Tuesday, September 15, 2020

የአየር አጋንንት በልባችን አድሮ እግዚአብሔርን እመቤታችንን እና ቅዱሳኑን ይሳደባል


/ብዙ ወንዶሞቼና እህቶቼ የሚሰቃዩበት ፈተና/
በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም
አጋንንት በሕይወታችን የሚያደርስብንን ችግር እስክናውቅ እንቸገራለን: ውጊያው እስኪገባን ግራ እንጋባለን: እውነቱ እስኪገለጥልን እውነቱ ሐሰት ይመስለናል።
ሼር በማድረግ በዚህ ፈተና ለሚሰቃዩ ወገኖቻችን አዳርሱ!
ተወዳጆች ሆይ በክፍል ሃያ ስድስት የአየር አጋንንት እና የአዚም መንፈስ በመደበኛና በጸሎት ሕይወታችን እንዴት እንደሚፈትነን አይተናል። በዚህ ክፍል ደግሞ ብዙዎች ለሰው የማይነግሩት የማያወያዩት ግን የሚቸገሩበትን እናያለን። የቅዱሳን አምላክ ምስጢሩን ይግለጽልን። ወዳጆቼ የአየር አጋንንት እና ሌሎቹም ርኩሳን መናፍት በውስጣችን ከገቡ ግራ እስኪገባን ድረስ ቅዱሳንን ይሳደባሉ፡፡ እስኪ ብዙዎቻችንን የምንቸገርበትን የራሳችን ሐሳብ እስኪመስለን የምንሰቃይበትን የአጋንንቱን የፈተና ስልት እንመልከት፡፡ አጋንንት በጌታ ሰው መሆን ወይም ሥጋ መልበስ ላይ መጠራጠር የሳድርብሃል፡፡ ሰው መሆኑም እውነት እንዳይመስልህ ያደርግሃል፡፡
እመቤታችንን ‹እውን በድንግልና ነው የወለደችው›› ብሎ ጥርጥር ያጭርብሃል፡፡  ልትቆጣጠረው በማትችለው ሐሳብ ከውስጥህ ሆኖ እግዚአብሔርን ይሳደባል።  አንተም ይህ ውስጣዊ የአጋንንት ስድብ ካንተ ወይም እራስህ ከልብህ አመንጭተህ የተሳደብክ ይመስልህና ከመጨነቅህ የተነሳ ድንግጥ ትላለህ፡፡ አንዳንዱ በድጋጤ ድርቅ ይላል፡፡ በእመቤታችን ላይ ከውስጥህ ጸያፍ ነገር የሚናገር ድምጽ ትሰማለህ። በተለይ ጸሎት ላይ ሆነህ ስዕሏን ስታይ ስታመሰግናት በማትቆጣጠረው መልኩ ከውስጥ ሲሳደብ ብሎም በሥጋ እንድታስብ ያደርግሃል።
ቅዱሳንን አፍ ባያወጣም ከውስጥ ሲሳደብ ትሰማለህ፣ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የማይሆን ነገር በማሳሰብና የሚያስደነግጥህ ነገር ከውስጥ ሲናገር ትሰማለህ፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን አትደናገጥ ቅዱስ ዮሐንስ በራዕዩ ‹‹ታላቅንም ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው›› በማለት አጋንንት በፈጣሪና በቅዱሳኖቹ ላይ የስድብን አፍ እንደሚከፍት ተጽፏል /ራዕ 13÷5/
ስድቡ ያናንተ ስላልሆነ እንዳትጨቅ፣ ነፍስህም ከእግዚአብሔር አንድነት የምትለይ አይደለችምና አትጎዳም፡፡ ሰይጣን ከውስጥ ሲሳደብ ነፍስ ትሰማለች ያኔም ትጨነቃለች ትደነግጣለች፡፡ ወዳጄ ነፍስ ፈጣሪዋን ስለምታውቅ ፈጣሪን አትሳደብም፡፡ ስድብ ቀድሞም ከነፍስ የተገኘ አይደለም፣ነፍስ ለዚህ ዓይነት ግብር አልተፈጠረችምና፡፡ ግን ስድቡን በውስጥ ሆኖ የሚናገረው የአየር አጋንንት እና ሌሎች ርኩሳን መናፍስት ናቸው፡፡ በተለይ የአየር አጋንነት: ዓይነ ጥላ እና ዛር ካለ በማያባራ መልኩ ይሳደባል። እንኳን ካንተ ከሰው መስማት የሚዘገንንህን የስድብ ናዳ በልብህ ጓዳ ሲያዘንብ ትሰማለህ።
ወዳጄ ሰይጣን ወደ እኛ ሕሊናና ልቦና ቀርቦ ይሳደባል፡፡ ያኔ ነው ስድቡ ከአንደበታችን ሳይወጣ በውስጥ የምነሰማው፡፡ በርትተን ከጸለይን እየመጣ ስድቡን የሚተነፍስብንን ስለሚተው እኛም ወደ ንጽሐ ጠባያችን እንመለሳለን፡፡
ወዳጄ ሰይጣን ወደ ሕሊናህ ቀርቦ ሲሳደብ ብትሰማ አንዲት ቃል አትናገር አትማረር ይልቁንም ‹‹ይህ ሐሳብ ያንተ ነው›› በለው፡፡ ሐሳቡ የእሱ እንደሆነ ከነገርከው ሥራውን ያውቃልና ይደነግጣል፡፡ አጋንንቱ ከሰው ጋር እያወራህ ድንገት በውስጥህ እግዚአብሔርን፣ እመቤታችንን ቅዱሳንን ሰድቦ ሊያስደነግጥህንና ትኩረትህን ሊያሳጣህ ይችላል፡፡ ያኔም ‹‹ይህ ሐሳብ ያንተ ነው በለው››
ወዳጄ ሰይጣን የሕሊናውን ያውቃልና ስትነግረው ይሰማል በዛም ያፍራል፡፡ መቼም ‹‹ስነግረው እንዴት ይሰማል?›› ትል ይሆናል፡፡ ባንተ ያደረች ላንተ የተሰጠች ጸጋ እግዚአብሔር ታሰማዋለች፡፡ ‹‹እግዚአብሔር ያሳፍርህ›› በለው፡፡ ሰይጣናት በክፉና ባልባሌ ሐሳብ የሚፈትናችሁ ከሆነ አትጨነቁ፡፡ ሰይጣን ልብ ውስጥ ሆኖ ለመሳደብ የዝሙት አጋንንትም ድረሻው ላቅ ያለ ነው፡፡ ፍትወትን በዓይነ ሥጋ እያሳየ የሚያሰቃየን አጋንንት ለስድብ ሰይጣናዊ ምላሱን መዘርጋት አይከብደውም፡፡
በጸሎት ሰዓት የስድብ ናዳ ከልቡ ጓዳ እያመጣ ሲጭንብህ እራስህ እንዳይመስልህ፡፡ ሰይጣን ነውና፡፡ ነፍስም የሷ መስሏት ትጨነቃለች፡፡ ወዳጄ እንደዚህ ያለን ጽኑ ስድብ አንተ/ቺ/ እንኳን የፈጠራችሁን እግዚአብሔርን ቀርቶ የምታውቁትን ሰው አትሰድቡም፡፡ ‹‹ማረኝ፣ ይቅር በለኝ፣ መንግሥትህን አትንሳኝ›› እያለች የምትጸልይ ነፍስ እንዴት ትሳደባለች? ነገር ግን የዚያ የርጉም ሰይጣንን ስድብ ሰምታ ጭንቅ ይሆንባታል እንጂ፡፡
ይህ ፈተና በጸሎት ጊዜ ይበርታ እንጂ በመደበኛው ሕይወትህ ማለትም ሥራ እየሰራህ እየተዝናናህ ከወዳጅህ ጋር እየተጫወትክ ቁም ነገር እያወራክ ድንገት ከውስጥህ ፈንቅሎ ጸያፍ የስድብ አሎሎ ይጭንብሃል። አንተ በሥጋህም በሕሊናህም ሌላ ስራ ይዘህ ሰይጣን ግን በውስጥህ እግዚአብሔርን እመቤታችንን ቅዱሳንን ይሳደባል አንተንም የሕሊና እረፍት ይነሳሃል። አንዳንዱንማ ጨርቅ መጣል ነው የሚቀረው እንጂ በቁሙ ያሳብደዋል። አንዳንዶች አጋንንት ውስጣቸው ሆኖ እግዚአብሔርን እመቤታችንን ቅዱሳንን የሚሳደበውን መቋቋም አቅቷቸው ለከፋ ሕመም የዳረጋቸው አሉ። የማይፈልጉትን እንደ ገደል ማሚቱ ከውስጣቸው የሚጮኸውን ስድብ ክፉ ሐሳብ መቋቋም አቅቷቸው እየተበሳጩ የሚጎዱ አሉ።
ወዳጄ በግልና በማህበር ጸሎት:በቅዳሴ ወዘተ ጊዜ ከውጥህ ሆኖ ወደ ሰማይ የሚሳደበው ለምንድነው? ካልክ አንደኛ ጸሎትህን እርግፍ አድርገህ እንድትተው ነው። ሁለተኛ እግዚአብሔርን እያሰብክ የፍቅርና አባትነት ስሜት ሳይሆን የፍርሃት ስሜት እንዲሰማህ ለማድረግ ነው። ሦስተኛ እግዚአብሔር ምህረት ሰጪ ሳይሆን ቀጪ ነው የሚለውን ክፉ መርዙን ሊተክልብህ ነው። አራተኛ የተሳደብኩት እኔ ስለሆንኩ እግዚአብሔር አይምረኝም ይቅር አይለኝም እንድትል ነው። አምስተኛ ተስፋ አስቆርጦህ ከመንፈሳዊ ሕይወት ሊያስወጣህ ሲፈልግ ነው። ስድስተኛ ነፍስህ በመንፈስ እንዳትቦርቅ ሥጋህ እንድትጨነቅ ስለሚፈልግ ነው። ሰባተኛ ከውስጥህ በሚሳደበው ስድብ አስጨንቆህ እራስህን ከመጉዳት እስከ ሞት ሊያደርስህ ነው።  ስለዚህ ንቃበት!
ከዚህው ጋር በተያያዘ ሰይጣን በሕሊናችን በጸሎት ሰዓት ስለሚሳደብ እኛ የተሳደብን የሚመስለን ለምንድነው? ካልን ከውስጥ ከሚወጣ ምስጋና ጋር ስድብ ስለሚወጣ ነው ከራሳችን የሚመስለን፡፡ ነገር ግን ምስጋናችን ከሰይጣን ስድብ ጋር አይቆጠርም፡፡ እኛ ፈጣሪ ፊት የቆምነው ለስድብ ሳይሆን ለምስጋናና ለጸሎት እንደሆነ ፈጣሪ ያውቃልና፡፡ እግዚአብሔርን የምትወድ ነፍስ ስለያዝክ የሰይጣንን ስድብ እየናቅህ አመስግን፡፡ ያማረ የተወደደ ምስጋናህን ከከዳተኛና ከተሳዳቢ ከሰይጣን ለይቶ የሚያውቅ አምላክ ነው ያለህ፡፡ ምንም የሰይጣን ስድቡ ካንተ ምስጋናና ጸሎት ጋር አንድ የሆነ ቢመስልህም ምስጋናዎችህ በእግዚአብሔር ዘንድ ከስድቡ ጋር አንድነት ስለሌላቸው ንጹሐን ናቸው፡፡
ወደጄ ሰይጣንን እራሱ ውስጥህ ሆኖ ይሳደብና የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ጠቅሶልህ ‹‹መንፈስ ቅዱስን የሰደበ ኃጢአቱ አይሰረይለትም›› እያለ ይሞግትኃል ያስጨንቅኃል፡፡ ሰይጣን ይህንን ኃይለ ቃል፣ ብዙዎችን ለማታለል ተጠቅሞበታል፡፡ ‹‹መንፈስ ቅዱስን የሰደበ›› ማለት መንፈስ ቅዱስ ሕፁፅ ያለ፣ ከሦስቱ አካላት አንዱ አይደለም ብሎ የካደ ኃጢአቱ አይሰረይም ማለት ነው፡፡ /ማቴ 12÷31/
ስለዚህ የሰይጣንን ስድብ በውስጥህ ተቃቀመው እንጂ ‹እኔ ነኝ፣ እግዚአብሔር ቢቀስፈኝስ፣ በጠራራ ፀሐይ መብረቅ ቢያወርድብኝስ: ጸሎቴን አይሰማኝም›› እያልክ ነፍስህን አታስጨንቃት ነፍሳዊ ሰላሟንም አታሳጠት፡፡ ይህ ፈተና ያንተ ብቻ ሳይሆን የአብዛኛው ምዕመናን ፈተና ስለሆን ሐሳቡን አታዳምጥ ተቃወመው፡፡
"ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቷል" ት.ሆሴ 4÷6
"ከትውልዱ ማን አስተዋለ" ት. ኢሳ 53÷8
ክፍል ሃያ ስምንት
የአጋንንት ፈተና በአጽዋማት ወቅት!
ይቀጥላል .....
ሰኔ 3-10-12
አዲስ አበባ

Tuesday, August 18, 2020

የአየር አጋንንት ፈተና በአጽዋማት ወቅት

/ያላወቅነው ያልነቃነው ግን ብዙ በረከት ያጣንበት/
በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም
አጋንንት በሕይወታችን የሚያደርስብንን ችግር እስክናውቅ እንቸገራለን፣ ውጊያው እስኪገባን ግራ እንጋባለን፣ እውነቱ እስኪገለጥልን እውነቱ ሐሰት ይመስለናል፡፡
ሼር በማድረግ ለወዳጆ አዳርሱ!
ተወዳጆች ሆይ በክፍል ሃያ ሰባት የአየር አጋንንት በልባችን አድሮ እግዚአብሔርን፣ እመቤታችንን እና ቅዱሳንን እንዴት እንደሚሳደብ አይተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ የአየር አጋንንት በአጽዋማት ወቅት እንደሚፈትነን እናያለን፡፡ የቅዱሳን አምላክ ምስጢሩን ይግለጽልን፡፡
ወዳጆቼ የአየር አጋንንት ከመቼውም በበለጠ በተንኮል ሥራ የሚጠመደው በአጽዋማት ወቅት ነው፡፡ እንደ ዓቢይ ፣ ገና፣ ሐዋርያት እና ፍልሰታ ያሉ የአዋጅ አጽዋማት ላይ ከመቼውም በበለጠ በጸሎት ጠንከር ስለምንል አጋንንቱ በፈተና ጠንከር ብሎ ይመጣል፡፡ የአየር አጋንንት በአዋጅ አጽዋማት ወቅት ቤተ ክርስቲያን ሄደን እንዳንጸልይ በማሳነፍ፣ በቤታችን እንዳንጸልይ በማይረባ ምክንያት በማደናቀፍ፣ ጸሎታችንን በማስታጎል የጸሎት በረከታችንን ያሳጣናል፡፡ እንኳን እኛ በገዳም ያሉ አባቶችም የአጋንንት ፈተና የሚበዛባቸው በአጽዋማት ወቅት ነው፡፡
አንዳንዶቻችን የአዋጅ ጾም ሲመጣ በፉከራ ‹‹ይህንን ጾምማ በጾም በጸሎት ነው የማሳልፈው›› ብለን ለራሳችን ቃል እንገባለን፡፡ ግን እንኳን የገባነውን ልንተገብር የባሰ ስንፍናና ኃጢአት ውስጥ ተዘፍቀን ያለ ሰዓት በጠዋት ከጾም እስከ ፍስክ ያሉትን ምግቦች ስልቅጥ አድርገን እንበላለን። መጠጥ የምንጠጣውም ‹‹ይሄን ጾምማ መጠጥ የደረሰበት አልደርስም›› እንላለን፡፡ ከቀናት በኋላ እዛው እንገኛለን፡፡ በሥጋ ፍትወት በዝሙት የምንፈተነውም ‹‹ይሄን ጾም ከዝሙት ርቂ እራሴን ጠብቂ አሳልፋለሁ›› እንላለን ግን ከበፊት የበለጠ በዝሙት ተፈትነን እንወድቃለን፡፡
በተለያዩ ፈተናዎች ጸሎት የተውን ‹‹ጾሙ ብቻ ይግባ ወዳሴ ማርያሙ፣ አርጋኖኑ፣ ሰይፈ ሥላሴው፣ ዳዊቱ ወዘተ አይቀረኝም ተግቼ ጸልያሁ›› እንላለን፡፡ ግን እንኳን ውዳሴ ማርያም፣ ዳዊት ቀርቆ አንድ አቡነ ዘበሰማያት መጸልይ አቅቶች ማታ ስንፍና ተጭኖን ሌሊት እንቅልፍ ጥሎያ ያለ ጸሎት እንውላለን እናድራለን፡፡ ስግደት ለመስገድ በዓለ ሃምሳ ከለከለኝ ይምጣልኝ ጾሙ ብለን የፎከርነው ጾሙ ሲመጣ ስንፍናን እንደ ባርኔጣ እራሳችን ላይ ጭነን፣ የወገብ፣ የጉልበት ችግር አለብኝ ብለን እንኳን የትሩፋት፣ የተጋድሎ ስግደት ልንሰግድ ቀርቶ ጸሎት ከመጀመራችን በፊት ሦስት ጊዜ ለሥላሴ የአምልኮ ስግደት መስገድ የሚያቅተን እንሆናለን፡፡
ንስሐ ለመግባት የስንት ዓመት ቀጠሮ ይዘን ጾሙን ስንጠባበቅ ጾሙ ሲመጣ እንኳን ንስሐ ለንገባ በኃጢአት ተዘፍቀን ግራ ስንጋባ ጾሙ ያልፈናል፡፡ ወሬ ለማውራት ሁለት ሰዓት ብንቆም ጉልበቴን ወገቤን የማንል ጸሎት፣ ስግደት ስንጀምር ሳይሆን ገና ስናስብ እንደ አዛውንት በሕመም መዓት እንያዛለን፡፡ ሌሊት ለጸሎት እነሳለሁ ብለን ማታ በስልካችን አላርም ሞልተን ግን እንደ እከ ለሽሽሽሽ ብለን ተኝተን እኛ ሳንነሳ ነግቶ ወፎ ጩኸት አሰምቶ ይቀድመናል። ወዳጆቼ  ይህ የሚያሳየን በአጽዋማት ወቅት ከፍተኛ የአጋንንት ውጊያ እንዳለብን ነው፡፡ በጾም ወቅት ካሰብነው በባሰ አንዳች መንፈሳዊ ነገር ሳንተገብር ጾሙ ያልፈናል፡፡ እኛም በእጃችን ባለው ጾም ሳንጠቀም ወደ ፊት በሚመጣው ባልጨበጥነው ጾም ተስፋ እናደርጋለን፡፡
አጋንንት የበለጠ የኃጢአት ሕይወት ውስጥ ከትቶ፣ እኛን ከእግዚአብሔር ጋር አለያይቶ ለማስቀርት በአጽዋማት ወቅት በዝሙት፣ በስካር፣ በሱስ ወዘተ ይፈትነናል፡፡ ባለ ትዳሮችንም ከጾሙ በረከት ለማራቅ፣ በፍትወት በማስጨነቅ ይፈትናቸዋል ይጥላቸዋል፡፡ በአዋጅ የታዘዝነውን ጾም በርትተን እንዳንጾም ጥውልውል የሚያደርግ የረሃብ ስሜት እና የተለያየ ሕመም እንዲሰማን በማድረግ ያለ ሰዓት እንድንበላ ብሎም ጾሙን አፍርሰን የፍስግ እንድንበላ ያደርገናል፡፡
አንዳንዶች ሕመማቸው የሚቀሰቀሰው፣ ጨጓራቸውን የሚያማቸው በአጽዋማት ወቅት ነው፡፡ እነዚህ ሕመሞች ለአጋንንቱ ሽፋን ስለሚሆኑ ማንም ጾም በመጣ ቁጥር የሚነሳበትን ሕመም የአጋንንት ፈተና ነው ብሎ ለመቀበል ይቸገራል፡፡ ስለዚህ አጋንንት በደዊያት እየተመሰለ፣በሕመም እያታለለ እንደሚጫወትብን ማሰብ አልቻልንም፡፡ በልቶ እንጂ ጾሞ የሞተ ሰው ስለሌለ ከነችግራችን ልንጾም ይገባል፡፡
ጾም በመጣ ቁጥር አጋንንት የውስጥ ሕመም የሚቀሰቅስብን አንደኛ አጋንንት ጾም ስለማይወድ የእሱን ባሕርይ በቀላሉ ከእኛ ጋር ለማዋሐድ ይመቸዋል፡፡ ሁለተኛ ጾም እንዳንለምድ ያደርገናል፡፡ ሦስተኛ የማንጾም ከሆነ እንበላለን እንጠጣለን ስለዚህ በሥጋ ፍትወት በቀላሉ ለመፈተን ይመቸዋል፡፡ አራተኛ ጾም እግዚአብሔርን የምናገለግልበት በረከት ስለሆነ ከጾም አገልግሎት ለማራቅ ይመቸዋል፡፡ ነቢይት ሐና እግዚአብሔርን በጾም በጸሎት ሰማንያ አራት ዓመታት አገልግላለችና፡፡ /ሉቃ 2÷37/ አምስተኛ በመጾማችን የምናገኘውን በረከት እና መንፈሳዊ ኃይል እንዳይኖረን ያደረጋል፡፡ ስድስተኛ ጾም አጋንንትን ከእኛ የምናርቅበት፣ የምንላቀቅበት መንፈሳዊ የጦር ዕቃ ስለሆነ የማንጾም ከሆነ አጋንንቱ በውስጣችን ተመችቶት ደልቶት ይኖራል፡፡ ሰባተኛ የማንጾም ከሆነ አንጸልይም ስለዚህ እግዚአብሔር እንዳይለመነን ያደርገናል፡፡ ነቢዩ ዕዝራ ‹‹ስለዚህም ነገር ጾምን፣ ወደ እግዚአብሔርም ለመንን፤ እርሱም ተለመነን›› ያለው እግዚአብሔር በጾማችን እንደሚለመነን ያሳየናል፡፡ /ዕዝ 8÷23/
ነቢዩ ዳዊት ‹‹ነፍሴን በጾም አስመረርኳት›› ይላል፡፡ እኛ ግን ነፍሳችንን በጾም ሳይሆን በመብል በመጠጥ ነው የምናስመርራት፡፡ /መዝ 69÷10/ ስለዚህ የአየር አጋንንት እኛ የተለያየ ክፉ መናፍስት በእኛ ሕይወት በመግባት እንዳይፈትነን በጾም መጠንከር አለብን፡፡
‹‹ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቶአል›› ት.ሆሴ 4÷6
‹‹ከትውልዱ ማን አስተዋለ?›› ት.ኢሳ 53÷8
ክፍል ሃያ ዘጠኝ
የአየር አጋንንት ራሳችንን እንድናጠፋ ያደርገናል
ይቀጥላል …….
ሰኔ 6-10-12 ዓ.ም
አዲስ አበባ

Tuesday, August 11, 2020

የአየር አጋንንት እና የቤተሰብ ዛር ራሳችንን እንድናጠፋ ያደርገናል

በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም
አጋንንት በሕይወታችን የሚያደርስብንን ችግር እስክናውቅ እንቸገራለን፣ ውጊያው እስኪገባን ግራ እንጋባለን፣ እውነቱ እስኪገለጥልን እውነቱ ሐሰት ይመስለናል፡፡
ሼር በማድረግ ለወዳጆ አዳርሱ!
ተወዳጆች ሆይ ዛሬ በራሴ በግል ጉዳይ በመዘግየቴ ይቅርታ እጠይቃለሁ። በክፍል ሃያ ስምንት የአየር አጋንንት በአጽዋማት ወቅት እንዴት ባለ ፈተና እንደሚፈትነን አይተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ የአየር አጋንንት እና ግብር የለመደ የቤተሰብ ዛር እራሳችንን እንዴት ለሞት እንደሚዳርገን እናያለን፡፡ የቅዱሳን አምላክ ምስጢሩን ይግለጽልን፡፡ ወዳጆቼ የአየር አጋንንት እና የቤተሰብ ዛር የመጨረሻው ግባቸው እኛን የሰው ልጆች አሰቃይቶ መግደል ነው፡፡ ይህንን ተንኮሉን በብዙዎች ላይ እየተገበረ ነው፡፡ በዓለማችን ላይ ራስን የማጥፋት ችግር እየባሰ መጥቷል፡፡ ሞልቶናል ተርፎናል የሚሉት ምዕራባውያን ራስን የማጥፋት ችግር ግራ እያጋባቸው ይገኛል፡፡
ምዕራባውያን ምንም ሳይቸግረው ራሱን በሚያጠፋ ዜጋቸው ግራ እየተጋቡ ነው፡፡ ምክንያቱም በራሱ ፈቃድ ለመሞት ምክንያት የሌለው ሰው ራሱን እያጠፋ ስለመጣ ነው፡፡ ይህ ድርጊት እኛም ሀገር እየተለመደና ለቤተሰብ የእግር እሳት እየሆነ መጥቷል፡፡ ብዙዎቻችንም በተለይ የምናውቀው፣ በደንብ የምንቀርበው ሰው ራሱን ካጠፋ ‹‹እንዴት ራሱን ያጠፋል? ምን ነካው?›› እያልን ሟች ላይ እንበይናለን፡፡
ግን ራሱን ካጠፋው ሰውዬ ጀርባ ያለውን አጋንንት በመንፈሳዊ ዓይን ካየን ሟች የአየር አጋንንት እና የቤተሰቡ ግብር የቀረበት ዛር የሞት ሰለባ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ በሰፊው እንዳየነው የአየር አጋንንት አእምሮንና ልቦናን ተቆጣጥሮ ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው ‹‹የማልፈልገውን አደርጋለሁ፣ ይህን የማደርገው እኔ ሳልሆን በእኔ ያለ ኃጢአት ነው›› ብሎ የገለጠው አጋንንት ሰው ልብና እና አእምሮ ውስጥ በመግባት ልቡን ሰውሮት ራሱን እንዲያጠፋ ያደርገዋል፡፡
ማንም በራሱ ላይ ጨክኖ ራሱን ለማጥፋት የሚሞክር የለም፡፡ ግን በተፈጠረብን ችግር፣ ባጋጠመን አስቸጋሪ ነገር ውስጣችን የገባው የአየር አጋንንት እያበሳጨን፣ ራሳችንን መቆጣጠር እያቃተን፣ እያወቅን ግን ልቦናችንን ሰውሮ ራሳችንን በገመድ አልያም በመድኃኒት፣ በመርዝ: ከፎቅ ላይ በመወርወር እና በሌሎች ዘዴዎች ራሳችንን እንድናጠፋ ያደርገናል፡፡ የዘንድሮ አጋንንት ትንሽ ለየት ያለ ይመስለኛል፡፡ በፊት መርዝ በማጠጣት እና በገመድ ነበር የሚገድለው ዘንድሮ ከሳይንስ ተባብሮ ሰዎችን በቀላሉ እራሳቸውን የሚያጠፉበትን በማስተማር የእጅ ደም ስርን በማስተልተል ይገድላል፡፡ በዚህ ስልት ስንቱ ወጣት ለሞት በቅቷል፡፡
ወዳጆቼ መንፈስ ቅዱስ የራቀው፣ አጋንንት የቀረበው ሰው ራሱን ያጠፋል፡፡ እኛ ደግሞ የአጋንንቱ የሞት ደባ ስለማይታየን ሟቹን ተጠያቂ እናደርጋለን፡፡ ይህ ብቻ አይደለም የአየር አጋንንት ልቦናችንንና ሕሊናችንን ከተቆጣጠረ መኪና ሥር በመክተት፣ ከባሕር፣ ገደል በመክተት፣ ራሳችንን በመሣሪያ በመምታት እንድናጠፋ ያደርገናል፡፡ ዛሬ ስንቱ በአየር አጋንንት ግፊት ራሳቸውን እያጠፉ አጋንንቱ ሳይሆን ሟቹ እየተወቀሰ ይኖራል፡፡ የአየር አጋንንት ውስጣችን ከገባ ምንም ሊያደርገን ስለሚችል በመንፈሳዊ ተጋድሎ በመበርታት ልናርቀው እና እኛም ልንርቀው ይገባል፡፡
ወዳጆቼ ከላይ እንደጠቀስኩት በተለይ ግብር ለምሳሌ ደም፣ እርድ የለመደ የቤተሰብ ዛር ካለ ቤተሰቦቻችን የዛሩን ግብር ትተው፣ ንስሐ ገብተው ሲተዉት አጋንንቱ ልጆች እና የልጅ ልጆች ላይ በመደር እርስ በእርስ በማባለት፣ ደም በማፋሰስ፣ የሰውንም ደም በማፍሰስ እና እራሳቸውን እንዲያጠፉ ያደርጋቸዋል፡፡ አጋንንት ስንቱን በተኙበት በማነቅ ለሞት ዳርጓል፡፡ ቡና እየጠቱ አጋንንት አንቋቸው የሞቱ አሉ፡፡ አንዳንድ የዋሆች ‹‹አጋንንት የመግደል ሥልጣን የለውም፣ እኔን መፈተን እንጂ መግደል አይችልም›› ይላሉ፡፡ አጋንንት በጾም፣በጸሎት በስግደት ተጠምዶ፣ ሕገ እግዚአብሔር ወዶ እና ፈቅዶ የሚፈጽም ከሆነ በእውነትም ሥልጣን የለውም፡፡
ግን ያለ ጾም፣ ጸሎት፣ ስግደት እና ያለ ትሩፋት የሚኖር ከሆነ አይደለም በሥጋው መግደል፣ በነፍሱ ሲዖል መዶል ይችላል፡፡ ሰው በቀጥታ ከእግዚአብሔር ሲርቅ በተዘዋዋሪ ከአጋንንት በመጣበቅ ነው የሚኖረው፡፡ ትዝ ካላችሁ ጌታችን እኛን ለማዳን በቀራንዮ በተሰቀለ ጊዜ የማያፍረው ሰይጣን በሕማም፣ በስቃይ እና በሞት አፋፍ ያለውን ፈጣሪ ፍጡር መስሎት ቀረብ ብሎ ‹‹ሥጋውን ከነፍሱ ለይቼ፣ ሥጋውን በመቃብር ነፍሱ በሲዖል ገዝቼ እኖራለሁ›› ብሎ ቀርቦ ውርደት ተከናንቦ ሄዷል፡፡ ልብ በሉ በፈተና፣ በችግር፣ በቤተሰብ ሐዘን፣ በማጣት ወዘተ በድንገት እራሳችሁን አጥፉ አጥፉ እያለ ሞት ሞት ከሸተታችሁ ቆም ብላችሁ አስቡ፡፡ እንዲህ ዓይነት ክፉ የሞት ሐሳብ የእናንተ ሳይሆን ሕይወታችሁን ሳይሆን ሞታችሁን የሚፈልገው የአጋንንት ክፉ ሐሳብ እንደሆነ አውቃችሁ ተጠንቀቁ ንቁ፡፡
ወዳጆቼ በተረታችን ‹‹የበሰበሰ ዝናብ አይፈራም›› አይደል የምንለው፡፡ ተስፋ የቆረጠ፣ የእኛን ነፍስ በሲዖል እየዋጠ የሚኖረው አጋንንት እኛን ለመግደል እና ለማጥፋት የሚቦዝን ስላልሆነ በጸሎት መበርታት እና መትጋት እንኳን ከአጋንንት ከሲዖል ሞት ያድነናል፡፡
‹‹ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቶአል›› ት.ሆሴ 4÷6
‹‹ከትውልዱ ማን አስተዋለ?›› ት.ኢሳ 53÷8
ክፍል ሠላሳ
የአየር አጋንንት እና የብኩንነት ሕይወት
ይቀጥላል …..
ሰኔ 7-10-12
አዲስ አበባ

Tuesday, August 4, 2020

የአየር አጋንንት እና የብኩንነት ሕይወት

በቀሲስ ሄኖክ ወልደ-ማርያም
አጋንንት በሕይወታችን የሚያደርስብንን ችግር እስክናውቅ እንቸገራለን፣ ውጊያው እስኪገባን ግራ እንጋባለን፣ እውነቱ እስኪገለጥልን እውነቱ ሐሰት ይመስለናል፡፡
ሼር በማድረግ ለወዳጆ አዳርሱ!
ተወዳጆች ሆይ በክፍል ሃያ ዘጠኝ የአየር አጋንት እና የቤተሰብ ዛር እራሳችንን እንድናጠፋ እንደሚያደርገን አይተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ አጋንንት እንዴት በሕይወታችን ብኩን እንደሚያደርገን እናያለን፡፡ የቅዱሳን አምላክ ምስጢሩን ይግለጽልን፡፡ ወዳጆቼ በሰፊው እንዳየነው የአየር አጋንንት በተንኮል የተካነ ስለሆነ በሕይወታችን ብኩን እንድንሆን ያደርገናል፡፡  አጋንንት ቀድሞ በተሰጠው ጸጋ ስላልተጠቀመ እኛም በሕይወታችን እግዚአብሔር በሰጠን ጸጋ መክሊት እንዳንጠቀም ያደርገናል ያባክነናል፡፡ ሕይወታችን ብኩን፣ ትዳራችን ብኩን፣ ገንዘባችን ብኩን፣ የጨበጥነው እንደ ጉም እየተነነ፣ የያዝነው እየመነመነ ባዶ ያደርገናል፡፡ የአየር አጋንንት ከሰላቢ መንፈስ ጋር በማበር የምናገኘውን፣ የያዝነውን ይስልብብናል፡፡
ወዳጆቼ ስለ ብኩንነት ካነሳን አጋንንት በተለያየ እና በማናውቀው መንገድ ብኩን ያደርገናል፡፡ አንዳንዶቻችንን ለዘመናት በመጠንቀቅ እና በመጠበቅ ይዘን የቆየነውን ለተክሊል ክብር ያሰብነውን ድንግልና በማባከን በዝሙት ለክፎን የማንወጣበት ሕይወት ውስጥ ከቶ ያባክነናል፡፡ ሌሎቻችንን ገዳማት፣ አብያተ ክርስትያናት በመሄድ፣ በመጸለይ፣ በመመጽወት ያገኘነውን ጸጋ በዝሙት ጥሎን ጸጋችንን አስጥሎን የመንፈሳዊ ብኩን ያደርገናል፡፡ የበረቱትን ቅዱስ ቁርባን በመቀበል ያገኙትን መለኮታዊ ጸጋ በሐሜት፣ በምቀኝነት ጸጋቸውን አስጥሎ የቆራቢ ወረኛ አድርጎ ብኩን ያደርጋቸዋል፡፡ ወጥተው ወርደው፣ ሌት ተቀን እንቅል አጥተው ሠርተው ያገኙትን ገንዘብ በመጠጥ፣ በአልባሌ ውሎ፣ በመልካም ጓደኝነት አስመስሎ ገንዘባቸውንም ሕይወታቸውንም ብኩን ያደርጋል፡፡ ብቻ የአጋንንትን ተንኮሉን፣ ውጊያውን ካላወቅን በሥጋም በነፍስም ብኩን እንሆናለን፡፡ 
ወዳጆቼ አንዳንዴ በኪሳችን፣ በቦርሳችን ያያዝነው ገንዘብ የረባ ነገር ሳንገዛበት፣ ምኑንም ሳናውቅ ገንዘቡ የለም፡፡ አንዳንድ ሞኞች ‹‹አሁን አጋንንት ገንዘብ የሚሰልበው እንደ ሰው አይጠቀምበት፣ምን ይሠራለታል›› እያሉ እየተሰለቡ ይሟገታሉ፡፡ ወዳጄ አጋንንት ኑሮህን ለማቃወስ፣ በገንዘብህ ያሰብክበት ቦታ እንዳትደርስ ገንዘብህን ይሰልበዋል፡፡ ያኔ በማታውቀው ስልት ገንዘብህ ከእጅህ ሲወጣ፣ የመደናገጥ ጣጣ ይመጣል፡፡ አሥራት ያልወጣበት ገንዘብ፣ ጸሎት የሌለበት ሕይወት፣ የእግዚብሔር ረድኤት ስለማይኖረው የአጋንንት መጫወቻ ነው የሚሆነው፡፡
በተለይ አንዳች ጥሩ ነገር ካለን፣ ባለን ለመለወጥ ስንጥር፣ አጋንንት የማጨናገፊያ ድንበር እየሠራ የሙሉ ጎዶሎ ያደርገናል፡፡ ያለንን ይነጥቀናል፣ ያገኘነውን ያባክንብናል በዚህም ሕይወት ለእኛ የቀን ጨለማ ይሆናል፡፡ ግን አሁንም በመባከን ሕይወት ውስጥ ካለን ወደ እግዚአብሔር በንስሐ ተመልሰን፣ በጸሎት የምንማልል ከሆነ እግዚአብሔር በአጋንንት የተንኮል ሴራ የባከነ ሕይወታችንን በመቀየር አዲስ የሕይወት ምዕራፍን ይከፍትልናል፡፡
ብዙዎቻችን በአንድም በሌላም ብኩን ሆነናል፡፡ የእውቀት ብኩን፣ የማስተዋል ብኩን፣ የጊዜ ብኩን፣ የቸርነት ብኩን፣ የአዛኝነት ብኩን፣ የዕድሜ ብኩን፣ የበረከት ብኩን፣ የፍቅር ብኩን፣ የስኬት ብኩን፣ የትዕግሥት ብኩን፣ የሥራ ብኩን፣ ወዘተ ሆነናል፡፡ አጋንንት በተለያየ የፈተና ስልት ሕይወታችንን ሲያባክን ከመንቃት እና ወደ እግዚአብሔር ከመጠጋት ይልቅ ሥጋዊ አስተሳሰብ ተጭኖን በራሳችን ላይ ያለ ቀስቃሽ ተኝተናል፡፡
ጌታችን ዛሬ የምንኖረውን የብኩንነት ሕይወት በሉቃስ ወንጌል ላይ በምሳሌ አስተምሮናል፡፡ ከወላጅ አባቱ ‹‹ገንዘቤን አካፍለኝ›› ብሎ የተለየው ወጣት ገንዘቡን ይዞ ወደማያውቀው ሀገር ተሰዶ በዚያም ገንዘቡን በትኖ ኖረ፡፡ ገንዘቡ ሲያልቅ የሚበላው ቢያጣ ከአንዱ ጋር ተዳበለና የእርያ ጠባቂ ሆነ፡፡ ከረሃቡ ጽናት የተነሳ የእሪያዎችን አሰር ለመብላት ተመኘ፡፡ ግን እሪያዎች የሚበሉትን አሰር የሚሰጠው ጠፋ፡፡ በመጨረሻም ወደ ልቡ ተመልሶ፣ በስሕተቱ አልቅሶ ወደ አባቱ ቤት በክብር ተመልሷል፡፡ /ሉቃ 15÷11-32/
እኛም ከእግዚብሔር ጋር ስንለይ ነው ከአጋንንት ጋር የምንዳበለው፡፡ ከእግዚአብሔር ስንለይ፣ የአጋንንት ሲሳይ እንሆናለን፡፡ አጋንንቱም እንደ ጠፋው ልጅ የእኛንም ውድ ሕይወት እያባከነ፣ ጸጋችንን በኃጢአት እያስበተነ ብኩን ያደርገናል፡፡ የጠፋው ልጅ ወደ ልቡ ተመልሶ ወደ አባቱ ቤት በመምጣቱ ከቀድሞው የተሻለ ሽልማት እና ሕይወት አግኝቷል፡፡
እኛም ከመባከን ሕይወት ወጥተን፣ ወደ አባታችን ወደ እግዚአብሔር ከተመለስን አዲስ የበረከት ሕይወት ይኖረናል፡፡ የጠፋው ልጅ የአባቱን ቤት ማዕድ ንቆ፣ የእሪያን አሰር ለመብላት ናፍቆ ነበር፡፡ ወደ አባቱ ቤት ሲመለስ ግን ፍሪዳ አርዶለት ደግሶ ነው የተቀበለው፡፡ እኛም የእግዚአብሔርን የበረከት ሕይወት ረግጠን፣ ንቀን የአጋንንትን የመከራ እንጀራ ነው የበላነው፡፡ ግን ወደ እግዚአብሔር ከተመለስን ከመለኮት ማዕድ ከቅዱስ ቁርባን ተቋድሰን፣ በጸጋው ተሸልመን በክብር እንኖራለን፡፡
ስለዚህ አጋንንት የነጠቀንን ሊመልስልን የሚችለው እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ አጋንንት የወሰደብንን ሊሰጠን የሚችለው እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ከእግዚአብሔር መለየት ልዩ ብኩንነት ነው፡፡ እኛ ብኩን የሆነው አጋንንት ሲጠናወተን ሳይሆን እግዚአብሔር ሲለየን ነው፡፡ ከእግዚብሔር መለየት ብኩንነት ብቻ ሳይሆን የቁም ሞት ነው፡፡ እኛ በቁማችን ለአጋንንቱ ሞተንለት ነው እርሱ የሚገድለን፡፡ ስለዚህ ከሕይወት ብኩንነት ለመውጣት ወደ እግዚአብሔር መጠጋት ያስፈልጋል፡፡
‹‹ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሳ ጠፍቶአል›› ት.ሆሴ 4÷6
‹‹ከትውልዱ ማን አስተዋለ?›› ት.ኢሳ 53÷8
ክፍል ሠላሳ አንድ
የአየር አጋንንት የተረጋጋ መንፈስ እንዳይኖረን ያደርጋል
ይቀጥላል ……
ሰኔ 8-10-12 ዓ.ም
አዲስ አበባ