Tuesday, November 10, 2015

የ ኪዳነ ምሕረት ተአምር

የሚገርም የእመቤታችን ማርያም ተአምር ታሪክ ፦በራያ አልማጣ በጥሙጋ ከተማ ኪዳነ ምሕረት በተባለች ቤተክርስቲያን ለበተክርስቲያኑ ግንባታ የሚሆን ድንጋይ በመኪና ተጭኖ ከመጡት ብዙ ድንጋይ መካከል አንደኛው ድንጋይ ሲጠረብ አልጠረብም ይላል አሁንም ግንበኞቹ በተደጋጋሚ ሞከሩ ሊጠረብ አልቻለም ከዛ ሳይጠረብ ለግንባታ ሊጠቀሙበት ወደ ላይ ለመስቀል አንደኛው ግንበኛ በሁለት እጁ ተሸክሞ ወደ ላይ በሚወጣበት ጊዜ የተሸክመው ሰው እዛው ባለበት ቦታ ልክ እንደ ኤሌክትሪክ ይነዝረዋል ከዛም ከላይ ወደታች ሲወድቅበት ያ ተአምረኛ ድንጋይ ከ ሁለት ይከፈላል በጣም በሚገርም ሁኔታ ከአንደኛው ድንጋይ የምትመለከቱት የእመቤታችን ሥዕል ታየ በጣም የሚገርመው ለ 3 ዓመት መራመድ ያቃታት ሴት የድንጋዩ ፍንጣሪ እግሯን ሲመታትፈውስ አገኘች ማየት ማመን ነው ጥሙጋ እየመጣቹህ መመልከት ትችላላቹህ የእመቤታችን አማላጅነት አይለየን አሜን

Saturday, October 17, 2015

አንዳሳ ቅዱስ ጊዬርጊስ ፀበል

በደብረ መንክራት አንዳሳ ቅዱስ ጊዬርጊስ ለበርካታ አመታት ስትሰቃይ የነበረች እህታችን የቅዱስ ጊዬርጊስን ፀበል በመጠጣት እና በመጠመቅ ከሆዷ ውስጥ ሶስት መርፌ እና አንድ ምላጭ ወጦላታል። ይሂን ታምር በአይኔ በማየቴ እግዚአብሄርን አመሰግናለሁ። ፀበሉ በርካታ ታምራትን እያደረገ ሲሆን በተለያዩ ደዌዎች፣በርኩሳን መናፍስት የተጠቁ ወዘተ እየተፈወሱ ይገኛሉ። ክብር ለቅዱስ
ጊዬርጊስ አምላክ ለእየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ጋር ይሁን

Thursday, October 1, 2015

ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ

ግንቦት 14- ሙሽራው ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ ከጫጉላ ቤቱ ወጥቶ የመነነበት ዕለት ስለሆነ በሀዘን የሚያስለቅሰውን ቅዱስ ገድሉን እንመለከታለን፡፡ በተጨማሪም ዛሬ የታላቁ አባት የአባ ጳኩሚስ በዓለ ዕረፍት ነው፣ ድንጋዩን እንደ ጀልባ ተጠቅመው ጣናን የተሻገሩት የአቡነ ያሳይ ዘመንደባም ዕረፍታቸው ነው፡፡
መልካም የበረከት ንባብ!!!
ሙሽራው ገብረ ክርስቶስ፡- ሙሽራው ገብረ ክርስቶስ ወላጅ አባቱ የቍስጥንጥንያው ንጉሥ ቴዎዶስዮስና እናቱ ንግሥት መርኬዛ በስለት ያገኙት ብቸኛ ልጃቸው ስለሆነ ሃይማኖትን እያስተማሩት በምግባር በእጅጉ ተንከባክበው አሳድገውታል፡፡
የአባቱን ንግሥና በመውረስ ቍስጥንጥንያን እንዲገዛላቸው በመፈለግ ወላጆቹ ለአካለ መጠን ሲደርስ የሮሙን ንጉሥ ሴት ልጅ አጋቡት፡፡ እርሱ ግን ዓለምን ፍጹም በመናቅ የክርስቶስን መስቀል ለመሸከም የተዘጋጀ ነበርና የሠርጉ ዕለት ሌሊት የእርሱንም ሆነ የሙሽይቱን ድንግልና እንደጠበቀ ከጫጉላ ቤት ወጥቶ በመርከብ ተሳፍሮ ሩቅ ሀገር በመሄድ በቤተክርስቲያን ተቀምጦ ከነዳያን ጋር ተደባልቆ በመለመን ለምኖ ያገኘውንም ለሌሎች እየመጸወተ በጾም በጸሎት ተጠምዶ 15 ዓመት ኖረ፡፡
እመቤታችን ተገልጻ ለአንድ የቤተክርስቲያኑ አገልጋይ የገብረ ክርስቶስን ጽድቅ ብትነግረው ምሥጢሩን ለሀገሩ ሁሉ አዳረሰበት፡፡ ሙሽራው ገብረ ክርስቶስም ‹‹ግብሬ ታወቀ፣ ከዚህ ውዳሴ ከንቱ ልሽሽ›› በማለት ወደሌላ ሀገር በመርከብ ሲጓዝ ፈቃደ እግዚአብሔር መርከቢቱን ያለ አቅጣጫዋ ወስዶ አባቱ ደጅ አደረሰው፡፡ ማንነቱን እንደደበቀና ዓለምን ምን ያህል እንደናቃት ይረዳ ዘንድ በአባቱና በንጉሡ ደጅ የኔ ቢጤ ለማኝ ሆኖ ለአባቱ ውሾች የሚሰጠውን ፍርፋሪ እየተመገበ አሁንም 15 ዓመት ሙሉ በትዕግስት ተቀመጠ፡፡
የአባቱ አሽከሮች እንኳን እጣቢና ቆሻሻውን ሁሉ እየደፉበት ሲያሠቃዩት የአባቱ ውሾች ግን የእግሩን ቁስል ይልሱለት ነበር፡፡ በአጠቃላይ ገብረ ክርስቶስ እጅግ የተከበረ የታላቅ ንጉሥ ልጅ ሲሆን ነገር ግን ዓለምን ፍጹም በመናቅ ስለ ጽድቅ ተሰዶ እየለመነ ያገኘውን እየመጸወተ በጾም በጸሎት እየተጋደለ 30 ዓመት ሙሉ ተቀመጠ፡፡ በመጨረሻም ጌታችን እመቤታችንን፣ ቅዱሳን መላእክትን ሁሉ፣ ከገብረ ክርስቶስ በፊት የነበሩ ነቢያትን ሁሉ፣ ሐዋርያትን፣ ጻድቃንን፣ ሰማዕታትን ሁሉ አስከትሎ መጥቶ ቃልኪዳን ከገባለት በኋላ ከጌታችን ጋር አብረውት የመጡት ሁሉ በታላቅ ክብርና ምስጋና እያመሰገኑት ጌታችን ክብርት ነፍሱን በእቅፉ ተቀብሎ አሳርጓታል፡፡
የቁስጥንጥንያው ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስ በቅዳሴ ላይ ሳሉ ከንጉሡ ቤት ሄደው የገብረ ክርስቶስን ሥጋ እንዲያመጡ የእግዚአብሔር ድምፅ ከሰማይ በትእዛዝ መጣላቸውና ሄደው ቢያዩ የገብረ ክርስቶስን ሥጋ በንጉሥ አባቱ ደጅ ወድቆ አገኙት፡፡ በገብረ ክርስቶስም እጅ ላይ በጥቅል ወረቀት የተጻፈ ደብዳቤ ነበርና ወስደው ሊያነቡት ሲሞክሩ ወረቀቱ አልላቀቅ ብሎ ፈጽሞ እምቢ አላቸው፡፡ ብዙ ምሕላና ጸሎት ከተደረገ በኋላ ወረቀቱ ከእጁ ላይ ተላቀቀና ሲነበብ ገብረ ክርስቶስ ስለ አምላኩ ፍቅር ብሎ ለ30 ዓመታት ያሳለፈውን እጅግ አሠቃቂ መከራ በተለይም በአባቱ ደጅ ማንም ሳያውቀው ያሳለፈውን እጅግ አሳዛኝ መከራና በኀዘን የሚያስለቅሰውን ታሪኩን በራሱ እጅ በዝርዝር ጽፎት ተገኝቷል፡፡ ንጉሡ አባቱና ንግሥት እናቱም ይህንን ልጃቸው የጻፈውን መልእክት ባነበቡ ጊዜ የሚሆኑት ጠፋቸው፡፡
በጣም የሚገርመው ደግሞ ወላጆቹ ሚስት አድርገው ያመጡለት የሮሙ ንጉሥ ሴት ልጅ ለባሏ ታማኝ ሆና 30 ዓመት ሙሉ በእናት አባቱ ቤት በትዕግስት ስትጠብቀው መኖሯ ነው፡፡ እርሷም ታሪኩ ሲነበብ ብትሰማ እንደ ዕብድ ሆነች፡፡ የቅዱስ ገብረ ክርስቶስን ሥጋውን ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲወስዱ እጅግ አስገራሚ ተአምራት በድውያን ሕመምተኞች ላይ ተፈጽሟል፡፡ ከተአምራቱ የተነሣ መንገዱ በሕዝብ ተጨናንቆ አላሳልፍ ቢላቸው ንጉሡ በመንገድ ዳር ወርቅ እየበተነ ሰው ወርቁን ለማንሳት ሲሄድ በፍጥነት ወደ ቤተ ክርስቲያን አድርሰውታል፡፡ ዕረፍቱም ጥቅምት 14 ቀን ሲሆን ዛሬ ከጫጉላ ቤቱ መንኖ የወጣበት ዕለት ነው፡፡
አቡነ ያሳይ ዘማንዳባ፡- የደብረ በንኰል ገዳም አበምኔት አቡነ መድኃኒነ እግዚእም በአንድ ቀን ለሰባት አባቶች የምንኵስናን ልብስ አልብሰዋቸል፤ አስኬማ ዘመላእክትን አስታጥቀዋል፡፡ እነዚህም ሰባት ታላላቅ አባቶች "ሰባቱ ከዋክብት" በመባል የሚታወቁት ናቸው፡፡ እነዚህም አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ፣ አቡነ ሳሙኤል ዘቆየፃ፣ አቡነ ሳሙኤል ዘጣሬጣ፣ አቡነ ያሳይ ዘማንዳባ፣ አቡነ ዮሐንስ ዘጉራንቋ፣ አቡነ ታዴዎስ ዘባልተዋር እና አቡነ ያፍቅረነ እግዚእ ዘጉጉቤን ናቸው፡፡ እነዚህም 7ቱ ከዋክብት ከተሰዓቱ (ከዘጠኙ) ቅዱሳን በኀላ መላዋን ኢትዮጵያ በወንጌል ያዳረሱ ታላላቅ ቅዱሳን ናቸው፡፡ አቡነ ያሳይ ዘማንዳባም አንዱ ናቸው፡፡
ጻድቁ ድንጋዩን እንደ ጀልባ ይጠቀሙበት ነበር፡፡ የማንዳባው አቡነ ያሳይ የመድኃኔዓለምን ታቦት ይዘው ወደ ደሴቲቱ የገቡት ትልቁን ድንጋይ እንደ ጀልባ ተጠቅመው በድንጋዩ ላይ ተቀምጠው የጣናን ሐይቅ እየቀዘፉ ነበር፡፡ ትልቁ ጠፍጣፋ ድንገይ ዛሬም ድረስ በገዳማቸው ውስጥ በክብር ተቀምጦ ይገኛል፡፡
ጻድቁ በይበልጥ የሚታወቁት በ"አትማረኝ ዋሻ" ታሪክ ነው፡፡ በገድላቸው ተጽፎ እንደሚገኘው ዋሻው በጣና ሐይቅ ደሴቶች መካከል ከሚገኙ ገዳማት መካከል ከማን እንደ አቡነ ያሳይ መድኀኔዓለም አንድነት ገዳም በስተ ምእራብ አቅጣጫ የጣና ሐይቅን ጉዞ ከገታው አንድ ተራራ ሥር የሚገኝ ነው፡፡
ጻድቁ ከእግዚአብሔር በተሰጣቸውም ጸጋ በጣና ሐይቅ ላይ እንደ ጀልባ በሚጓዙበት አንድ ጠፍጣፋ ድንጋይ ተቀምጠው በጣና ደሴት ላይ ለአገልግሎት በመፋጠን ላይ እያሉ ዛሬ አትማረኝ ዋሻ ተብሎ ወደሚጠራው አካባቢ ሲደርሱ አንድ አባት ዋሻው ውስጥ “አትማረኝ፣ አትማረኝ፣ አትማረኝ” እያሉ ሲጸልዩ ያገኟቸዋል፡፡ አቡነ ያሳይ በሰውዬው ጸሎት በመገረም ቀርበዋቸው “አባቴ ምን ዓይነት ጸሎት ነው የሚጸልዩት? ይበሉ ከዛሬ ጀምረው “ማረኝ” እያሉ ይጸልዩ" በማለት አቡነ ዘበሰማያትን አሰተምረዋቸው ይሄዳሉ፡፡ አትማረኝ እያሉ ይጸልዩ የነበሩት አባትም “ማረኝ” እያሉ መጸለያቸውን ቢቀጥሉም ብዙ መግፋት ሳይችሉ ጸሎቱ ይጠፋባቸዋል፡፡ ጸሎቱን ያስጠኗቸው አባት አቡነ ያሳይ በድንጋዩ ላይ ተቀምጠው ጣናን አቋርጠው ርቀው ሳይሄዱባቸው ከኀላ በውኃ ላይ በባዶ እግራቸው እየተራመዱ በመከተል ይደርሱባቸዋል፡፡ “አባታችን ያስጠኑኝ ጸሎት ጠፋብኝ፡፡ እባክዎ እንደገና ያስተምሩኝ” ይሏቸዋል፡፡ አቡነ ያሳይ የእኚህ አባት መብቃት (በባሕር ላይ በባዶ እግራቸው መራመዳቸውን) ተመልከተው “አባቴ እግዚአብሔር የልብ ነውና የሚመለከተው እንዳስለመዱት ይጸልዩ የእርስዎ ይበልጣል” ብለዋቸው ይሔዳሉ፡፡ በዚህም ምክንያት ቦታው አትማረኝ ዋሻ ተብሎ ተጠርቷል፡፡
አቡነ ያሳይ እጅግ አስገራሚ ተአምራትን በማድረግ ወንጌልን በሀገራችን ያስፋፉ ሲሆን ተጋድሎአቸውን ፈጽመው ከጌታችን ታላቅ ቃልኪዳን ተቀብለው በዛሬዋ ዕለት ዐርፈዋል፡፡ በረከታቸው ይደርብን!
ኃያል መነኮስ አባ ጳኩሚስ፡- በሥርዓተ ምንኵስና ታሪክ ሌላውን ታላቅ ሥፍራ የያዘው ደግሞ የአባ እንጦንስ ደቀ መዝሙር የነበረው አባ ጳኩሚስ ነው (23ዐ-346 ዓ.ም)፡፡ አባ ጳኩሚስ ግብፅ ውስጥ ኤስና በምትባል መንደር ከአረማውያን ቤተሰቦች በ29ዐ ዓ.ም ተወለደ፡፡
በቆስጠንጢኖስ ዘመነ መንግሥት ለውትድርናም ተመልምሎ አገልግሎት ሰጥቷል፡፡ በውትድርናው ዘመን የክርስቲያኖችን ቆራጥነት፣ ደግነትና ርኀራኄ በማየቱ ልቡ ስለተነካ ግዳጁን ፈጽሞ ሲመለስ በ313 ዓ.ም የክርስትናን እምነት ጠንቅቆ በመማር አምኖ ተጠመቀ፡፡ የአባ ጳኩሚስ ልቡና የቅዱስ እንጦንስ ደቀ መዝሙር በነበረው በአባ ጴላጦንስ ኑሮ ስለተማረከ ወደ በረሃ ወርዶ የብሕትውናን ኑሮና ሥርዓት ሲማር ከቆየ በኋላ በ32ዐ ዓ.ም በዓባይ ወንዝ አጠገብ ታቤኒስ ከተባለው ቦታ የራሱን ገዳም መሠረተ፡፡
እዚህ ጋር የመነኮሳትን ትውልድ መመልከቱ ተገቢ ይሆናል፡፡ ርዕሰ መነኮሳት የሆኑት አቡነ እንጦንስ በእግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ ምንኩስናን ከሊቀ መልአኩ ከቅዱስ ሚካኤል እጅ ተቀበሉ፡፡ እንጦንስም ታላቁ መቃርስን አመነኮሷቸው፤ ታላቁ መቃርስም ጳኩሚስን አመነኮሷቸው፤ እንዲህ እንዲህ እያለ የአባቶቻችን የምንኩስና ትውልድ እስከ ጻድቁ አባታችን ተክለ ሃይማኖት የደረሰ ሲሆን እሳቸውም ያመነኮሷቸው እጅግ ብዙዎች ናቸው፡፡



ጳኩሚስም ቴዎድሮስን፣ ቴዎድሮስ ደግሞ አቡነ አረጋዊን(ዘሚካኤልን)፣ አረጋዊ ክርስቶስ ቤዛነን፣ ክርስቶስ ቤዛነ መስቀል ሞዐን፣ መስቀል ሞዐ ዮሐኒን፣ ዮሐኒ ኢየሱስ ሞዐንና ተክለ ሃይማኖትን(በቆብና በአስኬማ)፣ ኢየሱስ ሞዐ
ተክለ ሃይማኖትን(በቅናትና በቀሚስ)፣ ተክለ ሃይማኖት ኢየሱስ ሞዐን (በቆብና በአስኬማ) ወልደዋል፡፡
ዻኩሚስ መጀመሪያ ወደ ምንኩስናው ዓለም የመጣው በታላቁ አባ ዸላሞን አማካኝነት ነው፡፡ ለተወሰነ ጊዜም መንፈሳዊ አባቱን እየረዳ ሕይወተ መነኮሳትን አጥንቷል፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወቱና በተጋድሎ እየበረታና እየደረጀ ሲሔድ ከአባ ዸላሞን ተለይቶ ማሕበር መስርቶ ለመኖር አምላኩን ጠይቆ ፈቃድ በማግኘቱ በሕግ የሚመራ የመጀመሪያውን ገዳም መሥርቷል፡፡
ቅዱስ ዻኩሚስ ጸሎቱ አጋንንትን ከአካባቢው አያስቀርባቸውም ነበር፡፡ አካሉ አልቆ በአጥንቶቹ እስኪቆም ድረስ ጾሟል፡፡ ዓርብ ዓርብ የጌታችንን ሕማማት እያሰበ ከእንባ ጋር ይሰግዳል፡፡ እንባውና ላበቱ ከፊቱ እየወረደ አካባቢው ጭቃ ይሆን ነበር፡፡ ጌታችንም መስቀል ተሸክሞ ይታየው ነበር፡፡ አባ ጳኩሚስ ሲሰግድ ወዙ ወርዶ መሬቱን ጭቃ አደረገው፣ ወዲያው ጌታችን ተገለጸለትና ጳኩሚስ "አንተን አገኝ ብዬ እንዲህ እደክማለሁ" አለው ጌታችንም "እኔም እንጂ ላንተ ብዬ እንዲህ ሆኜ ተሰቅያለሁ" ብሎ በዕለተ ዓርብ እንደተሰቀለ ሆኖ ጐኑን እንደተወጋ ደሙ እንደፈሰሰ ሆኖ ታይቶታል፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን በበረሃ ሳለ መልአክ መጥቶ በነሐስ የተጻፈ ሕግ ሰጠው እርሱም በዚሀ የመጀመሪያውን ሥርአተ መነኮሳትን አዘጋጅቷዋል። ከዚህም ባለፈ በርካታ ሥራዎችን ሠርቷል፡፡ ቅዱስ ዻኩሚስ ጫማ ሳይጫማ እሾህን ሳይሰቀቅ ይረግጥም ነበር፡፡
አባታችን ቅዱስ ዻኩሚስ ከርሕራሔው የተነሣ አጋንንት ያደሩባቸውን ሰዎች ሲያገኝ በቀጥታ ከመፈወስ ይልቅ ደዌውን ርኩሳን መናፍስቱንም ወደ እርሱ እንዲገለበጡ ያደርግ ነበር:: ከዚያም በጾም በጸሎትና በስግደት መድረሻ ያሳጣቸዋል፡፡ ያንጊዜ በግዳቸው እየጮሁ ሲወጡ ደጉ አባት "ምነው ትንሽ ቆዩ እንጂ" እያለ ይቀጣጠብባቸዋል፡፡ አንድ ዕለት ቅዱስ ጳኩሚስ አንዲት ሴት ብዙ አጋንንት ሰፍረውባት ስትሰቃይ አየና "አቤቱ ጌታዬ ሆይ ይህን ሁሉ እንዴት ትችለዋለች?" ብሎ በእርሷ ላይ ያለውን የአጋንንት መንጋ ወደ እርሱ እንዲገለበጥ ፈጣሪውን ለመነ፡፡ በዚህ ጊዜ በአንድ ቀፎ ውስጥ ያሉ ንቦች ወደ ሌላ ቀፎ እንደሚገለበጡ እነዚያ አጋንንት በሙሉ ከዚያች ሴትዮ ወጥተው በአባ ጳጉሚስ ላይ ሰፈሩ፡፡ እርሱም ማቅ ለብሶ አመድ ነስንሶ በሥግደት በጾምና በጸሎት አሰቃያቸው፡፡ የዚህን ቅዱስ አባት ትሩፋትና ተጋድሎ ስላልቻሉ አጋንንቱ "እንሂድ እንጂ እንግዲህማ ምን እናደርጋለን" ሲሉ ሰማቸው፡፡ ቅዱስ ጳኩሚስም "ለምን አትቆዩም ሰው እንዲህ ካለ ኃጥእ ወዳጁ ቤት እኮ ጥቂት ጊዜ ያርፋል" ቢላቸው "እኛስ ከገነት ካስወጣነው ከአዳም በቀር እንዲህ ያለ ሰው አላየንም ትሩፋቱ አቃጠለን ሊያስቀምጠን አልቻለም" ብለው መስክረውለት ሄዱ። (ኤፌ.6፥11 "የዲያብሎስን ሽንገላ ትቃወሙ ዘንድ እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ ልበሱ።")
አባ ዻኩሚስ ስለ ክብራቸው መልአክ ነጥቆ ወስዷቸው ገነትንና ሲኦልን አሳይቷቸው መልሷቸዋል።
በዙሪያው ለተሰበሰቡት መነኰሳትም የአንድነት ኑሮ ሕግ አወጣላቸው፡፡ ምንኩስና በእግዚአብሔር ፈቃድ በአባ እንጦንስ ቢመሠረትም ሕይወቱን በማስፋፋት ደረጃ የቅዱስ ዻኩሚስን ያህል የደከመና የተሳካለት ግን የለም፡፡ በአባ እንጦንስ ለተጀመረው የማኀበረ መነኰሳት ኑሮ የተጠናከረ ሥርዓት አውጥቶ የበለጠ ከማስፋፋቱም በተጨማሪ ዘጠኝ የወንድና ሁለት የሴቶች ገዳማት መሥርቷል፡፡ አባ ጳኩሚስ ያወጣው የመነኰሳት የአኗኗር ሕግ ዋናው ቅጂ ሲጠፋ ወደ ላቲን የተተረጐመው ግን እስከዛሬ ድረስ ይገኛል፡፡ ከሕግጋቱ መካከል፡-
፩. መነኮሳት ጠዋትና ማታ በማኀበር እንዲጸልዩ
፪. በኀብረት በአንድነት እንዲሠሩ
፫. ቅዱሳት መጻሕፍትን አዘውትረው እንዲመለከቱ
፬. መነኮሳት ሹመት እንዳይሾሙ ከልክሏል
፭. መነኮሳት የቁም ጽሕፈት እንዲማሩ
፮. ገቢና ወጪአቸው አንድ ላይ እንዲሆን
፯. መነኮሳት በአንድነት እንዲመገቡ
፰. አንድ ዓይነት ልብስ እንዲኖራቸው
፱. መነኮሳት ንጽሕናቸውን ጠብቀው እንዲኖሩ
፲. ከግብፅ ውጪ ምንኩስናን ያስፋፉ አባቶችን አስተምሮ አመንኩሷል፡፡ (ለምሳሌ በኢትዮዽያ ምንኩስናን ያስፋፉት አቡነ አረጋዊ የዚህ አባት ደቀ መዝሙር ናቸው)
፲፩. መነኮሳት ከገዳማቸው በፍጹም እንዳይወጡ ከልክሏል
፲፪የመጀመሪያውን ሥርዓተ መነኮሳት አዘጋጅቷል
፲፫. መነኮሳት ደግነት፣ ፍቅርና ታዛዥነት እንዲኖራቸው...የሚሉት ይገኙበታል፡፡
አንድ ሰው ወደ ገዳማቱ ሲመጣ የሦስት ዓመት አመክሮ ይሰጠውና ጠባዩና ፍላጐቱ ይገመገማል፡፡ ከዚያ በኋላም ብርታቱና ጽናቱ ታይቶ ወደ ማኀበረ መነኰሳቱ ይቀላቀላል፡፡ አባ ጳኩሚስ በዚሁ ዓይነት መንገድ ሥርዓት ሠርተው ሕግ አጽንተው ገዳማትን ካስፋፉና አበምኔት ሁነው 40 ዓመት ካገለገሉ በኋላ ከጌታችን ቃልኪዳን ተቀብለው ለደቀመዛሙርቶቻቸው ቴዎድሮስ ሹመውላቸው በተወለዱ በ56 ዓመታቸው በ346 ዓ.ም በሰላም ዐርፈው ቅድስት ነፍሳቸውን ጌታችን በክብር ተቀብሏታል፡፡
የቅዱሳኑ በረከት በአማላጅነታቸው በምንታመን በሁላችን ላይ ይደርብን አሜን! ይልቁንም እኔን ኀጥኡን ምልጃቸው ሥርየተ ኃጢአትን ያሰጠኝ!!
(ምንጭ፡- ገድለ ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ፣ ገድለ አቡነ ያሳይ-ያለታተመና በገዳሙ የሚገኝ፣ ስንክሳር ዘወርሃ ግንቦት፣ የቅዱሳን ታሪክ፣ መዝገበ ታሪክ)

Tuesday, September 1, 2015

አቡነ ኤዺፋንዮስ

ግንቦት 17- ዕረፍቱ ለአቡነ ኤዺፋንዮስ፡- "ኤዺፋንያ" ማለት የመለኮት መገለጥ ሲሆን "ኤዺፋንዮስ" ማለት ደግሞ ምሥጢረ መለኮት የተገለጠለት ማለት ነው::
ቅዱስ ኤዺፋንዮስ የተወለደው ክርስቶስን ከሚጠሉ አይሁዳውያን ቤተሰቦች ሲሆን ቤተሰቦቹ ከአንድ አህያ በቀር ምንም የሌላቸው ድኆች ነበሩ፡፡ በዚያ ላይ በልጅነቱ አባቱ በመሞቱ ከእናቱና ከአንዲት እህቱ ጋር በረኃብ ሊያልቁ ሆነ፡፡ ሕጻኑ ኤዺፋንዮስ በአህያው እንዳይሠራ አህያው ክፉ ነበርና በእናቱ ምክር ሊሸጠው ገበያ አወጣው፡፡ ሊሸጠውም ከአህያው ጋራ ሲጓዝ ፊላታዎስ ከሚባል ጻዲቅ ክርስቲያን ጋር ተገናኘ፡፡ ፊላታዎስም ሊገዛው ፈልጎ ለግዢ ሲደራደሩ አህያው የኤዺፋንዮስን ኩላሊቱን ረግጦት ለሞት አደረሰው፡፡ በዚህ ጊዜ አብሮት ያለው ጻድቁ ክርስቲያን ፊላታዎስ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ብሎ በትእምርተ መስቀል አማትቦ በቅፅበት አዳነው፡፡ አህያውንም "ስለ እኛ በተሰቀለው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ትሞት ዘንድ ይገባሃል" ብሎ በቃሉ እንዲሞት ቢያዘው አህያው ወዲያው ሞተ፡፡ ኤዺፋንዮስም እነዚህን አስገራሚ ሁለት ተአምራት ካየ በኀላ ጻድቁን ክርስቲያን "በስሙ ተአምራት የምታደርግበት የተሰቀለው ኢየሱስ ክርስቶስ ማነው?" አለው፡፡ ፊላታዎስም ክርስቶስን ሰበከለት፣ ኤዺፋንዮስም እያደነቀ ሔደ፡፡
ከወራት በኀላ ሀብታም አይሁዳዊ አጎቱ ወሰደውና ገንዘቡን ሁሉ አውርሶት ስለሞተ ኤዺፋንዮስ ገና በ16 ዓመቱ ባለጠጋ ሆነ፡፡ የኦሪትን ሕግ ሁሉ እየተማረ ቢያድግም ያቺ ገበያ ላይ ያያት ተአምር ግን በልቡ ውስጥ ትመላለስ ነበር፡፡
በአንዲት ዕለትም ስሙ ሉክያኖስ ከሚባል ጻድቅ መነኩሴ ጋር ተገናኘ፡፡ አብረው ሲሔዱም አንድ ነዳይ አገኙና ምጽዋትን ጠየቃቸው፡፡ ጻድቁ ሉክያኖስም ገንዘብ ስለሌው የሚለብሰውን የጸጉር ዐፅፉን አውልቆ ለድኃው መጸወተው፡፡ በዚያን ጊዜ የብርሃን ልብስ ከሰማይ ሲወርድለት መላእክት ሲያለብሱት ኤዺፋንዮስ ተመለከተ፡፡
ይህንንም ድንቅ ነገር ከተመለከተ በኀላ ኤዺፋንዮስ ከመነኩሴው እግር ሥር ሰግዶ ክርስቲያን እንዲያደርገው ለመነው፡፡ መነኩሴውም ወስዶ ለኤጲስቆጶሱ ሰጠውና አስተምሮ አጠመቀው፡፡ መመንኮስም አንደሚፈልግ ቢነግረው "ሀብት ንብረት እያለህ መነኩሴ መሆን አይገባህም" አሉት፡፡ ከዚህ በኀላ ኤዺፋንዮስ እኅቱን አምጥቶ አስጠመቃትና ገንዘቡን ሁሉ ሸጦ ለድኆችና ጦም አዳሪዎች መጸወተው፡፡ በተረፈው ደግሞ ቅዱሳት መጻሕፍትን ገዛ፡፡ ከዚህም በኀላ መነኮሰና ለእርሱም ለእኅቱም ለጥምቀት ምክንያት ወደሆነው ስሙ ሉክያኖስ ወደተባለው መነኮስ ገዳም ገባ፡፡ በዚህም ጊዜ ዕድሜው 16 ብቻ ነበር፡፡
ከዚህም በኀላ ሽማግሌውን አባ ኢላርዮስን አገኘውና ሕግጋትን ሁሉ አስተማረው፡፡ ከዚህም በኀላ መናንያኑ እስኪያደንቁት ድረስ በፍጹም ትጋትና ቅድስና ተጋደለ፡፡ ብዙ አስገራሚ ተአምራትን አደረገ፡፡ ድውያንን ፈወሰ፣ በጸሎቱ ሙታንን አስነሣ፣ ከደረቅ መሬት ላይ ውኃን አፈለቀ፡፡ ያለጊዜውም ዝናም አዘነመ፡፡ ብዙ አይሁዶችንም ተከራክሮና በተአምሩ እያሳመነ አጠመቃቸው፡፡
ከዚህም በኀላ መምህሩ ኢላርዮስ በነገረው ትንቢት መሠረት በቆዽሮስ ደሴት ላይ ዻዻስ ሆኖ ተሾመ፡፡ ብሉይን ከሐዲስ የወሰነ እጅግ ምጡቅ ሊቅ ነውና ብዙ መጻሕፍትን ተረጎመ፡፡ በሺሕ የሚቆጠሩ እጅግ ጠቃሚ ድርሳናትን ደረሰ፡፡ በአፍም በመጽሐፍም ብሎ መናፍቃንንና አይሁድን ምላሽ በማሳጣቱ ቤተ ክርስቲያን "ጠበቃየ" ትለዋለች፡፡ ከደረሳቸው መጻሕፍት መካከል "ሃይማኖተ አበው ዘኤዺፋንዮስ፣ መጽሐፈ ቅዳሴውና አክሲማሮስ (ስነ ፍጥረት የሚተነትን) በዋነኛነት ይጠቀሳሉ፡፡ በተለይም አክሲማሮስ በተሰኘው ድርሰቱ ስነ ፍጥረትን እንዴት አድርጎ እጅግ ጥልቅ በሆነ መንገድ እንዳብራራው በቃላት ለመግለጽም አስቸጋሪ ነው፡፡ እጅግ በጣም የሚደንቅ ነው በእውነት፡፡ እግዚአብሔር ለቅዱሳኑ የሚገልጥላቸውን ሰማያዊ ዕውቀት ከማድነቅ ውጭ ልላ ምን ማለት እንችላለን!!!
ሊቁ ቅዱስ ኤዺፋንዮስ በመልካም እረኝነትና በሚደነቅ ቅድስና ሲያገለግል ኖሮ በ406 ዓ/ም ዐርፏል፡፡ የዕረፍቱን ሁኔታ በተመለከተ ከዮሐንስ አፈወርቅ ጋር የተገናኘ ታሪክ አለው፡፡
በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ዘመን የነበረችው ጨካኟና አረመኔዋ ንግሥት አውዶክሲያ የድሃ ንብረት እየቀማች ተወስድ ስለነበር ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም ዘወትር ይመክራትና ይገሥጻት ነበር፡፡ አንድ ቀን አንዱ ድሃ ሄዶ ለዮሐንስ አፈወርቅ ነግሮት ሄዶ ‹‹የድሃውን ንብረት መልሺለት›› ቢላት እምቢ ስትለው ከቤተ ክርስቲያን እንዳትገባና ከክርስቲያኖችም ህብረት እንዳትቀላቀል አወገዛት፡፡ ‹‹ከግዝትህ ፍታኝ›› ብትለውም ‹‹የድሃውን ገንዘብ ካልመለሽ አልፈታሽም›› ስላላት ‹‹በከንቱ አወገዘኝ አባት ያስተምራል እንጂ እንዲህ አያደርግም›› እያለች ታስወራበት ጀመር፡፡ ለቅዱስ ኤጲፋንዮስም ‹‹ዮሐንስ ያለ አግባብ አውግዞኛልና መጥተህ አስፈታኝ አለዚያ ሃይማኖቴን እቀይራለሁ፣ ቤተ ክርስቲያንንም አቃጥላለሁ›› ብላ ላከችበት፡፡ ቅዱስ ኤጲፋንዮስም ሄዶ ዮሐንስ አፈወርቅን ‹‹ሰይጣን በልቧ አድሮባታል ያሰበችውንም ያስፈጽማታልና ለአገልግሎታችንም እንቅፋት እንዳትሆን ፍታት›› ቢለው ቅዱስ ዮሐንስም እምቢ አለው፡፡ እርሷም በየከተማው እየዞረች ‹‹ተመልከቱ ዮሐንስ ኤጲፋንዮስንም አወገዘው›› እያለች በውሸት ታስወራ ጀመር፡፡ ኤጲፋንዮስም እንዲህ ማለቷን አልሰማም ነበርና ከዮሐንስ ጋር በኋላ ተሰነባብተው ሊለያዩ ሲሉ ዮሐንስ ‹‹ለምን በነገሬ ገባህብኝ›› አለው፡፡ ኤጲፋንዮስም ‹‹አልገባሁም›› ቢለው በንግግር ሳይግባቡ ቀርተው ተጣሉ፡፡ በዚህም ጊዜ ሁለቱም የሚሞቱበት ጊዜና የሚሞቱበት በምን ዓይነት ሁኔታ እንደሆነ ተገልጦላቸው አንዳቸው ለአንዳቸው ትንቢት ተነጋግረዋል፡፡ ዮሐንስ ኤጲፋንዮስን ‹‹ሄደህ ከቤትህ አትገባም ከመንገድ ላይ አንበሳ ሰብሮ ይገድልሃል›› አለው፡፡ ኤጲፋንዮስም ለዮሐንስ ‹‹የእኔን ትላለህ አንተም እንጂ ደግሞ ተግዘህ በከሃዲዮች ተወግዘህ በአንጾኪያ ደሴት ታስረህ ተሠቃይተህ ትሞታለህ›› አለው፡፡ በተነጋገሩትም ትንቢት መሠረት ኤጲፋንዮስ ወደ በዓቱ ሲሄድ አንበሳ ገደለውና የአንበሳ ሆድ መቃብሩ ሆነለት፡፡ ስንክሳሩ ግን በመርከብ ሲሄድ እንዳረፈ ይገልፃል፡፡ ዮሐንስም በግዞት ታስሮ ብዙ ከተሠቃየ በኋላ ግንቦት 12 ቀን ዐረፈ፡፡ ጨካኟና አረመኔዋ ንግሥት አውዶክሲያም ‹‹ዮሐንስ ኤጲፋንዮስን አውግዞት ወደ ሀገሩ አባሮት በመንገድ ላይ እንዲሞት አደረገው›› እያለች በሀሰት አስወርታ የቤተ ክርስቲያን ጠላቶች የሆኑትን ሰዎች ሰብስባ ዮሐንስን እንዲያወግዙት ካደረገች በኋላ በግዞት ታስሮ እንዲኖርና ተሠቃይቶ እንዲሞት አድርጋዋለች፡፡
የቅዱስ ኤዺፋንዮስ ምልጃና በረከቱ በምልጃው በምንታመን በሁላችን ላይ ይደርብን! አሜን!!!
(የግንቦት ወር ስንክሳር፣ የቅዱሳንታሪክ-37-39፣ መዝገበ ታሪክ፣ የዲ/ን ዮርዳኖስ አበበ ጽሑፍ)

Thursday, August 20, 2015

ፖርት ሳይድ ማርያም በግብጽ

ከስዕልዋ ዘይት የሚፈልቅበት ተአምር አድራጊዋ የእመቤታችን ስዕል ፖርት ሳይድ ማርያም በግብጽ; በረከትዋ ይደርብን:: መጋቢ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ




ከእጇ ዘይት የሚፈልቅ የቅድስት ኤልሳቤጥ አስገራሚ ታሪክ

Tuesday, August 18, 2015

አቡነ ሐራ ድንግል ገድል



ከሁሉ አስቀድመን የአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንልጆች የሆን እኛ የክርስቶስ ወገኖች ሰዎች ነገርን ከማብዛት በማሳነስ ነገርን ከማስረዘም በማሳጠር ክቡርና ልኡል ትሩፋቱ ፍፁም ገድሉም ብዙ የሆነ ምስራቃዊ የክብር ኮከብ አርያማዊ የፅድቅ ጸሀይ የኦርቶዶክሳዊ ሀይማኖት ዓምድ የመንፈሳዊ ምግባርማደሪያ የሆነየአባታችን ሐራ ድንግልን ገድሉንና ትሩፋቱን የፅድቁንም ስራ እንጽፍ ዘንድ ህይወትን ሰጪ በሚሆን በባታዊ አድሮ በሚኖር ገዳማዊውን በሚጎበኝ የአለማዊውንም ሰው በደል በመለኮታዊ ስልጣኑ በሚያስተሰርይ በአምላክ ፈቃድ ለመጀመር ተግተን ተመኘን፡፡ ለሁላችንም የጥምቀት ልጆች ከኦሪታዊው ከሙሴና ከወንጌላዊው ከዮሀንስ ጋር አሸናፊ እግዚአብሄርን በቀናች ሀይማኖትና በመልካም ምግባር ካገለገሉት ከጻድቃንና ከመነኮሳትም ጋር ሰማያዊ የነፍስ ደስታ እድልን ያድለን ክብር ምስጋና ለእርሱ ይሁን ለዘላለሙ አሜን፡፡ አቡነ ሐራ ድንግል አስቀድመን በመጻፋችን የጠራነው የዚህ ጻድቅ አባቱና እናቱ በላጉና ምድር ይኖሩ ነበር ፡፡ እርስዋም ከደራ ምድር አንድ ክፍል ናት:: አባቱም ዮሐንስ የሚባል የሬማ ቄስ ነበር:: እናቱም ወለተ ጊዮርጊስ ትባል ነበር ሁለቱምበወገን ከከበሩ ቤተሰቦች ነበሩ እነርሱም ጻድቃንና ደጋግ ሰዎች እግዚአብሄርን የሚፈሩ ነበሩ ከክፋትም ስራም ሁሉ የራቁ ነበሩ በበጎ ምግባርም ሁሉ የጸኑ ነበሩ ሶስት ወንዶች ልጆች ነበሯቸው ከእነርሱም አንዱ የአለም መብራት የኢትዮጵያ ብርሀን ሐራ ድንግል ነበር ይህንም ገድለኛ ልጃቸውን ከመውለዳቸው አስቀድሞ ገንዘባቸውን ለድሆችና ለጦም አዳሪዎች ለባልቴቶችና ለሙት ልጆች ለካህናትና ለምእመናን ለህዝበ ክርስቲያኑ ሁሉ ይሰጡ ነበር :;ይህንም ያደርጉ ነበር ስጡ ይሰጣችኋል ዳግመኛም ለሌለው ይስጥ የሚለውን የወንጌል ቃልና ሌላውም መጽሀፍ ካለህ ስጥ ከሌለህም እዘን የሚለውን ቃል አስበው ነው:: በዚህም ነገር ላይ እንዲህ እያሉ ይጸልዩ ነበር አንተን ደስ የሚያሰኝ ፈቃድህንም ሁሉ የሚያደርግ በደግነቱም ለፍጥረትህም ሁሉ የሚጠቅም ሰሎሞን:-ብልህልጅ አባቱን ደስ ያሰኛል ሰነፍ ልጅ ግን እናቱን ያሳዝናል ብሎ እንደተናገረ የእኛንም ልብ ደስ የሚያሰኝ ጠቃሚ ልጅ ስጠን ጸሎትም እንደሚጠቅም ከቅዱሳት መጻህፍት ምሳሌ አግኝተው ይህን ሁሉ ጸሎት ጸለዩ:: ሀና በአንደኛ መጽሀፈ ነገስት ለሚጸልይ የጸሎትን መልስ ይሰጠዋል የጻድቃኑንም እድሜ ያረዝማል ብላለች ዳዊትም:-66 መዝሙር መንገድህን ለእግዚአብሄር ግለጥ በእርሱ ታመን እርሱም ያደርግልሀል ብሏል፡፡

ከዚህም በኋላ እግዚአብሄር ጽሎታቸውን ልመናቸውንና እንደ ጣፋጭ ዕጣንና እንደ ንጹህ መሥዋዕት በተቀበላቸው ጊዜ በዚያች ዕለት በጋብቻ ስርአት ተገናኙ ሁለቱም በንጽህና ሐብል የታሰሩ ነበሩና ዝሙትንና ሀጢያትንም አያውቁም ነበርና ነገር ግን :-ወንድ ሁሉ በሚስቱ ጸንቶይኑር ሚስትም በባልዋ ጸንታ ትኑር በሚለው የመጽሀፍ ስርዓት እርስ በርሳቸው ይጠባበቁ ነበር፡፡ በዚያችም በተገናኙባት እለትም ወለተ ጊዮርጊስ መልካም ስራው እንደጸሀይ አወጣጥ የሚያበራ የኢትዮጵያ ብርሀን ሐራ ድንግልን ጸነሰችው ከጸነሰችውም በኋላ በዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በንጉስ አጽናፍ ሰገድ ወለደችው:እርሱንም በወለደች ጊዜ እጅግ ደስ አላት አባቱና ዘመዶቹም እጅግ ደስ አላቸው ሀሴትም አደረጉ ሃጥአንን በእግዚአብሄር ዘንድ በጸሎቱ የሚያስምራቸውና ዳዊት በ111ኛው መዝሙሩ :-መልካም ዛፍ መልካም ፍሬ ያፈራል ክፉ ዛፍ ግን ክፉ ፍሬን ያፈራል ዛፍ ከፍሬው ይታወቃልና ብሎ እንደ ተናገረ ወላጆቹን በምእመናን ሁሉ አንደበት የሚያመሰግናቸው የተባረክ ልጅ ተወልዶላቸዋልና በአርባኛው ቀንም ይህን ልጃቸውን ሐዋርያት በኢየሩሳሌም አንድ ሆነ እንደ አዘዙትሥርዓት የዚያች ቤተክርስቲያን ወሰዱት ያንጊዜም በጥምቀት ፀጋ የወለደው ስሙን ሐራ ድንግል ብሎ ሰየመው:: ከዝያም በኋላ አባቱና እናቱ ተቅብለው ወደ ቤታቸው ወሰዱት በህግና በሥርዓትም አሳደጉት የሰሎሞንን ቃል አውቀው ቅዱሳት መጽሀፍትን ብሉይ እስክ ሀዲስ የዳዊትንም መዝሙር ለሚያስተምር መምህር ሰጡት ያም ህፃን ቅዱሳት መጽሀፍትን ይሚሉትን አውቆ ስላስተዋለ እስኪያድግና አቅመ አዳም እስኪደርስ ድረስ ለትምህርት የተጋ ሆነ በመምህሩ ፈቃድ የድቁና ሹመት ከጳጳሱ ይቀበል ዘንድ በዚያ ወራት ሄደ የድቁና ሹመትም ተቀብሎ በደስታና በሀሴት በሰላምና በህይወት ወደ መንደሩ ተመልሶ ገባ
የጥበባት ባህርና የቋንቋ ባለቤት ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም የትምህርት ምንጭ ለሆነው ለደቀ መዝሙሩ ለጢሞቴዎስ በላከው መልእክቱ:-የዲያቆናት ንጹሓን ይሁኑ ለጸሎትም የነቁና የተጉ ይሁኑ ብሎ እንደተናገረ በንጽህናና በቅድስና በጸሎትና በጭምተኝነት በፍቅርና በትህትና እግዚአብሄርን ያገለገለው ጀመር፡፡ አባታችን ሐራ ድንግልም በእነዚህ የብሉይና የሐዲስ መጽሀፍት ቃላት ጸንቶ ሲኖር ክቡር ዳዊት 88 መዝሙር ሞትን ሳያይ በህይወት የሚኖር ማነው? ዳግመኛም 143 መዝሙር ሰውስ ከንቱ ይመስላል ዘመኑም እንደ ጥላ ያልፋል ብሎ እንደተናገረ:: በአቤልና በሴት ከተጀመረው ከዚህ ሞት የሚድን ስለሌለ አባቱና እናቱ ከዚህ ዓለም ድካም ዓረፉ ወደ ዘላለም ህይወትም ሄዱ አባታችን ሐራ ድንግልም በወላጆቹ ሞት የመረረ ልቅሶን አለቀሰ አዘነም፡፡ አባታችን ሐራ ድንግልም ከአባቱና እናቱ ሞት በኋላ ሬማ በምትባል ደሴት እየተመለለሰ በቤታቸው ውስጥ ለጥቂት ወራት ተቀመጠ ከሬማም ወደ ዘጌ ይሄድ ነበር ከዘጌም ወደዚያው ወደ ሬማ ይመለስ ነበር እንደዚህ አለም ሰዎችም ሚስት ሊያገባ አልወደደም ነገር ግን በድንግልና ኖረ::ልብሰ ምንኩስናም ሳይለብስ አርባ ዓመት ሆነው ከዚህም በኋላ በጽኑዕ ደዌ ታመመ የንዳድ በሽታም ያዛው ክደዌው ጽናት የተነሳም በስጋውና በነፍሱ ከእግዚአብሄር ፈውስን ያገኝ ዘንድ ልብሰ ምንኩስናን ለመልበስ ወደደ መዓዛ ድንግል የተባለውን የሬማ መምህር ልብሰ ምንኩስናን ይሰጠው ዘንድ ለምኖ ነገረው እርሱም ልብሰ ምንኩስናን አለበሰው ለወጣንያን ለማእከላውያንና ለፍፁማንም መነክኮሳት የሚገባቸውን የምንኩስናን ህግ ሁሉ ሰጠው ከዚህም በኋላ እግዚአብሄርን ከሞት ስላዳነው ከደዌው ተፈወሰ::ከዚህም በኋላ የቅስና ማረግን ከዚያ ጳጳስ ከተቀበለ በኋላ በዚሁ ደስ እያለውናሀሴት እያደረገ ከመንገዱ ተመልሶ ወደ ቤቱ ገባ እግዚአብሄር እርሱ የተመኘውንና የፈለገውን አድርጎለታልና በዚህ ሁኔታ እያለ ወደ አለም መመልስ አልፈለገም ተመልሶ ከዘመዶቹና ከሀገሩ ሰዎች ተሰውሮ ወደ ሸዋ ሊሄድ ወደደ ወደ አሰበበት ለምድረስ በመንገድ ላ ሲሄ ዘመዶቹ ወደ ሀገራቸው ሲመለሱ ያገኙትና ከ እነርሱም አንዱ የወንድሙ ልጅና የልቡ ወዳጅ ስለንበር ሁሉንም ያነሳሳቸው አርከ መርዓዊ ይባላል እነርሱም ግራርያ በተባለ ሀገር ያዙትና ወዴት ትሄዳለህ አሉት እባክህ ወደ ሀገርህ ተመለስ ለሀገርና ለዘመዶችህ የሚቀርብ ገዳም እንፈልግልሃለን አንተም እንዳዘዝከን እንደርጋለን እንጂ ከፈቃድህ አንወጣም አንተ አባታችን ጽድቀህ እኛንም በጽድቅህ እንድታጸድቀን ትሉ ከማያንቀላፋ እሳቱም ከማይጠፋ ከገሀነም እሳት እንድታድነንም እንወዳለንና እንደማንሸነግልህ ም በአምላካችን በ እግዚአብሄር ስም እንምልልሀለን ይሄን ቃላቸውን ከሰማ በኋላ እሺ አላቸው::እንሱም 7 ምሳሮች ይዘው ከቁስቋም ጀምረው ገዳም እስካደረገው ድረስ መንገዱን ይጠርጉ ዛፎችንም ይቆርጡ ጀመሩ ወደ ገዳሙ በደረሱ ጊዜ ማረፊያዬ ይህች ናት በድካሜም ጊዜ የማርፍበት ትንሽ ቤት ስሩልኝ እንጂ ከዚህ ወደ ሌላ አትሂዱ እስከሞቴ ድረስ በ እርሷ እንድኖር እግዚአብሄር አዞኛልናየስጋዬንም በድን እስከ ሙታን ትንሳኤ ድረስ በውስጧ ይኖራል አላቸው በዚያችም ቀን ዕንጨቱን ቆርጠው መሬቱን ቆፍረው አጥር አጠሩለት እርሱንም በገዳሙ ትተውት ወደ ቤታቸው ሄዱ አባታችን ሐራ ድንግልም በተራበ ጊዜ እንጀራ አይበላ ነበር ጥቂት ምስር አተርና አደንጓሬ ይበላ ነበር ብትንሽ ጽዋ መክደኛ ጽዋ ሰፍሮ በትንሽ ድስት ይቀቅለው ነበር ያም በጽዋው መክደኛ ሰባት መስፈሪያ ነበር በሶስት አንድ ቀን ይመገበው ነበር ከምድርም ፍራፍሬም በበላ ጊዜ እሼ የሚባል ፍሬ ይመገብ ነበር ከምናኔው በኋላ ግን ከውሃ በቀር ሌሎች መጠጦችን አልጠጣም ነበር::ያንጊዜም ብዙዎች አራዊት አንበሶች ነብሮች ዝሆኖች ተኩላዎችና ጅቦች የዱር እንስሳዎች ያስፈራሩት ዘን ወደ እርሱ መጡ እርሱ ግን እግዚአብሄር ከእርሱ ጋር ስለነበር ከፊቱ እንዲሸሹ አስፈራርቶ አስደነገጣቸው እንጂ አልፈራቸውም ይህም ነገር ከሆነም በኋላ የቅል ዓይነት ተክልና ወይን ሎሚና ኮክ ተከለ እነዚህንም ተክሎች ከሩቅ ወንዝ ውሃ በእጁ ቀድቶ በትከሻው ተሸክሞ ያጠጣቸው ነበር መንገዱም ሩቅ ስለነበር አባታችን ሐራ ድንግል እንዲህ ብሎ ጸለየ ከ እናቴ ማህጸን ያወጣሀኝ እስከ እዚች ሰአት ያደረስከኝ ፈጣሪዬ እግዚአብሄር ሆይ እስራኤል ከግብጽ በወጡ ጊዜ ሙሴ ከዓለት ውሃን እንዳወጣ ከዚህ ምድር ውሃን አውጣ ዘንድ ጸሎቴንና ልመናዬን ስማኝ ይህን ብሎ በሁለት ረድፎች ምድሩን ቆፈረ በመስቀልም ምልክት ባረካቸው ወዲያውኑ ከሁለቱም ረድፎች ውሃዎች ፈሰሱ በፈለቁት ውሃዎች በየጊዜው እንዲያፈሩና ሊያዩት ወደ እርሱ ለሚመጡት ሰዎች ምግብ እንዲሆኑ እንዚህን ተክሎች አጠጣቸው ለሚልውምኑትም ድሆችም ቅጠሉ ፍሬ ያፈራውን አይነት በገበያ አሽጦምጽዋት ይሰጣቸው ነበር::በዚያ ጊዜም የበጎ ነገር ጠላት ሰይጣን በሴት አምሳል በንጭ ሀር በወርቅበብር በጉትቻዎችና በቀለበቶች አጊጦ መጣና እንዲህ አለው ለምን ብቻህን ትኖራለህ ? ሁለት ሆነው መኖር ሰዎች ልማዳቸው ነውና ከ እኔ ጋር ብትኖር አይሻልህምን? አባታችንም ትቆጣ የ እግዚአብሄርን ቃል በሚጸልይበት በጠበል እቃ የነበረውን ውሃ በሰይጣ ረጨበት ሰይጣንም ድንግጦ ሸሸ በባህርም ስጠመ አባታችን እስኪሰማ ድረስ ባህሩን አወከው አባታችንን ለማሳት ሰባት ጊዜ መጣ ነገር ግን በ እግዚአብሄር ሀይል ድል ተደረገ::
አንዲት ሚዳቆ ነብር እያባረራት መጣች ወደ አባታችን ሐራ ድንግል ቤትም ገብታ በእርሱ ተመአጥና ከ እግሩ በታች ተጋደመች አባታችንም ወደ ፈጣሪው ወደ እግዚአብሄር እየጸለየና እየለመነ ተቀምጦ ነበር ያቺን ሚዳቆ የሚያባርራት ነብርም መጣ አባታችን ወዳለበት ደርሶ በደጁ ቆመ አባታችንንም ባየው ጊዜ ጊዜው ቀን ስለ ነበረ ፈርቶ ወደ ውስጥ አልገባም ያም ነብር ተቆጥቶ በዚያው ቦታ ተፍገመገመ አባታችን ነብሩን ገድለህ ትበላት ዘንድ እግዚአብሄር አልሰጠህም ነብሩም ይህን ነገር ከአባታችን ቃል ሰምቶ ሳይገድላት ሄደ በዚያች ሌሊት በእርሱ ዘንድ አደረች በማግስቱም ከቤቱ ወጥታ በደጅ ስትመላለስ አባታችን ባያት ጊዜ እንዲህ ብሎ አሰናበታት ከቦታሽ አባርሮ ያሳደደሽ ወደ እኔም ያደረሰሽ ያ ነብር ትናንት ስለሄደ ወደ ቦታሽ ሂጂ ይህንም ሰምታ ወደ ቦታዋ ተመለሰች:;
አባታችንም ሁለት ደቀመዝሙሮች ነበሩት ወንዱ እሱን ያዘዘውን የሚፈጽም ነበር ተስፋዬ እና አመተ እግዚእ አለምን ንቃወደ ገዳብ የገባች ነበረች እርሳውም ከአባታችን ቤት ትንሽ በሚርቀው ቤት ተቀምጣ ከምናኔዋ ጀሮ በሞት እስከ ተለየች ድረስ ረዳትና አገልጋይ ሆና ራሷን ለአባታችን ሰጠች እርስዋም በስጋ ዝምድና ከሚቀርቡት አንድዋ ነበረች እርሷም በአገልግሎቷና በታዛዥነቷ እንደዚህ ይሁን የሚለውን ፈቃዱን በመፈጸም እጅግ ደስ አሰኘችው በምግባርዋ ደግ በነገሯም እውነተኛ በልቡናዋም ብልህ ነበረች::
ከዚህም በሃላየአንዲት ታቅ ሴት አሽከሮች ወደ አባታችን መጡ ሊጣሉትም ወደቤቱ ገቡ አንተ ከንጉሱ ፈቃድ ወጥተህ በአመጽ የምትኖር የንጉስ ከዳተኛ አይደለህምን እያልይ ፈጽመው ሰደቡት ከገቡበትም ወጥተው የ አባታችን የወይን ዘለላም ምንም ሳያስቀሩለት ቆረጠው ወሰዱ አባታችንም ምንም አልተናገራቸውም የወሰዱትንም ወይን ለእመቤታቸው የወይኑ ዘለላ ሰጡ እመቤታቸውም ይሀ ወይን ከማን አመጣችሁ ሐራ ድንግል ከሚባለው መንኮስ ነው አላት አንዱንም የሆድ በሽታ ይዞ አንጀቱን ቆረጠው እመቤታቸውም እነዚህን አንተን ያስቀየሙ የበደሉና ማርልኝ ብላ አሽከሮችን ላከች እግዚአብሄር ይቅር የሚላቸውና በደላቸውና የሚተውላቸው ከሆነ ይቅር እላቸዋለሁ አሽከርም በተመለሰ ጊዜ ሆዱን የቆረጠው ሞተ ጻድቁ አባታችንን ስለተሳደበ እግዚአብሄር ትቆጥቶታልና ይህ የሰሙትን የተደረገውን ባዩ ጊዜ አደነቁ:: ይህ ድንቅ ነገር ከሆነ ረዥም ወራት በሃላ አመተ ወልድ የተባለች አንዲት ሴት ታመመች እርስዋም በዚሁ በሽታ ሞተች መላእክተም ሞትም ነፍስ ወሰዱ ያችንም ነፍስ እያጣደፉና እያዳፉ ወደ ፈጣሪዋ አደረሳት በዚች ሰአትም አባታችን ሐራ ድንግል ወደ ፈጣሪው ወደ እግዚአብሄር እንዲህ እያለ ጸለየ አለቀሰም ይህችን ዛሬ የሞተችውን ሥጋዋም በመሬት ተጥሎ በነፍስዋ ወደ አንተ የመጣችውን ማርልኝና አንሳልኝ ነፍሴንና ስጋዬን በአንተ ላይ ጥያለሁ ብላ በእኔ ላይ እንደ ተማጠነች አቤቱ አንተ ራስህ ታውቃለህና በህይወት ሳለችም እንዳገለገችኝ አንተ ራስህ ታውቃለህ አባታችንም ይህን ጸሎት ጸልዮ ዝም አለ እግዚአብሄርም ይህችን ነፍስ ለምን ወደ እኔ አመጣችሃት የሕራ ድንግል አደለች የ እርሱ ስለሆነች ወደ እርሱ መልሳት እርሳም በስማይ ሳለች ከፈጣሪዋ አንደበት ከሰማች በኋላ የመላእክት ቅዱስ ገብርኤልን ለወዳጄ ሐራ ድንግል ሶስት ጊዜ እንዲህ ብለህ አዋጅ ንገር ሲለ ከዚያ ከፈጣሪ አንደበት ሰማች:: ሐራ ድንግል ሆይ በ እጅህ የተባረከውንና በቃልህ የተጽናናውን ስምህን የጠራውንና መታሰቢያህን ያደረገውን ለተራቡትም ለተጠሙትም እህልና ውሃ በመስጠት በዓልህን ያከበረውን ሀጢአተኛና በደለኛ ሳለም በጸሎትህና በቃል ኪዳንህ የታመነውን የገድልህንም መጽሀፍ ያጻፈውን ያነበበውንና የተረጎመውን የሰማውንና ለሰዎች ያሰማውን አጽምህንም እየጠበቀ በገዳምህ የተቀመጠውን አንተን ወድዶ ከሩቅ ወይም ከቅርብ ሀገር በመምጣት ገዳምህን የጎበኘውን ወንድ ልጁንና ሴት ልጁንም በስምህ የጠራውን እነዚህ ሁሉ በየወገናቸው ከስጋና ከነፍስ ባርነት ነጻ የወጡ ይሆኑ ዘንድ እስከ ሰባት ትውልድ ምሬልሃለሁ አንተ አገልግለሃልና ከህፃንነትህም ጀምረህ እስከዚች ሰአት ፈቃዴን ፈጽመሃልና:: በሞት ከሥጋዋ የተለየች ያች ነፍስም ይህን ነገር በሰማች በኋላ ከሰማይ ተመለሰች ከሥጋዋ ጋር ተዋህዳ በአባታችን ጸሎት ተነሳች ለወዳጄ ሐራ ድንግል ሂድና አዋጅ ንገር ብሎ መላኩ ገብርኤልን ሲያዝዘውከ እግዚአብሄር የሰማችውን ቃል ኪዳን ለሰዋች ተናገርች አባታችን ሐራ ድንግልም በጸጋ አወቀ የእግዚአብሄር ምስጢር ባየችው በዚች ሴት መነሳት ደስ አለው::እግዚአብሄርም ለአባታችን ሁለት ቃል ኪዳን ሰጠው አንደኛው ያቺ ሴት ናት ሁለተኛውም ከዚህ አለም በሞት ተለይቶ ወደ ዘላአለም ህይወት በሄደ ጊዜ እግዚአብሄር የሰጠው ነው:: የአባታችን ሐራ ድንግልም የእረፍቱ ቀን በደረሰ ጊዜ እግዚአብሄር የምህረትና የይቅርታ ቃል ኪዳንን ይሰጠው ዘንድ ከሰማይወደ እርሱ መጥቶ ወዳጄ ሐራ ድንግል ሆይ ስለ እኔ ብዙ አመታትን ደክመሃል እኔም እንዲህ ብዬ ቃልኪዳ እስትሃለሁ:: ሐራ ድንግል ሆይ በ እጅህ የተባረከውንና በቃልህ የተጽናናውን ስምህን የጠራውንና መታሰቢያህን ያደረገውን ለተራቡትም ለተጠሙትም እህልና ውሃ በመስጠት በዓልህን ያከበረውን ሀጢአተኛና በደለኛ ሳለም በጸሎትህና በቃል ኪዳንህ የታመነውን የገድልህንም መጽሀፍ ያጻፈውን ያነበበውንና የተረጎመውን የሰማውንና ለሰዎች ያሰማውን አጽምህንም እየጠበቀ በገዳምህ የተቀመጠውን አንተን ወድዶ ከሩቅ ወይም ከቅርብ ሀገር በመምጣት ገዳምህን የጎበኘውን ወንድ ልጁንና ሴት ልጁንም በስምህ የጠራውን እነዚህ ሁሉ በየወገናቸው ከስጋና ከነፍስ ባርነት ነጻ የወጡ ይሆኑ ዘንድ እስከ ሰባት ትውልድ ምሬልሃለሁ አንተ አገልግለሃልና ከህፃንነትህም ጀምረህ እስከዚች ሰአት ፈቃዴን ፈጽመሃልና::
አባታችን ሀራ ድንግል ይህን ቃል በሰማ ጊዜ እግዚአብሄርን ሲያመሰግን እንዲህ አለ አምላኬ ሆይ ከፍ ከፍ አደርግሃለሁ ቅዱስ ስምህንም ለዘላለም አከብራለሁ ሁልጊዜ አመሰግንሃለሁ ስምህንም ለዘላለም ዓለም አከብራለሁ ደግ ወይም ክፉ ቢሆን በእኔ የተማጠነ ሰው ሁይድን ዘንድ ይህን ቃል ኪዳን ሰጥተሀኛል እግዚአብሄርም ይህን ምስጋና ከእርሱ ከተቀበለ በኋላ ከእርሱ ዘንድ ሄደ:: ገዳሙንም እንዲህ እያለ ባረካት የአብና የወልድ የመንፈስ ቅዱስም በረከት በገዳሜና ስሜን በሚተሩ ሁሉ ላይ ይደር አምላክን በወለደች የ እመቤታችን የማርያም በረከትም በገዳሜና እኔን በሚወድዱ ሁሉ ላይ ይደር የሚካኤልና የገብርኤል በረከት የማያንቀላፉ ትጉሃን ዝም የማይሉና አመስጋኞች የሆኑ የሱራፍኤልና የኪሩቤል በረከት በገዳሜና በእኔ በሚማጸኑ ሁሉ ላይ ይደር የ እስጢፋኖስ የጊዮርጊስ የመርቆርዮስ የፋሲለደስ የቴዎድሮስና የገላውዴዎስ የድል አድራጊዎች ሰማእታት ሁሉ በረከት በገዳሜና ፈቃዴን በሚፈጽሙት ሁሉ ላይ ይደር የ አባታችን አቡነተክለሀይማኖትና የ አባታችን አዎስጣቴዎስ የ አባታችን የገብረ መንፈስ ቅዱስና በኢትዮጵያ ውስጥ በገዳማትና በአድባራት በደሴቶችም የሚኖሩት ሁሉ በረከት በገዳሜና በውስጥዋ ሆነው አስከሬኔን በሚጠብቋት ሁሉ ላይ ይደር የሀይማኖት አምድና የቸርነት መዝገብ የሆነው እንደ መላእክትም በንጽህና የተሸለመው አባታችን ሐራ ድንግል ይህን ቃለ ቡራኬ ከተናገረ በኋላ በኢያቄምና በሐና በፋሲለደስና በገላውዴዎስ በፊቅጦርም በዓል ጥር አስራ አንድ ቀን ከዚህ ከሀላፊው ዓለም ድካም አረፈ:: በአሉም ጥር 11 ቀን በታላቅ ድምቀት በባህርዳር ይከበራል፡፡
ምንጭ ገድለ አቡነ ሐራ ድንግል ጽሎቱና በረከቱ ከሁላችን ከህዝበ ክርስቲያን ጋር ይኑር ለዘለዓለሙ አሜን!