Monday, January 4, 2016

ፃድቃኔ ማርያም - ድንቅ ተአምር

ዛሬ ፃድቃኔ ማርያም ሄጄ በአይኔ ያየሁትን ተአምር ልፅፍላችሁ ወደድኩኝ፡፡ ቀኑ ቅዳሜ ነው ፤ ሰዎች አብዛኛውን ጊዜ ወደ ፃድቃኔ ለመሄድ የሚነሱበት ቀን ስለሆነ መጀመሪያ የሚወጣው አውቶቡስ እንዳያመልጠን ከባለቤቴ ጋር በጠዋት ነበር አውቶቡስ ተራ የደረስነው ፤ ነገር ግን ሰው እዛ ያደረ ይመስል 12፡00 ላይ አውቶቡሱ ሞልቶ መንቀሳቀስ ጀምሮ ነበር፡፡ ባለቤቴም ‹‹አይ በዚህም ሰዓት ደርሰን አመለጠን ይገርማል ተወው ባክህ እመቤቴ እንደፈቀደች›› አለችኝና ሁለተኛው አውቶቡስ ላይ ገባን፡፡ ይህኛው ደግሞ ቀጥታ ዘላቂ ሰው ስላጣ የመንገድ ሰዎችንም በመጫን ነበር የሞላው፡፡ ጉዞ ወደ ፃድቃኔ ማርያም ፤ ውዳሴዋን ደግመን ጉዞ ጀመርን፡፡ መኪናው ሲያወርድ ፤ ሲጭን 9፡00 አካባቢ ደብረ ምጥማቅ ደረስን ፤ እዚህ እንውረድና በአቋራጭ እንሂድ ተባብለን ሰላ ድንጋይ ሳንደርስ ወረድን ፡፡ እቃችንን ለአንድ የሀገሬው ሰው አሸክመን አቋራጩን ተያያዝነው ፡፡ ልጁ እንዲህ አለን ‹‹ ዛሬ ግን ማደሪያ የምታገኙ አይመስለኝም በጣም ብዙ ሰው ነው የመጣው አለን›› :: ‹‹ችግር የለውም ውጪ አንጥፈን እናርፋለን ለመተኛት መች መጣን›› አልነው፡፡

ደጇን ስንረግጥ ልጁ ያለው አልቀረ የወንዶች ማረፊያ ሁለቱም አዳራሽ ከአፍ እስከ ገደቡ ሞልቷል ፤ በረንዳውን ላይ ብናይ የበረንዳው ይብሳል ፡፡ የኔን ማረፊያ ውጭ አነንጠፍንና የእሷን ለማየት ወደ ሴቶች ማረፊያ እያቀናን ሳለ ፤ አንዲት መንፈስ ያደረባት ሴት ፤ እጇም እግሯም በሰንሰለት ታስራ እንዲ እያለች የእመቤታችንን ማዳን ትመሰክራለች ‹‹ ዛሬ ደግሞ ኪዳነምህረት ድንቅ ነገር ሰርታለች ሂዱነና እዩ›› እያለች ለሰዎች ስትናገር እንደ አጋጣሚ እኔም ሰማሁ፡፡ እሷ የጠቆመችን ቦታ ላይ ስንሄድ አንዲት የ12 ዓመት ህፃን ልጅ እና እህትየዋ አንድ ላይ ቆመው ተመለከትን ፡፡ ጠጋ ብለን ምን ተደርጎላቸው ነው ስል ስጠይቅ ‹‹ የዚች ህፃን አይኗ በራላት›› ሲሉ ነገሩን፡፡ ለኔ የተደረገልኝን ያህል ደነገጥኩኝ፤ በጣምም ደስ አኘኝ፡፡ እህትየዋ የምትይዘውን የምትጨብጠውን ነገር አጥታ ነበር ፡፡ ታናሽ እህቷ የተደረገላትን ነገር እያየች ከአእምሮዋ በላይ ስለሆነ እና ደስታው ፈንቅሏት ታለቅሳለች ፤ እኛም ገርሞን ማደሪያችንን ትተን ልጅቷ ጋር ረዥም ደቂቃዎች ስለሁኔታ ለመስማት እዛው አረፍ አልን ፡፡ እህትየዋም ሰዎች ጥያቄዎችን ሲጠይቋት እንዲህ አለች ፡-

‹‹ ቤት ውስጥ ከእኩያዎቿ ጋር ስትጫወት የበረንዳ ብረት አይኗን መታት ፤ ለጊዜው ከማበጥ ውጪ ምንም አልሆነም ነበር ፤ ነገር ግን በጊዜ ሂደት አይኗ እያበጠ መጣ ፤ እይታዋንም ጋረዳት ፤ ትምህርቷንም አቋርጣ ለ6ወር ያህል ህክምና ፍለጋ አሉ የተባሉ የአይን ስፔሻሊስቶች ጋር ብራችንን አውጥተን ሄድን ፤ መፍትሄ ግን ሊመጣ የልጅቷም አይን ማየት ግን አልቻለም ፤ ቤተሰባችን ጭንቅ ውስጥ ገባ ፤ በመጨረሻ እመቤቴ እንዳደረገች ታድርጋት ብይ እዚህ ይዣት መጣሁ ዛሬ ሶስተኛ ቀናችን ነው ፤ ለሶስት ቀን ያህል ፤ ጠዋት ተሸክሜአት ጸበል እወስዳታለሁ ፤ እምነቱን ከፀበል ጋር ደባልቄ አይኗ ዙሪያው ላይ እቀባታለሁ ፤ ይህው እናንተ እንደምታዩት እግዚአብሄር ፈቅዶ ዛሬ አይኗ ሊያይ ችሏል›› ብላ ለቅሶ፡፡

‹‹ሁሉን የምትገዛ ጌታ አምላክ ሆይ፥ ሥራህ ታላቅና ድንቅ ነው›› ዮሀንስ ራዕይ 15 3-4 ፤ ‹‹ይህች ከእግዚአብሔር ዘንድ ሆነች፥ ለዓይናችንም ድንቅ ናት።›› መዝሙረ ዳዊት118፥23 ከማለት ውጪ ሌላ ምን ይባላል፡፡አምኖ የመጣ እንዲህ ይደረግለታል ፤ ብዙዎቻችን ግን እግዚአብሔር ቤት ስንሄድ በሁለት ልብ ሆነን ነው ፤ ስንመለስም ከሁለት ያጣ የምንሆነው ለዚህ ይመስለኛል፡፡
ያየነውን ነገር ማመን እስኪያቅተን ድረስ እየተገረምን ማረፊያ ፍለጋ ስንንቀሳቀስ ሰዎች ተሰብስበው አየን ፡፡ ሁሌ ማታ 11፡00 ላይ በወንዶች ማረፊያ አካባቢ እና በሴቶች ማረፊያ አካባቢ አዲስ ለመጡ ሰዎች የቦታውን ስርዓት ፤ ምን እንደሚደረግ ፤ ምንስ እንደማይደረግ አባቶች ለ30 ደቂቃ ያህል ያስረዳሉ፡፡ ጠጋ ስንል ተረኛው አባት እንዲህ ሲሉ ነገሩን፡-

‹‹ ይህውላችሁ ልጆች ሀገር አቋርጣችሁ ከተለያየ ቦታ እዚ የመጣችሁት እናንተ ፈልጋችሁ ብቻ አይደለም ፤ እግዚአብሔርም ፈቅዶላችሁ ጭምር ነው፡፡ ስለዚህ እሱ ፈቅዶ እና ወዶ እስካመጣችሁ ድረስ የመጣችሁበትን አላማ የሚያስተጓጉል አንዳች ነገር ማድረግ የለባችሁም ፤ ይህ ቦታ የምህላ ፤ የፀሎት ፤ የሱባኤ ቦታ ነው ፤ እዚህ ቦታ ላይ ከእናንተ የሚጠበቅባችሁ ነገር አለ እርሱም ፡- ወደ ገዳም ስትወርዱ ጫማችሁን አድርጋችሁ መግባት አይቻልም ፤ ሴቶችም ወንዶችም በገዳም ውስጥ ስትመላለሱ ክርስትያናዊ አለባበስ መልበስ አለባችሁ ፤ በማደሪያችሁም ሆነ ገዳም ስትወርዱ ጮክ ብሎ መነጋገር አይቻልም ፤ ብዙ ሰዎች አርምሞ ስለሚይዙ እነሱንም መረበሽ ስለሆነ ይህ አጥብቆ የተከለከለ ነው ፤ የቻለ በቀን ሰባት ጊዜ ፀሎት ማድረስ አለበት፤ ካልቻለህ ግን ሶስቱን ጸሎት ማስተጓጎል የለበትም ፤ ከሰኞ እስከ አርብ ድረስ በሽተኛ ካልሆነ በቀር ምግብ 12 ሰዓት ላይ ነው መብላት የሚቻለው እስከዚያ ሁሌ ጾም ነው(ከበዓለ 50 በቀረ) ፤ የተፈቀዱት ምግቦች ቆሎ ፤ባቄላ ፤ ጥጥሬዎች እና በሶ ከሰኞ እስከ አርብ ሲሆን ቅዳሜ እና እሁድ ዳቦ መብላት ይፈቀዳል ፤ እንጀራ እና ወጥ ገዳም ውስጥ ባላችሁበት ጊዜ መብላት አይቻልም ፤ ጸበል ጠዋ በ11 ይከፈታል ከዚያ በፊት ጸበል መውረድ አይቻልም እስከ ሰባትም ስንትም ሰዓት ይቆያል ፤ እዚህ ቦታ ላይ በዓመት 1ጊዜ ብቻ ነው ቅዳሴ ያለው ፤ ጠዋት ሊነጋ ሲል 11 ሰዓት ላይ ኪዳን ማድረስ ፤ ሲነጋ ትምህርተ ወንጌል መሳተፍ ፤ከ ሰዓት ከ9፡40 ጀምሮ ምህላ ማድረስ አለባችሁ የዛኔ ነው የመጣችሁበትን አላማ እና እናንተ የምትገናኙት ›› እያሉ ብዙ ነገር ነገሩን መከሩን፡፡

እኛ እንኳን ለ3 ቀን ነው የመጣነው ገዳም ውስጥ የሚኖሩ መነኮሳት ይህን ሁሉ ችለው ነው የሚኖሩት? ይገርማል ፤ እግዚአብሔርም አለምን ትተው እሱን ብለው የመጡትን ያስችላቸዋል:: በመጨረሻም ፀሎት አድርገውልን ወደ ማደሪያችን ሸኙን፡፡ ይህን ስመለከት ብዙ ቦታዎች ስንሄድ የቦታውን ስርዓት ሳናውቅ የምናጠፋ ሰዎች እንበዛለን ፤ ልክ እንደ ፃድቃኔ ማርያም ገዳም ቀን በቀን ሳይሰለቹ እንደዚህ አይነት ነገሮች ሁሉም ቦታ ቢለመድ ጥሩ የሚል ሀሳብ አለኝ፡፡

የሚቀጥለው ቀን ጠዋት
ለሊት ኪዳን አድርሰን ወረፋው እንዳይበዛ ፀበል ወረድን ፤ ፀበል ተጠምቀን ስናበቃ ለመጠጣት አንዱ ልጅ ጋር ጠጋ ብዬ ቁጭ አልኩ ፤ ጎንበስ ብዬ ሳየው አንዳች ነገር ጉልበቱ ላይ ትልቅ እጢ ቋጥሮ ተመለከትኩኝ ፤‹‹ወንድሜ ምን ሆነህ ነው›› አልኩት፡፡ እሱም ‹‹ ተወኝ ባክህ ልቤ ደንድኖ አልሰማ ብዬ ነው እንዲ የሆንኩት አለኝ››፡፡ አልገባኝም አልኩት ‹‹ሰው ንስሀ ገብቶ ወደ በፊቱ ምግባሩ ከተመለሰ የባሰውን ነው የሚሸከመው አለኝ›› ይባስ ግራ አጋባኝ፡፡ ቀስ ብለህ ልታስረዳኝ ትችላለህ አልኩት፡፡ እርሱም፡-
‹‹ ትውልዴ አዲስ አበባ ነው የ22 አካባቢ ልጅ ነኝ ፡፡ይህውልህ የዛሬ 2 ዓመት በፊት እጠጣለሁ ፤አጨሳለሁ ፤ እጨፍራለሁ ብቻ ምንም ከሀጢያት የቀረኝ ነገር የለም ሁሉን አደርጋለሁ ፡፡ በዚህ ሁኔታ ላይ ሳለሁ የዚያን ጊዜ ጉልበቴ ላይ ከዚህ በፊት ሆኖ በማያውቅ በልክ ትልቅ እጢ ወጣብኝ ፤ ብዙ ቦታ ብሄድ ኦፕራሲዮን መሆንን ነበር እንደ መፍትሄ ያስቀመጡልኝ ፤ እሱን ደግሞ እኔ አልፈልገውም ፡፡ እናቴ እስኪ ፃድቃኔ ሂድ አለችኝ ፤ ‹‹ምን ማለትሽ ነው ዶክተሮች ኦፕራሲዮን እያሉ እዛ ምን ልሰራ ነው የምሄደው›› ብዬ ከእሷ ጋር ተጣላን ፤ ውዬ አድሬ ሳስበው መሄድ እንዳለብኝ ውስጤ ነገረኝ ፡፡ ከአዲስ አበባ ተነስቼ በሶ እና ቆሎ ብቻ በመያዘ ቀጥታ እዚህ ቦታ መጣሁ ፤ አንድን አባት አግኝቼ ችግሬን ስነግራቸው በደንብ አደመጡኝና ‹‹በል አሁን ጸበል እንዳትጀምር ፤ ንስሀ ግባ፤ ቀኖናህን ስትጨርስ መጠመቅ ትችላለህ›› አሉኝ፡፡ እሺ ብዬ ንስሀዬን ከራሴ ላይ አወረድኩኝ ፤ ቀኖናዬን ጨረስኩ ፤ከዚያ ጸበል መጠመቅ ስጀምር ሰዎች እምነት ሲቀቡ ተመለከትኩኝ ፤ ለምን እኔስ አልቀባም ብዬ ጸበሉን ከእምነት ጋር እየደባለኩ ቁስሉን መቀባት በጀመርኩኝ በሶስተኛው ቀን ተሸክሜ የመጣሁትን እጢ በመግል መልክ ከሰውነቴ ወጥቶ አለቀ ፤ ተሸሎኝ ወደቤቴ ስመለስ እማዬ ስታየኝ ማመን አልቻለችም ነበር ፤ አለቀሰች ፤ እመቤቴን ወላዲተ አምላክን ማመስገኛ ቃላት አጣች ፤ እኔም ለአንድ ዓመት ያህል ከቤተክርስትያን አልራኩም ነበር ፡፡ የሆነ ጊዜ ላይ ግን ከቤቱ ጠፋሁ ፤ ወደ ቀደመ ምግባሬ ቀስ እያልኩ ገባሁበት ፤ የተደረገልኝን ነገር ዘነጋሁ ፤ ይህው አሁን ደግሜ የዛሬ ሁለት ዓመት ይዥው የመጣሁትን እጢ አሁን ተመልሶ መጣብኝ ›› ብሎ ሲነግረኝ ሰውነቴን አንዳች ነገር አራደኝ፡፡

ስንቶቻችን ነን ገብተን የወጣን ፤ ውለታውን የዘነጋን ፤ የተደረገልንን ነገር የረሳን ፤ ከሞት አፋፍ ከጠላት ወጥመድ ጠብቆ አሳልፎን ዛሬ ላይ ከቤቱ ሸርተት ያልን? ቤት ይቁጠረው ፡፡ እኔ አይኔ የልጁ እጢ ላይ ነው ፤ ልጁ ደግሞ አይኑ እኔ ላይ ነው ፡፡ ‹‹ አሁን አኮ ቀንሶ ነው ያየህው›› አለኝ ፡፡ ‹‹ሳይቀንስ ባየው የቱን ያህል ነበር?›› ብዬ ራሴን ጠየኩኝ፡፡እንዲህ ሲል ቀጠለልኝ ‹‹ ትላንት ምልክት አይቻለሁ በጥቂት ቀናት ውስጥ አፍስሳ ትጨርስልኛለች ፤ በአውራ ጣቴ በኩል በቢጫ ፈሳሽ መልክ ትንሽ ትንሽ ሲወጣ ተመልክቻለሁ ፤ ከአሁን በኋላ ግን ወደ በፊቱ ማንነቴ እንዳልመለስ እግዚአብሔር ይጠብቀኝ ፤ እርግጠኛ ነኝ አሁን እድናለሁ አለኝ፡፡›› የልጁ እምነት ገረመኝ፡፡ ስንቶቻችን ነን አፋችንን ሞልተን በእምነት ‹‹እድናለሁ›› ማለት የምንችል ፤ እንዲህ ለማለትም ፍጹም እምነት ያስፈልጋል፡፡ የመጣሁበትን ጉዳዬ እረስቼ ቁጭ ብለን ስለራሱ ፤ አዛው ቦታ ላይ ስላየው ተዓምር ሲነግረኝ ሰዓቱ መዝለቁን አላስተዋልኩም ነበር፡፡ መጨረሻ ላይ ‹‹በል እመብርሀን ወላዲተ አምላክ ትርዳህ ፤እግዚአብሔር በምህረቱ ይጎብኝህ›› ብዬው ወደ ማረፊያየ ለመሄድ ብድግ አልኩ ፡፡መሬት መሬት አቀርቅሬ ፤ የነገረኝን ታሪክ ከራሴ ጋር እያቆራኝውት እንደ ውሻ የተፋሁትን ነገር ደግሜ የላስኩበትን ሁኔታዎች ሳወጣ ሳወርድ ምንም ሳላውቀው ማረፊያዬ ጋር ደረስኩኝ፡፡

የ ኪዳነ ምሕረት ተአምር

የወላዲተ አምላክ ድንቅ ተአምር

 

Thursday, December 24, 2015

አንዲት እህት ከሆዷ ውስጥ ጥቁር ወፍ ወጣላት

በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በደብረ ወልደ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ እና በመካነ ጎለጎታ ቅድስት ማርያም ጠበል ሰሞኑን ከአንዲት እኅት ከሆዷ ጥቁር ወፍ ወጣላት፡፡ በክርስትና ስሟ መንበረ ማርያም ተብላ የምትጠራው እኅት ለ20 ዓመታት ያህል በሆድ ሕመማት ስትሰቃይ መቆየቷን የምትናገረው መንበረ ማርያም፤ ስቃይዋን በዘመናዊው ሕክምና ለማስታገስ ያልሔደችበት ቦታና ያልወሰደችው መድኃኒት የለም፡፡ ይሁንና የምትወስደው ሕክምና ለጊዜው ስቃይዋን ከማስታገስ በስተቀር ከሕመሟ ልትድን ባለመቻሏ ከዚህ በኋላ ይግደለኝ እንጂ ሕክም ናም ሆነ መድኃኒት መጠቀም የለብኝም፤ ብላ ጠበል ለመጠመቅ እንደ ወሰነች ትናገራለች፡፡ በውሳኔዋም መሠ ረት ወደ ወልደ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተክርስቲያን ጠበል በመሄድ ስትጠመቅ በላይዋ ላይ የሰፈሩ 681 አጋንንት እንዳሉ በላይዋ ላይ ያደሩት የሰይጣን ሠራዊት ለፍልፎ በጥቁር ወፍ አምሳል ከሆዷ ውስጥ ሊወጣላት ችሏል፡፡ ምእመናን በዕለቱ ከሆዷ ውስጥ በትውከትነት እንደ ጥይት ተወርውሮ የወጣውን ጥቁር ወፍ ከነሕይወቱ በማየት በቪዲዮ በመቅረጽ የእግዚአብሔርን ድንቅ ተአምር እንደ መሰከሩ ተገልጿል፡፡


የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ ሰምቶ ይህንኑ ወፍ የወጣላትን መን በረ ማርያምንና ያጠመቋትን አባት ሊቀ ትጉኃን ስሙር አሐዱን በማነጋገር ድርጊቱ እንዴትና ምን ይመስል እንደነበር በሰፊው ዘግቧል፡፡

እግዚአብሔር ሥራው ድንቅ ነው፤ ተዓምሩ ዕፁብ ነው፤ ተነግሮ አያልቅም፤ ይህን ሥራውን መመስከር ደግሞ የእኛ ተግባር ነው፡፡ ለረጅም ዓመታት በሕመም ስትሰቃይ የነበረች በስመ ጥምቀቷ መንበረ ማርያም የተባለች ወጣት የእግዚአብሔርን የድንቅ ሥራው መገለጫ ሆናለች፡፡

ለዚህች እህት እግዚአብሔር ያደረገላት ገቢረ ተአምር ሲሰሙት ለጆሮ የሚከብድ፤ እንዲሁም በወቅቱ ድር ጊቱ ሲፈጸም የተመለከቱ ምእመናንን ሁሉ ያስደመመ ነበር፡፡ «ማን ያርዳ የቀበረ፤ ማን ይናገር የነበረ» ነውና ሥረ መሠረቱ ምን፣ እንዴትና መቼ ሆነ? የሚለውን ጉዳይ እሷው ባለታሪኳ እንዲህ ትተርክልናለች፡፡

«ያመኝ የነበረው ገና የአራት ዓመት ልጅ እያለሁ እሰቃይ ነበር፡፡ ለምሳሌ የራስ ምታት፣ ነስር፣ የሆድ ቁርጠት፣ የአንጀት ኢንፌክሽን ወዘተ እየተባለ በመታመም ሁልጊዜ ሐኪም ቤት እመላለስ ነበር፡፡ እናቴ እንደ ነገረችኝ የሕመሙ መነሻ ወተት ነው፡፡ «ወተት ጠጥተሽ የአንጀት ኢንፌክሽን ያዘሽ» ያለችኝ እናቴ በየክሊኒኩ እየወሰደችኝ ስታስመረምረኝ መድኃኒት እንደሚያዙልኝ አጫውታኛለች፡፡ ራሴን ማወቅ ስጀምር ትምህርት ቤት ገብቼ ስማር ሆዴን ያመኛል፡፡ በተለይ በበጋ ወራት ተምሬ ሁለት ወር ክረምት በሚሆንበት ወቅት ክፉኛ ያመኛል» ስትል ተናግራለች፡፡

መንበረ ማርያም በሕመሟ መጥናት ብዙ ጊዜ ሐኪም ቤትና ክሊኒክ ተመላልሳ እንደታከመች ገልጻል ናለች፡፡ ነገር ግን ጠበልስ አልሞከረች ይሆን? የሚለው ጥያቄ አጫረብንና ጠየቅናት፤ እርሷም ስትመልስ «በዚያን ወቅት ቤተሰቦቼ የሚያስቡት ሐኪም ቤት የሚባለውን እንጂ ጠበልን አልነበረም፡፡ እኔም ቢሆን በወ ቅቱ ጠበልን አላሰብኩትም፤ ብቻ ሐኪም ቤት ሔጄ የተለያየ መድኃኒት ይታዘዝልኛል እወስዳለሁ፡፡ ለጊዜው ያስታግሥልኛል፤ ጨርሶ ግን ሊያድነኝ አልቻለም፡፡ ይባስ ብሎ የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና ወስጄ ጥሩ ውጤት በማምጣት አራት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ ገብቼ የመጀመሪያ ዓመት መማር ስጀምር በሽታው ክፉኛ አሰቃየኝ፡፡ ያስጨንቀኛል፣ ከፍተኛ የራስ ምታት ሕመም ይሰማኛል፤ ማጥናት አልችልም ነበር፡፡ የሴሚስተር ፈተና ደርሶ ሁለት ሳምንት ሲቀረው አንደኛው ዐይኔ ውስጡ ሲቆስል ሌላኛው ዕንባ ማፍሰስ ጀመረ፡፡ ዕንባው ያለምንም ማቋረጥ ለ24 ሰዓታት ይወርዳል፡፡ ቤተሰቦቼ ሁኔታው አላምር ቢላቸው ወደ አንዲት ታዋቂ የዐይን ሐኪም ወሰዱኝ፡፡ እሷም 'በሕይወቴ እንዲህ ዐይነት ነገር ዐይቼ አላውቅም፤ ዐይኗ ውስጥ ቁስል አለና የመታት ነገር አለ ወይ?' ብላ ጠየቀች፡፡ ይሁንና ቤተሰቦቼም ሆኑ እኔ ምንም ነገር የመታኝ ነገር እንደሌለ ለዶክተሯ ነገርናት፡፡ በየሰዓቱ የሚደረግ ጠብታ አዛልኝ ለጊዜው ተሻለኝ፡፡ የከፍተኛ ትምህርቴን ግን ሳልማር ለሁለት ዓመት ያህል አቋረጥኩ» ትላለች የሕመሙን አስከፊነት የምትናገረው መንበረ ማርያም፡፡

መንበረ ማርያም እንደገለጸችልን በጤና መታወክ ሳቢያ ለጊዜው ትምህርቷን ብታቋርጥም ለትምህርቷ ያላት ቁጭት ከፍተኛ ስለነበር በሽታው መጣ ሔድ እያለ ቢያስቸግራትም ከዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በመግባት ትምህርቷን በሥራ አመራር የትምህ ርት ዘርፍ ለአራት ዓመታት ያህል ተከታትላ በ1996 ዓ.ም በዲግሪ ተመርቃለች፡፡

ይሁንና ሌላ ያላሰበችው ችግር ገጠማት፤ ይህስ ምን ይሆን? ለዚህም መንበረ ማርያም ስትናገር «የወር አበባዬ ከመጣበት ጊዜ አንሥቶ አሁን እስከዳንኩበት ጊዜ ድረስ በየወሩ በጣም እያመመኝ ክፉኛ ያሰቃየኛል፡፡ ስቃዩን ለማስታገሻ እያልኩ ፓ¬ራሲታሞል ክኒን በየአራት ሰዓት ልዩነት ሁለት ሁለት ፍሬ በመዋጥ በቀን 10 ፍሬ እወስድ ነበር፡፡ ሐኪም ቤትም ብሔድ የሚሰጡኝ መርፌ ነው፡፡ አልሻል አለኝ፡፡ የሕክምና ባለሙያዎቹ 'አግብታ ትውለድ፤ ሴቶች እንዲህ ዐይነት ሕመም ሲሰማቸው ይሻላቸዋልና መውለድ አለብሽ' ብለው አስተያየት ይሰጡኛል» ትላለች፡፡

እንደ መንበረ ማርያም አገላለጽ ብዙ ጊዜ መድኃኒትም መዋጥ ሌላ ችግር /Side-effect/ ስላለው መድኃ ኒት መውሰዱን ታቋርጣለች፤ «ከድጡ ወደ ማጡ» እንዲሉ ይባስ ብሎ በየወሩ ያማት የነበረው እንደ አዲስ የማያቋርጥ የማኅፀን ሕመም ይሰማት ጀመር፡፡ በዚህን ጊዜም በታወቁ የማኅፀን ሐኪም በመታየት በወር አበባ ሳቢያ የተነሣ በማኅፀኗ ውስጥ ትናንሽ ዕጢዎች እንዳሉ ይነገራትና የወር አበባዋ ከመምጣቱ በፊት ለአንድ ሳምንትና ከመጣም በኋላ ለአንድ ሳምንት የሚወሰድ ከባድና በጣም ውድ የሆነ መድኃኒት ይታዘዝላ ታል፡፡ ይህ የሆነው ከሁለት ዓመት በፊት ነው፡፡

«በዚህን ጊዜ የመጨረሻ ቁርጥ ውሳኔ ወሰንኩ» ትላለች መንበረ ማርያም፡፡ «መሞቴ ለማይቀር ነገር ለምን እሰቃያለሁ? በመድኃኒትስ ለምን እቃጠላለሁ?» በማለት ወደ ጠበል ቦታ ለመሔድ ወሰነች፡፡ ጠበሉን እንድትሞክር ያነሣሣትና ምክንያት የሆነቻት ደግሞ ጓደኛዋ እንደሆነች ተናግራለች፡፡ «አንድ ጓደኛዬ እንደ እኔ ዓይነት ሕመም ይሰማት ስለነበር ጻድቃኔ ማርያም ሔዳ ጠበል ጠጥታ እንደዳነች ነገረችኝ፡፡ እኔም ጠበል መጠጣትና መጠመቅ እንዳለብኝ መከረችኝ፡፡ መድኃኒቱን አቋርጬ ጠበል መጠመቅ ጀመርኩ፡፡ እየጾምኩ በተከታታይ ጠበሉን ስጠጣና ስጠመቅ በየወሩ የወር አበባዬ ሲመጣ ያመኝ የነበረውን ተወኝ፡፡ በመቀጠል ከማኅፀኔ ሥጋ ነገር ተቆርጦ ወጣ፡፡ በዚህ ጊዜ ቤተሰቦቼ «እጢው ወጣልሽ» በማለት ተአምር አሉ፡፡ ሥጋ መሰል ባዕድ አካል ከወጣልኝ በኋላ ምንም ዓይነት ስሜት ሳይሰማኝ ጤነኛ ሆንኩ፤ ጠበሉንም አቋረጥኩት» በማለት ገልጻለች፡፡

በዚህ መልኩ ለውጥ ያገኘችበትን ጠበል ስታቋርጥ ዳግም ሕመሙ ጀመራት፡፡ መንበረ ማርያም ትናገራ ለች፡፡ «ጠበሉን ለአንድ ዓመት እንዳቋረጥኩ በሽታው በባሰና በሚያስፈራ መልኩ ተመልሶ መጣ፡፡ እንደገና ጠበሉን መጠጣት ጀመርኩ፤ በዚህን ጊዜም ደጋግሞ የሆነ ነገር በሕልሜ ያሳየኛል፤ በሆነ መንገድ ላይ በጣም ጥቁርና ትልቅ ሰውዬ ዝም ብሎ ቆሞ ዐያለሁ፣ ቀጥሎ እኔ ሕፃን ልጅ ታቅፌ ሳመልጥ እሱ ትልቅ ድንጋይ ይዞ እየተከተለ በማስፈራራት ሲያሯሩጠኝ ዐያለሁ፡፡ ይህን ያየሁት በድሮው ቤታችን መገናኛ አካባቢ ነው፡፡

የመንበረ ማርያም ዋናው ታሪክ የሚጀምርው በግንቦት ወር 2001 ዓ.ም ነው፡፡ በዕለተ ሰንበት እሑድ ቀን ቅዳሴ አስቀድሳ ስትመለስ እንደተለመደው የወር አበባ ይታያትና በቃላት ሊገለጽ በማይችል ሁኔታ በጽኑ ትታመማለች፡፡ መንበረ ማርያም እንደገለጸችው «መጽሐፈ አርጋኖን ይዛ ከአንዱ ክፍል ወደ አንዱ ክፍል እየተንቆራጠጠች 'ወይኔ! እመቤቴ ኧረ አድኚኝ' እያለች መኝታ ክፍሏ ሆና ስታጣጥር በድንገት በግድግዳ ላይ የተሰቀለውን የቅዱስ ሚካኤል ሥዕል ታያለች፡፡ እያጣጣርኩ በክፍሌ ውስጥ ቁጭ ብዬ ድንገት የተሰቀለውን የቅዱስ ሚካኤል ሥዕል ቀና ብዬ ማየት ስጀምር የፌዝ ሳቅ መሳቅ ጀመርኩ፡፡ በዚህን ጊዜ ራሴን እየለወጠኝ ነው፤ አልፎ አልፎ እንጂ ምን እንደምሠራም አላውቅም፤ መጣሁልህ ይላል፡፡ እንደዛር ማጓራት ጀመርኩ፤ አባቴ ሲሰማ ደነገጠ፡፡ እሱ እንደነገረኝ ሁለት እጄን ይዞ የቅዱስ ገብርኤል ጠበል እየረጨ 'አንተ ማነህ?' ሲለው 'እባክህ አንተ አታውቀኝም! ዝም ብለህ ነው፤ ተቃጠልኩ ጊዜዬ ሲደርስ የምለቅበት ቀን አለ፡፡ እሷን የያዝኩት ከማኅፀን ጀምሮ ያሳደግኳት እኔ ነኝ' በማለት ለፈለፈ፡፡ በመቀጠል 'እናቷንም የገደልኩ እኔነኝ' ሲል ራሱን ገለጠ» በማለት መንበረ ማርያም አስረድታለች፡፡ እናቷ በካንሰር ሕመም ምክንያት በ1995 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸውንም ገልጣልናለች፡፡

በቅዱስ ሚካኤል ሥዕል ሳቢያ ማንነቱን የገለጠው ሰይጣን እንደያዛት ስታውቅ፣ የትመጠመቅ እንዳ ለባት ታስባለች፡፡ በመጨረሻም በደብረ ወልደ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ሔዳ ጠበል መጠመቅና መጠጣት ትጀምራለች፡፡ በአምስተኛው ቀን ያደረባት ርኩስ መንፈስ መለፍለፍ ይጀምራል፡፡ በተለይ ሰኔ 10 ቀን 2001 ዓ.ም በዕለተ ረቡዕ ስትጠመቅ 681 አጋንንት እንደ ሠፈረባት ይለፈልፋል፡፡ ብዙ ሰው እንደጨረሰና አሁንም ብዙዎችን እንደያዘ ገልጾ እርሷ ላይ ሲደርስ ግን እንደተጋለጠ ተናግሯል፡፡ «ምእመናን እንደነገሩኝ ከሆነ «አንቺ ስትጮኺ እንደ አንበሳ ነው፤ የሚያስፈራና ከአንቺ የሚወጣ ድምፅ አይመስልም ብለውኛል፡፡ እኔ ግን በመሐሉ «መድኃኔዓለም መጣ» የሚል ድምፅ ሰማሁ እንጂ ራሴን አላውቅም፡፡ 

መጨረሻ ላይ ራሴን ሳውቅ ከእኔ የወጣውን ጥቁር ወፍ ይዘው አሳዩኝ፡፡ አላመንኩም፡፡ ሰው እልል እያለ 'አይዞሽ ተነሽ እመቤታችን ከነልጇ የሠራችልሽ ተአምር በጣም ድንቅ ነው፡፡ ተነሥተሽ ድንቅ ተአምሯን ትመሰክሪያለሽ' አሉ፡፡ ልብሴን ለብሼ ስወጣ ብዙ ምእመናን ቆሞ በሞባይልና በቪዲዮ የወጣውን ጥቁር ወፍ ይቀርጻል፡፡ ከሆዴ የወጣው ትልቅ አፍ ያለው ወፍ ደም ጎርሶ በሕይወት ለተወሰነ ደቂቃ ልቡ ይመታል፡፡ እኔ ራሴን አላመንኩም፤ ደስታ አይሉት ሐዘን ተደበላለቀብኝ፣ ሰውነቴ ከላይ እስከታች ይርዳል» ስትል የእግዚአብሔርን ድንቅ ተአምር መስክራለች፡፡

ሰኔ 10 ቀን ከ681 አጋንንት ውስጥ ሰማንያው ጥቁር ወፍ ሆኖ ሲወጣ ሰኔ 12 ቀን ሌሎች ቀሪዎቹ በጉንዳን መልክ ወጥተናል ብለው በመለፍለፍ ለቀቁ፡፡ በወቅቱም የጠበሉ ቦታ በጉንዳን ተወሮ እንደነበር መንበረ ማርያም ገልጻለች፡፡ ያ በሕልሟ ሲያባርራት ያየችው ጥቁር ሰው እርኩስ መንፈስ እንደሆነና ሕፃኑ ደግሞ መድኃኔዓለም ሆኖ እንዳዳናት አምና ተርጉማዋለች፡፡
መንበረ ማርያም ስለተደረገላት ድንቅ ተአምር ሰኔ 10 እና 21 ቀን 2001 ዓ.ም የእመቤታችን ክብረ በዓል ዕለት በቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ቤተክርስቲያን በመድረክ ላይ ወጥታ ለሕዝበ ክርስቲያኑ መስክራለች፡፡

በመጨረሻ ያነሣንላት ጥያቄ «የተደረገልሽን ተአምር እንዴት ትገልጭዋለሽ?» ነበር፡፡ እሷም «እግዚአብሔር ያደረገልኝን ድንቅ ተአምር በቃላት ልገልጸው አልችልም፡፡ ኃያሉ እግዚአብሔር እኔን አድኖኛል ምስጋና ይድረሰው፡፡ እኔ ግን የማተኩረው ስለተደረገልኝ ተአምር መመስከር ብቻ ሳይሆን ስለማስተላለፈው ነገር ነው፡፡ ይኽም እግዚአብሔር እንዲህ ማዳን እየቻለ ሰይጣን ሊሰለጥንብን አይገባም፡፡ በሥራ፣ በትምህርት ቤትና በዕለት ተዕለት ሥራችን ላይ ውጤታማ እንዳንሆን መሰናከል እየሆነ ነው፡፡ ሕይወታችንን እያበላሸ መሆኑን አልተረዳንም፡፡ ስለዚህ ስመ ክርስትና ብቻ ይዘን መቀመጥ ሳይሆን በጾም በጸሎት እግዚአብሔርን ማገልገል ይኖርብናል፡፡ ከንስሓ አባት ጀምሮ የሃይማኖት አባቶችም ማስተማር አለባቸው፡፡ እያንዳንዱ ሰው ራሱን ይመርምር፤ ክፉ መንፈስን መዋጋት አለበት» ብላለች፡፡

«ማየት ማመን ነው» እንደተባለው በወቅቱ በደብረ ወልደ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስና በመካነ ጎለጎታ ቅድስት ማርያም የጠበል ቦታ ሲያጠምቋት የነበሩትና ድርጊቱን የተመለከቱት ሊቀ ትጉኃን ስሙር አሐዱ ስለሁኔታው እንዲነግሩን ጠይቀናቸው እሳቸውም ታሪኩን እንዲህ አወጉን፡፡ «ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለም፤ ነገሩ ተአምር ነው፡፡ ከዚህ በፊት በእርኩስ መንፈስ የታሰሩ፣ የተተበተቡ ሰዎችን በእግዚአብሔር ኃያልነትና መስቀል በመታገዝ በላያቸው ያለውን አጋንንት አስለቅቄያለሁ፡፡ ይህ ግን ልዩና በሕይወቴም ገጥሞኝ የማያውቅ ነው፡፡ በዕለቱ እኅታችን መንበረ ማርያም ወደምትጠመቅበት ክፍል ስትገባ ጀምሮ በጣም ትጮሃለች፡፡ በመስቀል እያጠመቅሁ ምንድን ነህ? ስለው አጋንንት ነን አሉ፡፡ ቀጥሎ ስንትናችሁ? አልኩት 600 አጋንንት ነን አሉና እውነቱን አውጣ ብዬ አጥብቄ ስይዘው 680 ብሎ ለፈለፈ፡፡ መጨረሻ ላይ 681ኛ ተልከስካሽ የዛር መንፈስ እንዳለ ገልጾ ከሰኔ 10 ቀን 2001 ዓ.ም ጀምሮ በተከታታይ በአራት ቀናት ውስጥ ተከፋፍሎ ወጣ» ብለዋል፡፡

እንደ እሳቸው አባባል ሰኔ 10 ቀን 2001 ዓ.ም 80ው ጥቁር ወፍ ሆኖ ሲወጣ፤ በነጋታው «593ቱ ጉን ዳን ሆኜ እወጣለሁ» ብሎ ጮኸ፤ ሲለቅ ወዲያውኑ ከየት መጣ ሳይባል አካባቢውን ጉንዳን ወረረው፡፡ በሦስተኛው ቀን ደግሞ ሰባት ሲወጣ ከሰባቱ አንዷ ብቻ ሴት ሆና ተገኘች፡፡ እሷም «ከውጭ ሀገር ነው የመጣነው፤ ሥራችን ተመሳሳይ ፆታዎችን ማጋባት ሲሆን በውጭው ዓለም አጥለቅልቀነው ወደ አፍሪካና ኢትዮጵያ በብዛት እየገባን ነው» ብላ ተናግራለች፡፡

«በመጀመሪያ ዋናውና አለቃው ' አጋንንት ጥቁር ወፍ ሆኖ ሲወጣ 600ው ሠራዊት ነኝ ብሎ ወጣ፡፡ አለ ቃውን አጋንንት» እንዴት ብለህ ነው የምትወጣው» ስለው እንደ አንበሳ አጓርቼ እወጣለሁ አለ፡፡ ልጅቷ እንደ አንበሳ እያጓራች ሳለ ጥቁር ወፍ በደም ተለውሶ ከሆዷ ውስጥ በአፏ ወጣ፤ ሲወጣም ልክ እንደ አየር ሞገድ ተወርውሮ ገንዳ ነገር ላይ አረፈ፡፡ ይህ እርኩስ መንፈስ ወፍ ሆኖ ሲወጣም ግፊት ስለነበረው እኔን ሁሉ ገፍትሮኛል፡፡ የወጣው ጥቁር ወፍ ከነሕይወቱ በመሆኑ ለተወሰነ ደቂቃ የማስካካት ድምፅ አሰምቷል፡፡ ለግማሽ ሰዓት ያህልም በሕይወት ቆይቶ ምእመናን ዐይተውታል፡፡ ድርጊቱ የሁሉንም መንገደኛ ቀልብ የሳበ ስለነበር መናፍቆች ሳይቀሩ ተመልክተው በእመቤታችን ድንቅ ተአምር ተገርመ ዋል፡፡ በተለይ አንድ ከነቀምት የመጣ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ በተአምሩ ተደንቆ ሲያለቅስ ዐይቻለሁ» በማለት ሊቀ ትጉኃን ስሙር አስረድተዋል፡፡

«አጋንንቱ መንበረ ማርያምን እንዴት እንደያዛት ስጠይቀው በተለያየ ምክንያት በይበልጥ በዛር ውላጅ ሲወርድ ሲዋረድ በዘር ሐረግ የመጣ እንደሆነ ለፍልፏል፡፡ ለ20 ዓመታት ያህል በሆዷና በማሕፀኗ ላይ ከፍተኛ ጫና በማድረስ ያሰቃያት እንደነበር ዘርዝሯል፡፡ በወር አበባዋ ጊዜ ምጥ እያበዛ ያሰቃያት እንደነበር ተናግሯል፡፡ እመቤቴ፣ እመቤቴ እያለች የእመቤታችን ማርያምን ስም እየጠራች አስቸገረችኝ እንጂ ሆዷን ኦፕራሲዮን አስደርጌ በሰበብ ልገድላት ነበር» ሲልም ተናግሯል ይላሉ፡፡

«ድርጊቱ በጣም የሚከብድ እና በእኔ ላይ የደረሰ ያህል ተሰማኝ፤ እኔም በሁኔታው በጣም ያዘንኩበትና ያለቀስኩበት ነው፡፡ ምክንያቱም ይህ ድርጊት በእኔ ላይ ተከስቶ ቢሆን ኖሮ ምን ልሆን እንደምችል ትንሽ ቆም ብዬ ማሰብ ጀመርኩ፡፡ እሷ ግን እጅግ በጣም ጠንካራ፣ በእምነቷ ጽኑ ነች፡፡ በእምነቷ ጽናት እግዚአብሔር ድንቅ ሥራውን ሠራላት፡፡ አሁን ሙሉ ለሙሉ ጤነኛ ነች ብለዋል፡፡ እርኩስ መንፈሱ አባቷን ሳይቀር ሌሎች ሰዎችንም ይዣለሁ ብሎ በመለፍለፍ ልጅቷ ቤት ድረስ በመሔድ መጥተው እንዲጠመቁ ተናግሬያለሁ» በማለት ሊቀ ትጉኃን ተናግረዋል፡፡

በመጨረሻም «የማስተላልፈው መልእክት አለ፡፡ እግዚአብሔር ብዙ ሥራ ይሠራል፤ እግዚአብሔር እኛ እንድንድን የማያደርግልን ነገር የለም፡፡ ከዚች እኅት ትልቅ ትምህርት አግኝተንበታል፤ የክርስቶስ ስልጣን ይህን ዐይነት የሚሠራ ከሆነ እኛ የት ነን? ብለን ማሰብ አለብን፡፡ ትንሽም ብትሆን እምነት ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ወደ እግዚአብሔር በመቅረብ ጠበሉን፣ እምነቱን ልንጠጣ ይገባል፤ ሥጋና ደሙን ልንቀበል ያስፈልጋል፡፡ ይህ ከሆነ መዳን እንዳለ ማመን ይገባል» ሲሉ ሊቀ ትጉኃን ስሙር አሐዱ አስረድተዋል፡፡
በርግጥም መንበረ ማርያምና አጥማቂዋ ሊቀ ትጉኃን እንደገለጡት በየጠበሉ ቦታ ሲታይ በርኩስ መንፈስ በመተት፣ በዛር፣ በአጋንንትና በመሳሰሉት የተያዙ ሰዎች በእግዚአብሔር ኃይል ሲፈወሱ ማየት ጉድ ያሰኛል፡፡ ሰይጣን የምንፈራው ሳይሆን ታግለን የምናሸንፈው መሆኑን ማንም ሰው ሊያውቀውና ሊረዳው ይገባል፡፡ አውቆም በጾም በጸሎት እርምጃ ሊወሰድ ይገባል፡፡ የበለጠ ደግሞ መምህራን ሓላፊነት ወስደው ማስተማር ይኖርባቸዋል፡፡

ከእጇ ዘይት የሚፈልቅ የቅድስት ኤልሳቤጥ አስገራሚ ታሪክ

 


Tuesday, December 22, 2015

ድንቅ ተአምር - ሰሜን አሜሪካ ሚኒሶታ


ትላንት እሁድ ታህሳስ 10/2008 ዓ.ም በጾመ ነቢያትን ግዜ በደብረ ሰላም መድኃኔዓለም የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የተነገረ ተዓምር ላካፍላችሁ።

ቦታው ሰሜን አሜሪካ ሚኒያፖሊስ ሚኒሶታ ውስጥ ነው። እህታችን ዘጠኝ ወር በማሕጸኗ የተሸከመችውን ጽንስ በሰላም ተገላግላ እንደ እናት ወግ ልጇን አቅፋ ስማ ተንከባክባ ለማሳደግ ጊዜዋ ደርሶ ነበርና መያዝ የሚገባትን ነገር ሁሉ አዘጋጅታ ጨርሳ ወደ ሆስፒታል ታመራለች። በዚህ በጭንቅ ሰዓት ታድያ ካዘጋጀችው እቃዎቿ አንዱ የእናታችን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ስዕለ አድኅኖ ነበር። እህታችን ከመግባቷ በፊትም " እመቤቴ በሰላም ተገላግዬ ከቤተሰቦቼ በደስታ እንድገናኝ በሰላምም ወደቤቴ እንድገባ ከልጅሽ ከመድኅኔዓለም አማልጂኝ ጭንቁን አቅልይልኝ" ብላ ጸሎት አደረገች። ከጥቂት ጊዜም በኋላ ሴት ልጅን በሰላም ተገላገለች ሁሉም ነገር ደስታ ሆነ። ነገር ግን ይሄ ደስታ ምንም ያህል ሊቆይ አልቻለም ነበር። ባለቤቷ መታጠቢያ ክፍል ደርሶ እስኪመለስ ድረስ ነገሩ ሁሉ የተገላቢጦሽ ሆነ ያ ሁሉ ደስታ በደቂቃዎች ወደሃዘን ተለወጠ። እህታችን የወለደቻትን ልጅ እያጠባች ባለችበት ሰዓት በድንገት ራሷን ትስታለች። ወዲያው ሃኪሞች ተጠሩ ከፍተኛ እርዳታ ተደረገላት ነገር ግን መንቃት አለቻለችም። በዚህም ምክንያት በከተማዋ አሉ የተባሉ ስፔሻሊስት ዶክተሮች እና ሊሎችም ከፍተኛ የሕክምና ባለሞያዎች ቢሯሯጡም መልሱ ከነሱ አልነበረምና ምንም ሊረዷት አልቻሉም። በዚህ ጊዜ መላው ቤተሰብ በሃዘን ተዋጠ። 

በከተማው ካሉት አቢያተ ክርስቲያናት አንዱ ወደሆነው ታላቁ ደብር ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን በመምጣት ዘወትር በማሕሌት በኪዳን እንዲሁም በቅዳሴ ሰዓት በካሕናት አባቶች ጸሎት እንዲያዝላት ሽና ስሟ እየተጠራ እንዲጸለይላት
ይጠይቃሉ።ካሕናቱም በፍጹም ታዛዥነት ጽሎቱን ይጀምራሉ። እህታችን በዚሁ ሁኔታ ላይ እንዳለች ሳምንታት አለፉ። ካሕናቱም ጽሎቱን ቀጠሉ ነገር ግን አንድ ያልተጠበቀና አስደንጋጭ ነገር ተፈጠረ።የተፈጠረው ነገር ያልተጠበቀና እጅግ ተስፋ አስቆራጭ ነበር ሙሉ የሰውነት ክፍሏ ስራ አቆመ።የልብ ምቷም ቆመ። ሃኪሞቹ ተጠርተው ቢመጡም ከዚህ በላይ ምንም ማድረግ አይችሉም ነበር። ይሄን ጊዜ በሰው እጅ ያለው ተስፋ ሲሟጠጥ ሸክም ሲከብድ ቢዘገይ እንኳን የሚቀድመው የሌለው አምላክ ስራውን የጀመረው። እህታችን በእናቱ ፊት ለምልጃ ያቀረበችው ጸሎት ከዶክተሮቹ እጅ ተቀብሎ ስራውን መስራት ጀመረ። የተገጣጠሙላት መሳርያዎች ሳይነቀሉ ለስድስት ደቂቃዎች ቆሞ የነበረው የልብ ምቷ በድንግል አማላጅነት በመድኃኔዓለም ሐኪምነት ስራውን ጀመረ። ሃኪሞቹ በጣም ደነገጡ ምንም ያደረጉት ነገር ሳይኖር ለስድስት ደቂቃዎች ስራ አቁሞ የነበረው ልብ አሁን ደግሞ መስራት ጀመረ። ይሄ ከሰው ልጅ አእምሮ በላይ ነው። እስከዛሬም ሆኖ የማያውቅ ይሆናል ተብሎም የማይጠበቅ በጣም አስገራሚ ነገር ነው የተደረገው የሚል ብቻ ነበር የነሱ መልስ። ከዚህም በኋላ እህታችን ሙሉ በሙሉ ከበሽታዋ ድና እንደጓጓችለት በእመቤታችንን ምልጃ በመድኃኔዓለምን ምህረት ለዚህች ቀን ደርሳ ልጇን ታቅፋ አምጥታ ክርስትና ለማስነሳት በቃች ልጅቷም ወለተ ኪዳን ተብላ ተሰይማለች። ይህንን በሰው ሃሳብ ሲመዘን እጅግ ከባድና ከአስተሳሰባችን በላይ የሆነን ነገር ሌላ ሰው ቢናገረው እንዴት ይታመናል? በሳይንስ እይታ የልብ ምት አይደለም ለስድስት ደቂቃ ቀርቶ ለጥቂት የደቂቃዎች ሽርፍራፊ እንኳን ስራ ቢያቆም ያ ሰው ሞቷል ማለት ነበር። በሰው የተዘጋውን በር ሳይሆን በእግዚአብሔር እጅ ያለውን ቁልፍ ተመልከት እንዳሉ አቡነ ሺኖዳ ሳልሳዊ እሱ ታሪክን ቀያሪ ነውና የአራት ቀን እሬሳን ያስነሳ አምላክ ሃዘኑን በደስታ ለወጠ። የካሕናቱና የቤተሰቡ ያልተቋረጠ ጸሎት መንበረ ጸባዖት ደረሰ። አዎ በትክክልም ተደርጓል እህታችንም በአውደ ምህራት ቆማ በጸሎት ሲያስቧት የሰነበቱትን ካሕናት እና ምዕመናን አመስግና የጭንቅ ጊዜ ደራሿን ድንግልን ከምንም በላይ ደግሞ እርሱ ሐኪም እርሱ ስፔሻሊስት ሆኖ ለዚህ ያበቃትን ጌታ መድኃኔዓለምን በአንደበቷ አመሰገነች።
"ወመኑ መሐሪ ዘከማከ"
"አቤቱ እንዳንተ ያለ መሐሪ ማነው?" አይደል ያለው ሊቁ!
እህታችንን ያማለደች እመቤታችን ምልጃዋ ጸጋ ረድኤት በረከቷ አይለየን። መሐሪው አምላካችን የያንዳንዳችንን የልቡና መሻት ይፈጽምልን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!