በተመለሰ ጊዜ አብርሃም ከተባለ ደገኛ ቅዱስ ጋር ተገናኙና ሁለቱም በጋራ ለመኖር ተስማምተው ወደ አስቄጥስ ገዳም አበ ምኔት ወደ አባ ዮሐንስ ዘንድ ሄዱ፡፡ እርሱም ቦታ ሰጥቷቸው በውስጧ በተጋድሎ መኖር ጀመሩ፡፡ ያችም ቦታ እስከዛሬ ታውቃ ትኖራለች፡፡ ስሟም በግቢግ ትባላለች፡፡ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጣሪያዋን ሰንጥቆ ወደ እነዚህ ሁለቱ ቅዱሳን የወረደባት ናት፡፡ እነርሱም በክብር ሰገዱለት፡፡ ጌታችንም ባርኳቸውና አጽናንቷቸው ዐረገ፡፡ በዚያችም ጌታችን በወረደባት መስኮት ብርሃን ተመለከቱ፡፡ እስከዛሬም ድረስ የተከፈተች ሆና ትታያለች፡፡ እነዚህም ሁለት ቅዱሳን (አባ ገዐርጊና አባ አብርሃም) ለመኮሳት የሚሆኑ ብዙ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሱ፡፡ ከዚህም በኋላ አባ አብርሃም ጥር 2 ቀን ዐረፈ፡፡ ከእርሱም በኋላ አባ ገዐርጊ በ72 ዓመቱ ግንቦት 18 ቀን ዐረፈ፡፡
የአቡነ ገዐርጊ ምልጃና በረከቱ በምልጃው በምንታመን በሁላችን ላይ ይደርብን! አሜን!!!
(ምንጭ፦ የግንቦት ወር ስንክሳር)

Tuesday, July 21, 2015

ጩጊ ማርያም- ከጸበሉ ጠጥተው ስጋቸው ያልፈረሰ ፍየሎች

❖❖❖ በስመ ሥላሴ ❖❖❖

እነሆ ጌታ ፈቅዶ የሰማሁትን ያየሁትን እነግራቹ ዘንድ ጀመርኩ የዘንድሮዉን የሰኔ ጎሎጎታ ክብረ በዓል አከብር ዘንድ ወደ ቅዱሱ እና በጌታ ፍቅር በተጠመደዉ እና ከልጅነቱ ጀምሮ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርት ፀንቶ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬዎችን አፍርቶ በፀጋ ከፍ ወዳለዉ የነ አቡነ አምደሥላሴ ወዳጅ ወደነበሩት ወደ አቡነ ምዕመነድንግል ገዳም ነበር የተጓዝኩት ። የኚ አባት ገዳም ልዩ መታወቂያ ስሙ ጩጊ ማርያም በመሰኘት ይታወቃል ። ከጎንደር 25 km ርቀት ያላት ሲሆን ኮሶዬ ከተባለች አካባቢ ሲደርሱ ለበረታ የ2 ሰዓት ለደከመ ከ 2ሰዓት በላይ ሚያሰኬደዉን መንገድ ይጀምራሉ ። አቡነ ምዕመነድንግል እንደ ቀደምት አበዉ ጠንካራ እና ለሃይማኖተ ክርስቶስ ቀናተኛ የነበሩና በዋልድባ ገዳም በአበምኔትነት ያገለገሉ ኀላም ውዳሴ ከንቱን በመሸሽ ከገዳሙ ርቀዉ አሁን ወዳሉበት ብዙ ፅድ እና ወይራ ወዳለባት /ጩጊ / መጥተዋል በዚህ ስፍራ ለረዥም ግዜ ተጋድሎ አርገዉበታል ። በዚህ ስፍራ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከድንግል ማርያምና ከቅዱሳን ሁሉ ጋር ተገልጦ ለአባታችን ቃል ኪዳን ሰጥቶአቸዋል፣ አንዲሁም እንደ ትንሽ ብላቴና አቅፎአቸዉ ስሞአቸዋል ፣እንዲሁም በጌታ አዳኝነት አምነዉ በቅዱሱ አቡነ ምዕመነድንግል ፀሎት ሚታመኑ ሁሉ ፈዉስ ይሆናቸዉ ዘንድ ሁለት ማየ ዮርዳኖስ አፍልቆላቸዋል ከዚ ማየ ዮርዳኖስ የጠጡ ሁሉ ከደዌ ከመፈወሳቸዉ በተጨማሪ በድን ስጋቸዉ አይፈርስም አይበሰብስም ለዚ እንደማሳያ የሚሆኑ 16 ፍየሎች ከዚ ማየ ዮርዳኖስ ጠጥተዉ አሁንም ድረስ ሰዉነታቸዉ ሳይፈርስ አሁንም በሕይወት ያሉ ይመስላሉ ። አባታችን አቡነ ምዕመነድንግል አካሄዳቸዉን በጌታ ቃል እና ትምህርት ስላፀኑ ሞትን ሳያዩ እንደነ ሄኖክ ፣ ኤልያስ ፣ አቡነ አረጋዊ ፣ቅ.ያሬድ ተሰዉረዋል ።  አምላከ አቡነ ምዕመነድንግል እግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ ይማረን ፣ ይባርከን ። አሜን !!

Wednesday, July 1, 2015

ታላቁ ጻድቅ ንጉሥ የዐፄ ካሌብ

ግንቦት 20-ንጽሕናን ከቅድስና ጋር አስተባብሮ በመያዝ እግዚአብሔርንም ሰውንም በቅድስናና በፍቅር ያገለገለው የታላቁ ጻድቅ ንጉሥ የዐፄ ካሌብ ዕረፍት ነው፡፡ እናም ዛሬ በዕረፍቱ ዕለት ገድሉን ትሩፋቱን የቅድስና ሥራውን አብዝተን በመናገር አስበነው እንውላለን፤ በረከቱን እንካፈላለን፡፡ ይኸውም ታላቅ ጻድቅ ንጉሥ ዋጋው እጅግ የከበረውንና በነገሠ ጊዜ በራሱ ላይ የጫነውን የወርቅ ዘውዱን ከጌታችን መካነ መቃብር ላይ ይሰቅልለት ዘንድ ከአደራ ደብዳቤ ጋር ለኢየሩሳሌሙ ሊቀ ጳጳሳት ለአባ ዮሐንስ ከላከለት በኀላ ዓለምን ንቆ፣ ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ አንዲት የውኃ መንቀል ብቻ በመያዝ በአባ ጰንጠሌዎን እጅ በመመንኮስ ገዳማቸው አጠገብ ከሚገኝ ዋሻ ውስጥ ገብቶ 12 ዓመት በጾም በጸሎት በብዙ ድካምና ተጋድሎ እግዚአብሔርን ሲያገለግል ኖሮ ዛሬ ግንቦት 20 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፏል፡፡
መልካም የበረከት ንባብ ይሁንልን!!! (የጽሑፉ ምንጭ ገድለ አቡነ አረጋዊ፣ ገድለ አቡነ ጰንጠሌዎንና የኅዳርና የግንቦት ወር ስንክሳር ናቸው)

በቍስጥንጥንያ ዮስጢኖስ በነገሠ በ5ኛው ዓመት ዐፄ ካሌብ በኢትዮጵያ ነግሦ ነበር፡፡ የአይሁድም ንጉሥ ፊንሐስ ነበር፡፡ በዚህም ወቅት ሊቃነ ጳጳሳት የነበሩት የኢየሩሳሌሙ አባ ዮሐንስ፣ የቍስጥንጥንያው አባ ጢሞቴዎስ፣ የእስክንድርያውም አባ ጢሞቴዎስ፣ የአንጾኪያው አባ አውፍራስዮስ ነበሩ፡፡ ሳባ የምትባለው አገር በኢትዮጵያ ነገሥታት እጅ ውስጥ ነበረች፡፡
የሮም ነገሥታት አስባስያኖስና ጥጦስ አይሁድን ወረው አሳደዷቸውና ይህችን ሳባን አይሁድ ወረሷት፡፡ በውስጧም በጌታችን የሚያምኑ ብዙ ሕዝቦች ነበሩባት፡፡ በሳባ ውስጥም ክርስቲያኖች የሚኖሩባት ታላቅ ከተማ ነበረች፡፡ የአይሁድ ንጉሥ ፊንሐስም ወደ ከተማዋ ገብቶ በሺህ የሚቆጠሩትን ክርስቲያኖች ገደለ፡፡ ዙሪያ ዳር ድንበሯ በመስቀል ምልክት የታጠረች ስለነበረች ፊንሐስ መጀመሪያ መግባት ሳይችል ሲቀር ‹‹ወደ ውስጥ ገብቼ የከተማዋን አሠራር፣ ገበያዋን፣ አደባባዮቿን መጎብኝት እሻለሁ እንጂ ክፉ አላስብም፣ የማንንም ደም አላፈስም›› ብሎ ምሎ ወደ ውስጥ ገባ፡፡ ከነሠራዊቱ ከገባ በኋላ ግን መግደል ጀመረ፡፡ መጀመሪያውንም አቡነ ኂሩተ አምላክ ‹‹ውሸቱን ነው አታስገቡት፣ ሐሰተኛ ነው ደጁን ከፍታችሁ አታስገቡት›› ብለው ቢነግሯቸውም የሚሰማቸው ጠፋ፡፡ ፊንሐስም እንደገባ የሕዝቡን ገንዘብ ዘረፈ፤ ቀጥሎም በነልባሉ አየር ላይ ደርሶ እስኪታይ ድረስ እሳት አስነድዶ ‹‹ኤጲስ ቆጶሱን አባ ጳውሎስን አምጡልኝ›› ብሎ አዘዘ፡፡ እንደሞቱም ሲነገረው ዐፅማቸውን ከመቃብር አውጥቶ አቃጠለው፤ ቀጥሎም ቀሳውስትን፣ ካህናትን፣ ዲያቆናትን፣ መነኮሳትን ሁሉ በእሳቱ ውስጥ እንዲጨምሯቸው አዘዘ፡፡ አራት ሺህ ሃያ ሰባት ክርስቲያኖችም ወደ እሳቱ ተጥለው በሰማዕትነት ሞቱ፡፡
ፊንሐስም አቡነ ኂሩተ አምላክንና ታላላቅ መኳንንትን ግን አሳስሮ ብዙ አሠቃያቸው፡፡ ‹‹ክርስቶስን ያልካደ ሁሉ ተሠቃይቶ ይሞታል›› የሚል አዋጅ በከተማው እንዲነገር አዘዘ፡፡ አቡነ ኂሩተ አምላክንም አስሮ እያሠቃያቸው በከተማው አዞራቸው፡፡ ሕዝቡም ጌታችንን አንክድም እያሉ ወጥተው ተገደሉ፡፡ በዚህም ጊዜ የተገደሉት ቁጥራቸው 4252 ሆነ፡፡
የአቡነ አቡነ ኂሩተ አምላክን ሚስት ቅድስት ድማህን ከ2 ልጆቿ ጋር ይዞ አሠቃያቸው፡፡ አንደኛዋም የ12 ዓመት ሕፃን ምራቋን በፊንሐስ ላይ ተፋችበት፣ እርሱም ሰይፉን መዞ አንገቷን ቆረጠው፡፡ ለቅድስት ድማህም የልጇን ደም አጠጣት፡፡ ድማህም ‹‹ይህን እንዲሆን የፈቀደ እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን›› ብላ አምላኳን ስታመሰግን ሰምቷት እናቲቱንም አንገቷን ቆረጠው፡፡ አቡነ ኂሩተ አምላክንም ወደ ውጭ አውጥቶ ‹‹የምታመልኩትን ክርስቶስን ካዱ›› አላቸው፡፡ አቡነ ኂሩተ አምላክም ‹‹ክብር ይባውና ጌታዬን ኢየሱስ ክርስቶስን እያለመኩ ስኖር 78 ዓመት ሆነኝ፣ እስከ አራት ትውልድም ለማየት ደርሻለሁ፡፡ ዛሬም ስለከበረ ስሙ ምስክር ሆኜ ስሞት እጅግ ደስ ይለኛል፡፡ ወደዚህ ለመግባት ስትምል እኔም አስቀድሜ መሐላህን እንዳያምኑ ለወገኖቼ ነግሬአቸው ነበር፤ አንተ ሐሰተኛ ነህና ነገር ግን ይህ ሁሉ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው፤ ለዚህ ተጋድሎ ላበቃኝ ለእርሱ ምስጋና ይሁን›› እያሉ ፊንሐስን በተናገሩት ጊዜ ወደ ወንዝ ወስዶ አንገታቸውን አስቆረጠው፡፡ አቡነ ኂሩተ አምላክም በሰማዕትነት ከማረፋቸው በፊት የኢትዮጵያንና የሮምን መንግሥት ያጸና ዘንድ የአይሁድን መንግሥት ግን ያጠፋ ዘንድ ጌታችንን ለመኑት፡፡ ዕረፍታቸውም ኅዳር 26 ቀን ነው፡፡
አቡነ ኂሩተ አምላክም ሕዝቡን ተሰናብተው በተሰየፉ ጊዜ አንዲት ሴት ደማቸውን ለ5 ዓመቱ ልጇ ቀባችው፡፡ ይህንንም ሲያዩ ልጇን ነጥቀው ለንጉሡ ሰጥተው እርሷን ከእሳቱ ውስጥ ጨመሯት፡፡ ንጉሡ ፊንሐስም ሕፃኑን ‹‹እኔን ትወዳለህ ወይስ ክርስቶስ የሚሉት?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ የ5 ዓመቱ ሕፃንም ‹‹እኔስ የእጁ ሥራ ነኝና ክርስቶስን እወደዋለሁ፣ ይልቅስ ልቀቀኝና ወደ እናቴ ልሂድና ሰማዕትነቴን ልፈጽም›› አለው፡፡ ፊንሐስም ከእጁ እንዳይወጣ በያዘው ጊዜ እግሩን ነክሶት አምልጦት ሮጦ ሄዶ ከእሳቱ ውስጥ ገባ፡፡ ሁለተኛም የ10 ወር ሕፃን የተሸከመች አንዲት አማኝ ሴት ወደ ልጇ እያየች ‹‹ልጄ ሆይ ዛሬስ ላዝንልህ አልቻልኩም›› ብላ ስትናገር በእቅፏ ያለው የ10 ወሩ ሕፃን ልጇም አንደበቱን ከፍቶ ‹‹እናቴ ሆይ በፍጥነት ወደ ዘላለም ሕይወት እንሂድ ይህችን እሳት ከዛሬ በቀር አናያትምና›› አላት፡፡ እርሷም ልጇን ይዛ ዘላ እሳቱ ውስጥ ተወርውራ ገባች፡፡ የክርስቲያን ወገኖችም ይህን ሁሉ አይተው እኩሉ ወደ እሳት እኩሉ ወደ ሰይፍ ተሽቀዳደሙ፡፡ ራሳቸው የአይሁድ ሠራዊት ዕፁብ ብለው እስኪያደንቁ ድረስ ክርስቲያኖቹ ወደ ሰማዕትነት ተፋጠኑ፡፡ ቁጥራቸው ሃያ ሺህ ነበር፡፡ ክርስቲያኖቹም በሚሞቱበት ጊዜ የረዳቶቻቸውን የቊስጥንጥንያንና የኢትዮጵያን ነገሥታት ስም በጸሎታቸው ይጠሩ ነበር፡፡
ከዚህም በኋላ እሳቱ በሰማይ ውስጥ መልቶ 40 ቀንና 40 ሌሊት ታየ፡፡ ፊንሐስም ወደ ሀገሩ በተመለሰ ጊዜ ወደ ነገሥታቱ ሁሉ በኋይሉ እየተመካ ላከባቸው፡፡ የሮሜው ንጉሥ ዮስጢኖስም ይህን ሰምቶ ወደ እስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ ወደ አባ ጢሞቴዎስ መልአክት ላከ፡፡ ለሀገረ ናግራን ክርስቲያኖች ደማቸውን ይበቀልላቸው ዘንድ ለኢትዮጵያው ንጉሥ ለዐፄ ካሌብ መልእክት እንዲልክ ነገረው፡፡ ዐፄ ካሌብም ተጽፎለት መልእክቱ ሲደርሰው ፈጥኖ ተነሣ በዋሻ ከሚኖር ከአቡነ ጰንጠሌዎን በረከትን ተቀብሎ ለአቡነ አረጋዊም በጸሎት እንዲያስቡት ደብዳቤ ጽፎ ከላከ በኋላ ከሠራዊቱ ጋር በመርከብ ተጭኖ ወደ ሀገረ ናግራን ሄደ፡፡
ከመሄዱም በፊት ለአቡነ አረጋዊ የላከላቸው መልእክት እንዲህ የሚል ነው፡- ‹‹ፊንሐስ የተባለ አረማዊ የናግራን ክርስቲያኖችን ደም በከንቱ ያፈሰሰ፣ ቤተክርስቲያንን የመዘበረና ያጠፋ ፍጹም የእግዚአብሔር ጠላት ወደሚሆን ሔጄ እዋጋው ዘንድ ተዘጋጅቻለሁ፡፡ ስለዚህ አባቴ ሆይ! አንተም በበኩልህ ጸሎት አድርግልኝ፣ የጻዲቅ ጸሎት ትራዳለች፣ ኃይልንም ታሰጣለች፣ በጠላት ላይ ድልንም ታቀዳጃለችና›› ሲል ላከበት፡፡
አባታችን አቡነ አረጋዊም ለንጉሡ ጭፍሮች ‹ወደ ጦሩ ግንባር ሒድ፣ እግዚአብሔር ጠላቶችህን ከእግርህ በታች ያስገዛልህ፣ ለአንተም ግርማ ሞገስ ይስጥህ፣ በሰላም ይመልስህ›› ብለው መርቀው ላኩበት፡፡ ከዚህ በኋላ ዐፄ ካሌብ ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ ጥሎ ማቅ ለብሶ በፍጹም ልመና ብዙ ጸሎት ካደረገ በኀላ ወደ የመን ሳባ በመርከብ ተጓዘና ከከሐዲው ፊንሐስ ጋር ጦር ገጠመ፡፡ ከሐዲውን ንጉሥ ፊንሐስን ራሱ ዐፄ ካሌብ ገጠመውና በፈረሱ ላይ እንደተቀመጠ በጨበጣ በጦር ወግቶ ገደለውና ወደ ባሕር ገልብጦ ጣለው፡፡
ከዚያም ዐፄ ካሌብ ዛፋር ወደምትባለው ከተማ ሔዶ እርሷንም ተቆጣጠራት፡፡ በእዚያም ያሉ የፊንሐስን ሹማምንቶች እያፈላለገ በአደባባይ እንዲገደሉ በማድረግ የክርስቲያኖቹን ደም በሚገባ ተበቀለ፡፡ የናግራንንም ሕንፃዎቿዋን አደሰ፤ የሰማዕታቱንም መታሰቢያ አቆመ፡፡ ወደ እስክንድርያው አባ ጢሞቴዎስና ወደ ሮሜው ንጉሥ ዮስጢኖስም የድል መልእክት ላከላቸውና እነርሱም ሰምተው እጅግ ተደሰቱ፡፡ በአንጾኪያ፣ በእስክንድሪያ፣ በሮም፣ በቊስጥንጥንያና በዓለም ላይ ያሉ ክርስቲያኖች ሁሉ ይህን ሲሰሙ በእጅጉ ተደሰቱ፡፡ ይህም የሆነው በ525 ዓ.ም ነው፡፡ ጠፍተው የሔዱ ክርስቲያኖችንም ሰበሰባቸውና ወደቀደመ ቦታቸው መለሳቸው፣ ቤተክርስቲያናቸውን አነጸላቸው፡፡ ከሳባ ሀገር የማረከውን ንብረት ሁሉ ለቤተክርስቲያን ሰጥቶ ዓሥር ሺህ ጠባቂ ሠራዊት ሰቷቸው ወደ አክሱም በሰላምና በፍጹም ደስታ ተመለሰ፡፡
ንጉሡ ዐፄ ካሌብ የናግራን ሰማዕታት ደም ተበቅሎላቸው ሁሉንም ነገር አስተካክሎላቸው በደስታ ወደ አክሱም ከተመለሰ በኋላ ‹‹ይህን ያደረገልኝን አምላኬን በምን ላስደስተው?›› ሲል አሰበና ተድላውን፣ ደስታውን ዓለምን ንቆ፣ ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ አንዲት የውኃ መንቀልና አንዲት ምንጣፍ ብቻ ይዞ አባ ጰንጠሌዎን ገዳም አጠገብ ከሚገኝ ዋሻ ውስጥ ገብቶ በአባ ጰንጠሌዎን እጅ መንኩሶ ለመቀመጥ ወሰነ፡፡ አባ ጰንጠሌዎንንም ‹‹አመንኩሰኝ›› አላቸውና የመላእክትን አስኬማ አልብሰው አመነኮሱት፡፡ ዐፄ ካሌብም ዳግመኛ ከዋሻው ወጥቶ ዓለምን በዐይኑ እንዳያይ ማለ፡፡ ዋጋው እጅግ የከበረውንና በነገሠ ጊዜ የጫነውን ዘውዱን ከጌታችን መካነ መቃብር ወይም በር ላይ ይሰቅልለት ዘንድ ከአደራ ደብዳቤ ጋር ለኢየሩሳሌሙ ሊቀ ጳጳሳት ለአባ ዮሐንስ ላከለት፡፡ ዳግመኛም ንጉሡ ዐፄ ካሌብ ‹‹አባቴ ሆይ በአንተ ጸሎት በእግዚአብሔር ቸርነት ከጦርነቱ በሰላም ተመልሻለሁ፤ አሁንም የክርስቶስን አርዑተ መስቀል ተሸክሜአለሁና እግዚአብሔር ለፍጻሜው ያብቃህ እያልህ ስለ እኔ ጸልይልኝ›› ብሎ ወደ አባታቸን ወደ አቡነ አረጋዊ ላከበት፡፡ ስለዚህም ነገር አቡነ አረጋዊ በጣም ተደሰቶ ‹‹ልጄ ሆይ! መልካሙንና የበለጠውን አድርገሃል፣ አሁንም እግዚአብሔር የፈቀደከውን ነገር ሁሉ ይፈጽምልህ›› ብለው መረቁት፡፡ ኢትዮጵያዊው ንጉሥ ዐፄ ካሌብ ይህን ዓለም በመናቅ በበረሃ በዋሻ 12 ዓመት በጾም በጸሎት በብዙ ተጋድሎ ከኖረ በኋላ ግንቦት 20 ቀን ዐርፎ እስከ ዘለዓለሙ ድረስ የማያልፍ ሰማያዊ ክብርን ወርሷል፡፡ መካነ መቃብሩም አክሱም በአባ ጰንጠሌዎን ገዳም ምድር ቤቱ ውስጥ ይገኛል፡፡
ይኸውም አባ ጰንጠሌዎን ከተሰዓቱ ቅዱሳን ውስጥ አንዱ ሲሆን በገዳሙ ውስጥ ሳይቀመጥ ሳይተኛ በእግሩ ቆሞ 45 ዓመት የጸለየ የበረከት አባት ነው፡፡ ምድራዊ ወይም ሥጋዊ የሆኑ ፍትወታት ፈጽመው ጠፍተውለታልና ከመላእክትም ማኅበር ጋር አንድ ሆኗልና ከፍጹም ምስጋና በቀር እህል ወይም ውኃ ወይም ቅጠል እንኳ አይቀምስም ውኃም አይጠጣም ነበር፡፡ እርሱም የንጉሥ ልጅ ስለነበር አስቀድሞ ንግሥናን ንቆ የመነነ ነው፡፡ የመንፈስ ወንድሞቹም እንዲሁ፡፡
እነዚህም ተሰዓቱ ቅዱሳን ሁሉም የነገሥታት ልጆች ሲሆኑ በዓለም ነግሠው መኖርን እርግፍ አድርገው ትተው ከያሉበት ከቁስጥንጥንያ፣ ከአንጾኪያ፣ ከግሪክ፣ ከእስያ፣ ከሮምያና ከቂሣርያ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በአንድነት ተሰባስበው በአባ ጳኩሚስ ገዳም ገብተው በምንኩስና ሲኖሩ ኢትዮጵያ በሃይማኖት በምግባር ያጌጠች ቅድስት ሀገር መሆኗን ሲሰሙ ‹‹ይህችንማ ሄደን ማየት አለብን›› ተባበብለው ያላቸውን ሁሉ ይዘው ታቦቶቻቸውን፣ ካህናቶቻቸውን፣ ንዋየ ቅድሳቶቻቸውን፣ መጻሕፍቶቻቸውን ሁሉ ይዘው በዘሚካኤል (አቡነ አረጋዊ) መሪነት በመምጣት በ460 ዓ.ም ጳጳሱና ንጉሡ ካሉበት አክሱም ከተማ ገቡ፡፡
በዚያም ለ12 ዓመታት በፍጹም አንድነት አብረው ከተቀመጡ በኋላ ‹‹እርስ በራሳችን እየተያየን ብንኖር ተድላ ደስታ ይሆንብናልና ተለያይተን እንቀመጥ›› ብለው ተማከረው በተለያየ በዓት በተጋድሎ መኖር ጀመሩ፡፡ አባ ሊቃኖስ በደብረ ቁናጽል፣ አባ ጰንጠሌዎንም በእርሱ ትይዩ በሆነ ቦታ፣ አባ ገሪማ በደብረ መደራ፣ አባ ጽሕማ በደብረ ጸድያ፣ አባ ይምአታ በደብረ ገረዓልታ፣ አባ አፍጼ በደብረ ይሐ፣ አባ አሌፍ በደብረ አኅድአ መኖር ጀመሩ፡፡ አባ አረጋዊ ደግሞ በጣም ርቀው በመሄድ በደብረ ዳሞ በዋሻና በፍርኩታ ውስጥ በተራራም ላይ መኖር ጀመሩ፡፡
ተሰዓቱ ቅዱሳን ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን ያደረጉ ነበር፣ ተአምራቶቻቸውን መንፈሳዊ ዐይኑ ያልበራለት ሰው ከቶ ሊረዳውና ለገነዘበው አይችልም፡፡ መላእክትም ዘወትር ባለመለየት ይጎበኙዋቸው ነበር፡፡ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስም ዘወትር እየተገለጠላቸው ይባርካቸውና ቃልኪዳን ይሰጣቸው ነበር፡፡ በጸሎታቸውም አጋንንትን ያስወጣሉ፣ ድውያንን ይፈውሳሉ፣ ዕውራንን ያበራሉ፣ ሙታንን ያስነሣሉ፡፡ ለእያንዳንዳቸውም የሃይማኖታቸውን ኃይል አሳዩ፡፡ ከእነርሱ መካከል ተራራ ያፈለሱ አሉ፣ ባሕሩን ከፍለው ደረቅ መንገድ ያደረጉ አሉ፣ ጠዋት ዘርተው ማታ ሰብስበው የሚያጭዱ አሉ፣ ይኸውም የስንዴውን ነዶ በግራር ዛፍ ላይ አበራይተው የዛፉ ቅጠል ሳይረግፍ በሬዎቹም ከዛፉ ላይ ሳይወድቁ ምርቱ ብቻ እየወረደ በአውድማው ላይ እንዲከማች ያደረጉ አሉ፣ ወዲያውም ስንዴውን ለመገበሪያ ሠይመው ለዘጠኝ ሰዓት መሥዋዕተ ቊርባን ያደረሱ አሉ፡፡
በዓለት ድንጋይ ላይ የወይራ ተክል ተክለው በዚያኑ ጊዜ ጸድቆ ለምልሞ ታላቅ ዛፍ ከሆነ በኋላ በእግዚአብሔር ፈቃድ ግንዱ ደርቆ ቆርጠውና ፈልጠው እንጨቱን አንድደው እሳቱ ፍም ከወጣው በኋላ ፍሙን በቀጭን ሻሽ ወስደው ለዘጠኝ ሰዓት የቅዳሴ ማዕጠንት ያደረሱ አሉ፡፡ ለቤተክርስቲያን አገልግሎት የሚውልና ለሥርዓተ ቊርባን ማከናወኛ የሚሆን ውኃው ሳይፈስ በወንፊት ውኃ የሚቀዱ አሉ፡፡
ከእነሱም አንዱ በዐረፈ ጊዜ የሥጋው ሥርዓተ ግንዘት በመላእክት እጅ የተከናወነ አለ፡፡ ይልቁንም ቁመቱና ርዝመቱ ከታላላቅ ገደል እጅግ በጣም የሚበልጥ የድንጋይ ዓምድ ከወንዝ ማዶ ዘንበል ብሎ መጥቶ ሥጋቸውን በክብር ተቀብሎ በተራራው ጫፍ ላይ እስከዛሬም ድረስ ፈጽሞ ሳይነቃነቅና ሳይናወፅ ቀጥ ብሎ ቆሞ ይገኛል፡፡ የሰዎቹም የመግነዝ ምልክት ጥበበኛ እንደሣለው ሥዕል በድንጋዩ ዓምድ ላይ ተስሎ ወይም ተቀርፆ ይታያል፡፡ ቆመው ጸሎት በሚጸልዩበት ጊዜ ዓሥሩ የእጆቻቸው ጣቶችና ዓሥሩ የእግሮቻቸው ጣቶች እንደፋና የሚያበሩበትና እንደመብረቅ የሚብለጨልጩበት ጊዜ አለ፡፡
ሀገራችን ኢትዮጵያ ያለአንዳች ሐዋርያ ስብከት አስቀድማ በክርስቶስ እንዳመነችና በዚህም ምክንያት የልዕልናዋን ታሪክ ለዓለም ለማሳወቅ ፈጥነው የሄዱ አሉ፡፡ የኢትዮጵያ ምድር በእነዚህ የቅዱሳን ኪደተ እግር ተቀደሰች፣ በውስጧም በመመላለሳቸው አውራጃዎቿና አደባባዮቿ ሁሉ ታደሱ፡፡ መዓዛ ትምህርታቸውና ተአምራቶቻቸው በሁሉም አውራጃዎች ተሠራጨ፣ የእምነቷንም መሠረት አጸኑ፡፡
የቅዱሳኑ ምልጃቸውና በረከታቸው በአማላጅነታቸው በምንታመን በሁላችን ላይ ይደርብን! አሜን!!!